Wednesday, August 1, 2012

ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በአረብ ሀገር
ክፍል  ሶስት
ለካ ራስ ማጥፋትምከባድ ነው?..አቃተኝ!!
      በግሩም ተ/ሀይማኖት

  ሁለት አንባቢዎቼ የሚናገሩትን አያውቁትም እና ይቅር በላቸው የሚያስብል አስተያየት አስፍረው አይቻለሁ፡፡ የወገን ስቃዩ አይነገር..የሚሰሩት ሀገርን የሚያሰድብ ጸያፍ ስራ አይነሳ የሚሉ ገጥመውኛል፡፡ ቅር አይለኝም ማንም እንዳቅሙ ማሰብ እንደሚችለው ነው የሚያስበው፡፡ ከአቅምህ በላይ አስብ፣ አገናዝብና ተረዳኝ ተብሎ አይወቀስም፡፡ የሌለውን አምጣ፣ ያልተሰጠውን ፀጋ ተላበስ አይባልም፡፡ ‹‹..ሁሉም በተሰጠው ጸጋ ያገልግል…›› አይደል የሚለው ቅዱሱ መጽሀፍ? ታዲያ ያለ ተፈጥሮው ጭካኔህን ትተህ ሰብዓዊ ሁን፣ የሰው ስራ ማራከስህን ትተህ ራስህ ሰርተህ አሳይ አይባልም፡፡ ያልተሰጠውን ከየት ሊያመጣ? ተፈጥሮው ማጥላላት እና ሰውን ማንጓጠጥ፣ ከማገናዘብ ይልቅ በጭፍን መጓዝ ከሆነ ከዚህ ጨለማ ያውጣህ ብሎ ወንድማዊ ጸሎት ከማድረግ ውጭ ቱ!..ቱ!..ያሳድግህ ብልግናህ ካንተ ይዝለቅ አይባልም፡፡ ምንም ቢሆን ወንድም ነው ክፉ ያስብ እንጂ ክፉ ማሰብ ከእኛ አይጠበቅም፡፡ መጥፎ ሀሳብ ከእኛ ዘንድ ይራቅ..

   የመን በባህር ስገባ ያየሁትን ስቃይ እና በባህር የሚገቡ ሁሉ የሚያዩትን መከራ በመጽሀፍ ለማዘጋጀት ከሶማሊያ ጀምሮ መረጃዎቼን እያሰባሰብኩ ቆየሁ፡፡ ቀድመውኝ ወደ የመን ለገቡትም ሆነ ከኋላዬ ለተከተሉኝ በዛ ያሉ ስደተኞች መጠይቅ ፎርም በትኜ መረጃ ጠይቄያለሁ፡፡ 27ሰው ቃለ-ምልልስ አድርጌያለሁ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 12 የሚሆኑን በኮንትራት ለቤት ሰራተኛነት መጥተው ጉዳት የደረሰባቸው ናቸው፡፡ ሁለቱ ለ20 አመት የመን የኖሩ የቀድሞ ባህር ሀይል ባልደረባዎች ናቸው፡፡ ከዱባይ ከመጡት ውስጥ 7 ያህሉን አናግሬያለሁ፡፡ ከዚህ ውስጥ ሁለቱን በሞባይል ስልኬ በድብቅ ነው የቀረጽኳቸው፡፡ ምክንያቱም ለቃለ-ምልልስ ከማሳመኔ በፊት ነገሩ በድንገት በመነሳቱ ነው፡፡ ከቀዳኋቸው በኋላ ግን አለሳልሼ ነግሬያቸዋለሁ፡፡ ለምሳሌ አሁን ታሪኳን ያቀረብኩት ልጅ መግቢያው ላይ እንደ ተናገርኩት ለምን እንዲህ አይነት ዝርጥጥ ቃላት ተጠቀምሽ ከባህል ስርዓታችን አንጻር ስላልኳት ነው መረር ያለ ነገር በእልህ ተናግራ ልታወራኝ የተነሳችው፡፡      

