Wednesday, December 21, 2011


                  ሀበሻ በየመን
     ለመሆኑ እንዴት ናችሁ? አቀማመጣችሁን አላልኩም። ኮምፒዩተራችሁ ላይ አፍጥጣችሁ ይመስለኛል የምታነቡት። እሺ በስደት ያላችሁ..የስደት ኑሮ ቅብብሎሹ እንዴት አድርጓችሁዋል? እንዴ ምነው ተገረማችሁ? ልክ ነኝ እኮ ኑሮ ቅብብሎሽ አይደል እንዴ? ሰኞ ወደ ማክሰኞ ሲጠልዘን፤ ማክሰኞ ተቀብሎ አባብሎ ወደ ረቡዕ ሲወረውረን .. መስከረም ወደ ጥቅምት ሲጠልዘን፤ ጥቅምት ለህዳር፣ ህዳር ለታህሳስ…እያለ ቅብብሎሹ በርትቶ ጠውለዛው ደርቶ እዚህ ደርሰን የለ? አሁንም ቅብብሎሹ አንዱ ወደ አንዱ መለጋቱ  እንደቀጠለ ነው። ገና እንለጋለን፤ እንጠለዛለን። ስንት አመት ይሆን በቅብብሎሹ ውስጥ የምናሳልፈው?...

      አቦ ዛሬ ጣፋጭ ወግ እናውጋ ነው የሚባለው የብሶት ቁስል እንከክ እንበለው? ስለስደት ብናወራ አይመቻችሁም? ከስደትም ስደት አስከፊውን የአረብ ስደት…ከአረብ ሀገርም ስለየመን እናውራ። ምነው  ፊታችሁ ጨፈገገ? የስደት ነገር ሲነሳ ቤተሰብ ትዝ አላችሁ? ወደ እውነታው እንምጣ ከኑሮ ጋር ያለውን ትግል ለማሸነፍ ፣ ለመሸነፍም ቢሆን የትግል ሜዳ አድረጋችሁ የመረጣችሁት የመንን ነው እንበል። የመንን በሀሳብ ለመቃኘት ተዘጋጁልኝ። የመን ደሞ ጥሩም አለ መጥፎም አለ። ሞቱም፣ ዱላውም፣ መደፈሩም፣ ማግኘት፣ ማጣቱም ሁሉም አለ። ከሌሎች በከፋ ሁኔታ አለ።

      የመንም ይኖራል። ለጉድ!!..ይኖራል። ኑሮ ከተባለ ሀበሻ በየመንም እየኖረ ነው ማለት ይቻላል። ይህም ስደት ነው። ወደ ተሻለው ሳይሆን…ብዙ ብዙ እውነት የማይመስሉ እውነቶች የተሰገጡበት ህይወት ነው በየመን ያለው። ኑሮ ካሉት ፍሪጅም ይሞቃል ኮካኮላን ያስተረተው በየመን ያለ ሀበሻን ኑሮ ታይቶ ነው ማለት ይቻላል። አይደለም ካላችሁም አሁን እኔ ብያለሁ። ማነው የሚከራከረኝ? ከየመን በከፋ ሁኔታ ላይ ሱማሊያ የሚኖሩ መኖራቸውን ሳትረሱ ማለት ነው። አትቸኩሉ እኔው እነሱንም አሳያችሁዋለሁ።

      ችግር የማይነቅለው የለም። ኢየሱስ ክርስቶስም ተሰዷል። ነብዩም ተሰደዋል። አረ ቆራጡ እና ተፈጥሮን በቁጥጥር ስራ እናውላለን ያሉት ኮረኔል መንግስቱም ተሰደዋል። እኛ ለስደት አዲስ አደለንም። አለም ለስደት አዲስ እንዳልሆነ ሁሉ እኛም እየተሰደድን ነው። ተሰደናልም ገናም እንሰደዳለን።

    ሀበሻ በየመን እጅጉን አሰልቺ የሆነ ደግሞም ያልሆነ ዝብርቅርቅ ህይወት ከጥሩ ጎኑ መጥፎው ያመዘነበት ኑሮ መሀል ተሰንጎ ነው የሚኖረው። እርስ በእርስ የጎሪጥ መተያየት፣ ጥርጣሬ.. የበዛበት ነው ህይወቱ። መሰደብ.. <<ያ-ሀበሺ..ሸቃላ..ኦሪያ..ያ ሱማሌ..ያ አስወድ..>> የዘውትር መጠሪያ ኤጭ!..ድሮስ ክብር በሀገር አይደል? ነው እንጂ። ክብር በሌለበት ተንቆ፣ ተዋርዶ መኖር ያውም ከራስ ባልተሻለ ሰው። የመን ያለ የሀበሻ ቁጥር እንዲህ በዋዛ የሚሰላ አይደለም። በህጋዊ መንገድ ያለውና ህጋዊ ያልሆነው ከ70- 80 ይደርሳል ተብሎ ይገመታል። ታዲያ ይገመታል ነው። ይበልጣል እንጂ አያንስም። ወደ ሳዑዲ አረቢያ ተጓዡም ቀላል ተብሎ የሚጠራ አይደለም።