    ይህን ያስተዋለ፣ እውነቱን የሚያውቅ አንድ ሳሙኤል ተስፋዬ የተባለ አንባቢ ‹‹..በጣም የሚገርም ነው። አንዳንዶቹ የሚናገሩትን አይቁም። እንዴት ሰው ባልኖረበት ነገር አሳፋሪ መልስ ይሰጣል? እሱ ከሌላው ጋጠወጥ አድራጎት ካለው በምኑ ነው የሚለየው? /ወዳጄ አትሳሳት በምንም አይለይም፡፡ ፈስ ያለበት ዝላይ አይችልም በማለት አንድ እህቴ መልሳለታለች፡፡ ተደናቁረው ሊያደናቁሩነ የሞከሩት ሴቶች እህቶቻችንን ለአረብ በማቃጠር የሚሸጡ ሊሆኑ እንደሚችሉ መገመት ይቻላል፡፡ በአረብ ሀገር ነዋሪ ከመሆናቸው አልፎ ኢትዮሰፖት የሚባል ዌብሳይት ላይ ለገቢያ የሚያመቻች እርቃን ፎቶ የሚለጥፉ ናቸው፡፡ ለአብነት ይህን ክሊክ አድርገው ተመለከቱ…
http://www.ethiospot.com/photo/hubby-is-this-mar-like-tej-konjo-like-flower./ ለማንኛውም ልቦና ይስጠው ከማለት ውጪ ምን ይባላል? ግሩም ሃሳቦችህ እስካሁን አንዳንድ የተለያዩ ሚዲያዎች ነካኳቸው እንጂ እንዳንተ በግልጽ አላቀረቧቸውም ነበር፡፡ ዛሬም እድሜ ላንተ ጫፉ ላይ ቆመሃል። ነገ ድግሞ እኛም እያገዝንህ ወደ ውስጥ ትገባለህ ከዛም እኛ በአረብ አገር ያለን ሰዎች ምን ያክል ባህላችንን እያጎደፍን እንዳለን ሁሉም ያውቃል ማለት ነው፡፡ ከዛም በምክር ያለ ሆነው ለውጥ በእፍረት ይመጣል ማለት ነው። አንተም አሁን በበርሜል ያለውን ግድፈታችንን በማንኪያ ጨለፍከው እንጂ ገና ምንም አልነካኽውም። እናም ካንተ ብዙ እንጠብቃለን። አቀራረብህ በጣም ግልጽና የተብራራ ነው። ቀጥል።…››ሲል አደራውን የበለጠ አጥብቆብኛል፡፡ ምስጋናዬ የላቀ ነው እንዲህ ከጎን የሚሰለፍ ችግሩን የሚያውቅ ማግኘት መታደል ነው፡፡ ታዲያ ቃለ ይከበር እኛም እያገዝንህ ብለሀል፡፡

       ሌላው አንባቢዬ ደግሞ ‹‹..ያልከው ነገር እውነት ነው ምንም ስህተት የለውም የሚገርመው እንኳን ይህ ነገር ስህተት እንደሆነ ስትነግራቸው የሚመልሱልህ መልስ በጣም የሚያሳፍር ነው። ከሱዳን ወይም ከሌላ አገር ዜጋ ጋር መጋባታቸውና አብረው መኖራችው አይደለም ችግሩ፡፡ በአንድ ወንድ ሁለት ሶስቱ ሲጣሉ የሚታየው ነገር ነው ይበልጥ አንተነትህን እንድትጠላ የሚያደርግህ። እነሱም ቢሆኑ አብረው መዝለቅ እንደማይችሉ ነገር ግን ላላቸው በጣም አጭር ጊዜ ያውም የሕይወት አጋር ላለሆነ ሰው መደባደብ ብሎም እስከ መጋደል የሚያደርሱ አሉ፡፡ የኢትዮጵያዊ ስነ-ምግባር ኢትዮጵያ አየር መንገድ ተጥሎ ነው የተመጣው። ለማንኛውም ማወቅ ያለብን መልካም አስተሳሰብ እና መልካም ስነ-ምግባር ያላቸው ሴቶች የሉም ማለት አይቻልም አሉ። /አዎ እኔም አምናለሁ አሉ፡፡ ያውም አንገት ደፍተው የሚሰሩ…ከኢትዮጵያ ሲወጡ ለፍቅር አለያም ለትዳር ጓደኛቸው የሰጡትን ቃል የሚጠብቁ….በጣም ብዙዎች መልካም ስነ-ምግባር ያላቸው አጋጣሚም የረዳቸው….ሞልተዋል፡፡ ሁሌም ስናነብ እነዚህን ከግምት እናስገባ፡፡/  ነገር ግን መጥፎ ስነ-ምግባር ባላቸው ጥቂት ሰዎች ተሸፍነዋል።