     በእናታቸው፣ በአባታቸው፣  አልፎም በአያታቸው ኢትዮጵያ የሆኑ…ግማሽ ጎናቸው የመናዊ ትውልደ ሀበሻ 5.000.000/ አምስት ሚሊዮን/ አካባቢ ናቸው። ይህ የሚያሳየው የየመንና ኢትዮጵያ ትስስር የጥንት መሆኑን ነው። በፊት የመኒዎች በችግር ወደ ሀገራችን ይሰደዱ ነበር። ዛሬ ነገር ተገልብጦ እኛ ወደ እነሱ  ሆኗል። አሁንም ቢሆን ግን ኢትዮጵያ ያለው የመናዊ ቁጥር በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ነው። ከዚህ ከዚህ ጋር በተያያዘ ሳይሆን አይቀርም የመን ከአረቢኛው ቀጥሎ አማርኛ በሰፊው ይነገራል።

    <<ገንዘብ ካለ…>> ሁሉም የመናዊያን የሚያውቋት ተረት ናት።<<እወዲሻሎ..ኢንደሚኖ…አንቺ..>> በሁሉም ዘንድ የተለመደች ቃል ነች። ልክ እኛ ጋር ማዘር ፋዘር..እንደተለመደ ሁሉ። ጫት ሲነሳ ሐረርን የማያነሳ የመናዊ የለም።

    የዛሬዋ የመን ጥንት ወይም በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ <<ሀገረ ናግራን>> እንደምትባል ታሪክ ያስረዳል።በመጽሀፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ <<ኤደን>> ደግሞ <<አደን>> ተብሎ መለወጡን አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ። ዋና ከተማዋ ሰነዓ ጥንታዊነቷን ለማስረገጥ ከንግስት ሳባ የንግስና ዘመን ጋር ቁርኝት እንዳለው ይጠቀሰል። የመናዊያን ንግስት ሳባ ኢትዮጵያዊ ሳትሆን የመናዊ ነች ብለው ያምናሉ። ግብጾች የእኛ ናት እንደሚሉት ማለት ነው። ሳባ የመን ውስጥ ማሪብ የተባለ ቦታ ቤተመንግስት አላት። ምክምያታቸው ይህ ብቻ ነው። አባቷ ማነው? እንዴት ንግስት ሆነች ምላሽ የላቸውም። ምሁሮቻቸውም ሳባ ኢትዮጵያን አስተዳድራለች እንጂ ኢትዮጵያዊ አይደለችም ሲሉ ሽንጣቸውን ገትረው…ሽንጥ አላቸው እንዴ? እንጃ!.. ብቻ ለአባባሉም ቢሆን እንበለውና ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከራሉ።

      በአንድ ወቅት ፋጡማ ሁሬቢ… ከተባለች እንጋፋ የየመን ጋዜጠኛ ጋር የጦፈ ክርክር አድርገናል።
   
    <<ለመሆኑ ኢትዮጵያ በውጭ ንጉስም ይሁን ንግስት የተዳደረችበት አጋጣሚ አለ ወይ? እንደዚህ አይነት ታሪክ አንብበሽስ ታውቂያለሽ? ካልሆነ ግን ድንገት አለም ያለወቀው ታሪክ ልናገኝ ነው ማለት ነው እና ማስረጃውን ስጭኝ?>> አልኳት። <<እምቢኝ!...ያባ ቢላዋ ልጅ ለማን ተገዛንና የመንን የእኛ ንጉሶች ማስተዳደራቸውን እንጂ እኛ በየመናዊያን ስለመተዳደራችን ማን ተናገረና ያለመረጃ ልቀበል?እምቢኝ……የአባት፣ አያቴን ታሪክ መድገም ቢያቅተኝ ጠብቄ እኖራለሁ>> እያለ ውስጤ ፉከራ ይሁን ቀረርቶ ብጤ ፎካከረ። ከሌሎች ጋርም እንዲሁ ተከራክሬያለሁ። እነሱን ለመርታት ከመሞከር ይልቅ ድንጋይ መፍለጥ ይቀላልና በእንጥልጥል እተወዋለሁ።