     ተውጠዋል፡፡

     አበበች በስደት አገር ብታጠፋ አንድ ሃበሻ አጠፋች እንጂ አበበች አጠፋች የሚል የለም። ስለዚህ የብዙሃኑ በሆነ ስም ላይ ግለሰብ ወሳኝ መሆን አይችልም ሃሳብ ማቅረብ እንጂ። ለለውጥ ከሆነ ግን ግለሰብ የሚኖረው ሚና ትልቅ ሊሆን ይችላል። አሁንም አንተን የምልህ እንዲህ አይነት ነገሮችን በተከታታይ ፖስት ብታደርግ ለውጥ ሊመጣ ይችላል ብዬ አስባለሁ። ምክንያቱም ባሁኑ ወቅት በአረብ አገር ካሉት ስዎች ውስጥ 75% በላይ ኢንተርኔት ተጠቃሚ ናቸው። ስለዚህ እንደዚህ ዓይነት ብሎጎችን ማየታቸውና ማንበባቸው አይቀርም። ቢያንስ ቢያንስ አጠቃላይ ለውጥ ባይመጣ እንኳን መጠነኛ የሆነ ነገር ማየት እንችላለን ብዬ አምናለሁ።ይበል ያሰኛል።….›› ይህን የመሳሰሉ በርካታ አስተያየቶች ደርሰውኛል፡፡ ለአስተያየቶቻችሁ ምስጋናዬ የከበረ ነው፡፡

     የበለጠ ደግሞ አባቴ ወታደር እያለ የሰራትን ቤት ካርታ አሲዘው ስለሆነ የላኩኝ ቤታቸውንም እንደሚያጡ ሳስበው ሰቀጠጠኝ፡፡ ሞቴ ብዙ ነገራቸውን እንደሚያጨልመው በተቃራኒው ተስፋቸው፣ በልቶ ማደራቸው፣ መጠለያ ይዞ መቆየታቸው ሁሉ በእኔ ላይ የተጣለ ሀላፊነት እንደሆነ ሳውቅ ራሴን ጠላሁት፡፡.. ብዬ ነው በቀጠሮ ያቆየኋችሁ፡፡ ቀጠልኩ…ተከተሉኝ..