      ከክርስቶስ ልደት በሁዋላ በ575 ዓ.ም ጀምሮ ንጉስ አብርሃ ለ50 ዓመታት ልጆቹ 20 አመት የመንን ባስተዳደሩበት ወቅት አሁን ያለንባት ሰነዓ ከተማ ለአቢሲኒያ ዋና ከተማ ሆና አገልግላለች። በዛ ዘመን የተገነቡ ቤቶች ዛሬ ባብል የመን /የየመን በር/ በሚባለው ኦልድ ሰነዓ አካባቢ አሉ። የየመን ዋና የቱሪስት መስህብ ነው። በፎቶው ላይ የምታዩት ማለት ነው። ከአንድ ሺህ አመት በላይ ያስቆጠሩ 14000 ቤቶች አካባቢ አሉ። ሌላው ስለየመን አንስቶ ሳይወሳ የማይታለፍ የእርሻ ዘዴያቸው ነው። ለም አፈር የወርቅ ያህል ውድ ነው። ከመሬቱ ደረቃማነት የተነሳ የሚታዩትን አትክልቶች፣ የእህል አይነቶች ሲያዩ የመናዊያን ምን ያህል ጠንካራ እንደሆኑ ምስክሮች ናቸው። ለም የሆነውን አፈር ከሩቅ ቦታ ፈልገው ጭነው ያመጣሉ፣ ውሀ ከመሬት ለማውጣት እስከ 300 ሜትር ይቆፍራሉ።ያወጡትን ያጠጡታል፣ የፈለጉትን ይዘሩበታል። ያ- ደረቅ ድንጋያማ መሬት ህዝቡን አጥግቦ ያድራል።

     ሌላም ስለየመን ሲነሳ ሳይወሳ የማይታለፍ አለ።

    ጫት…….ጫት የህዝቡ መንቀሳቀሻ የደም ሴል ነው ማለት ይቻላል። ያለ ጫት ህይወት ያለ የማይመስላቸው ያገኙትን ሁሉ ለጫት የሚያውሉ ጥርሳቸው አልቆ ተፈጭቶላቸው በማንኪያ ሁሉ የሚወስዱ አሉ። በቀን ከ25000 ሺህ ሪያል በላይ /ከመቶ  አስር ዶላር በላይ/ ለጫት ወጪ የሚያደርግ ቤተሰብ በብዛት እንዳለ በአንድ ወቅት የመን ታይምስ ለንባብ ያበቃ መሆኑን አስታውሳለሁ።

    የመን ያለ ሀበሻ ባህሪውን፣ አብሮነቱን፣ መተሳሰቡን፣ ፍቅሩን፣ መተዛዘኑን፣ መደጋገፉን፣ መነቃቀፉን፣ ወሬ መውደዱን፣ ተንኮሉን፣ አብሮ መብላት መጠጣቱን፣ ሀሜቱን፣ በነገር መነቋቆሩን…ይዞ ነው የተሰደደው። ሀበሻ እርስ በእርሱ ፍቅር አለውም የለውምም የሚያሰኙ ብዙ እንከኖች አሉት። እዚህ ያለ ሀበሻ የወሬ ፍቅር አለው።

     ወሬ ይወዳል።

     የምን ወሬ ይወዳል ብቻ ነው? ወሬ በልቶ ወሬ ጠጥቶ፤ ወሬ ቀዶ ወሬ ሰፍቶ ነው የሚኖረው ያሰኛል። የመን ውስጥ ሀበሻ በገንዘብ እና ዕቃ ስርቆት አይደለም የሚታወቀው። ብዙም አይጠረጠርም። ስልክ ሰርቆ በመደወል ግን የሚያህለው የለም። ሱሱ ወሬ ነዋ!! ያማል ያሳማል።

    እዚህ ያለ ሀበሻ ሁሉ ህጋዊ አይደለም። በህጋዊ መንገድ የገባም አይደለም። አገባቡ በሁለት መንገድ የተከፈለ ነው። በባህር እና በአየር ነው የሚገባው። በባህር የሚገቡት የሚደርስባቸውን ስቃይ በተመለከተ ጥቂት ልበል።      
   
      ስለ የመን አሰቃቂ ጉዞ ከዚህ በፊት በባህር ስለሚደረግ ጉዞ፣ ሬሳው በየቦታው ውደቆ፣ የባህሩ ውሀ ሰውነት ላይ የሚፈጥረው ችግርን በተመለከተ …ያሰባሰብኩትን መረጃ በቪዲዮ መልክ አዘጋጅቼው ስለነበር እንድታዩት አስቀምጨዋለሁ። እዩት…
    
                                         በቀጣዩ እንገናኝ……….