     ገመድ ብፈልግ ከየት ላግኝ? መርዝ ነገርም ፈለኩ፡፡ ግን ምንም አላገኘሁም፡፡ ወይ አለመታደል ለካ ራስን ማጥፋም ከባድ ነው አቃተኝ፡፡ እንደምንም እግሬን አንፈርክኬ ለመቆም ሞከርኩ፡፡ አቃተኝ እና ወደኩኝ፡፡ ስወድቅ ጓ!...የሚለውን ድምጽ ሰምተው ልጆቹ መጡ፡፡ ሲመታኝ አለመጎዳቴን አይተው የሚበላ ነገር አምጥተው እንደ ውሻ በሰሀን ወረወሩልኝ፡፡ እህሉን ሳየው ጠንከር ያለ ርሃብ ተሰማኝ፡፡ ሽንቴን ሸንቼ የተጨማለቀ ሰውነቴን ታጥቤ ለመብላት ግርግዳ ተደግፌ እየተራመድኩ መጸዳጃ ቤት ገባሁ፡፡ ሽንቴ የምጥ ያህል ሲያስቃትተኝ ቆይቶ ያደናገጠኝ ነገር ገጠመኝ፡፡ ስሸና ማቃጠሉ እና በደም መታጀቡ ብቻ ሳይሆን ከሰገራዬ ጋር ተቀላቅሎ መሆኑ ይበልጥ አደናገጠኝ፡፡ አሁን ራሴን የማጥፋቱ ፍላጎት ዳግም ውስጤ አቆጠቆጠ፡፡ ቁስለቱም ከውስጤ ይቆጠቁጠኝ ጅመሯል፡፡ በዚህ አይነት ሁኔታ እንደማያኖሩኝ ታሰበኝ፡፡ ይጠርዙኛል /ወደ ኢትዮጵያ ይመልሱኛል/ ችግራቸውን አብዝቼ እንዲህ ሆኜ አይተው ሰቀቀን ከምሆንባቸው ራሴን ማጥፋቱን መረጥኩ፡፡

    በእንደዚህ አይነት ሁኔታ መኖር አልፈቅድም፡፡ የፍራሹን ጨርቅ ባለ በሌለ ሀይሌ ቀድጄ ሸምቀቆ አድርጌ አሰርኩና የደረጃው መደገፊያ ብረት ላይ አሰርኩት፡፡ እንደ ምንም ራሴን ከተትኩት፡፡ ግን እንዴት ያስፈራል? ጣር ይዞኝ የማወጣውን ድምጽ ሰምተው ተሯሩጠው ገመዱን በጠሱት፡፡ ተዝለፍልፌ ወሜት ስወድቅ አንደኛው በእርግጫ ጠለዘኝ፡፡ ለሁለት አንጠልጥለው መኪና የኋላኛው እቃ መጫኛ ውስጥ ከተቱኝ፡፡  አንደኛው ምን ሊያመጣ እንደሆነ እንጃ ሮጦ ወደ ውስጥ ሲገባ በኮቴው ድምጽ ታወቀኝ፡፡ ከፈት አደረገና የሆነ ፌስታል አምጥቶ ላዬ ላይ ጣለው፡፡ ወዴት እንደወሰዱኝ ከተማውን ስለማላውቅ አላውቀውም፡፡ ከተማውን ባውቀውም ስለማይታየኝ አላውቀውም፡፡ የሆነ ዘዋራ ስፍራ ከመኪና አውርደው ሲጥሉኝ ፌስታሉንም አጠገቤ አስቀመጡልኝ፡፡ መኪናቸውን አስነስተው ሲሄዱ ያለሁበትን አካባቢ ዞር ዞር ብዬ ቃኘሁት፡፡ ቆሻሻ መጣያ ቦታ ነው፡፡ አንዲት ከርታታ እንጀራ ፍለጋ ከሀገሯ የተሰደደች ምስኪን ቆሻሻ ተብላ ቆሻሻ ቦታ ብትጣል ለእነሱ ምን ይደንቃል? ለእኔ ግን አስለቀሰኝ፡፡ በድህነቴ፣ በእድሌ አለቀስኩ፡፡ በፈጣሪዬ አዘንኩበትና አለቀስኩ፡፡ ለምን እንዲህ ሲያደርጉኝ ዝም አለ? ለምን ፈጠረኝ አልኩ፡፡ እኛ ለአረብ መጫወቻ ነው የተፈጠርነው ስል አለቀስኩ፡፡ አልቅሼ…አልቅሼ… አልወጣልሽ አለኝ፡፡

     እዛ ቦታ ምን ያህል ሰዓት እንደቆየሁ አላውቅም፡፡ በህመሙ፣ በለቅሶው ድካምና ህመም ስለነበረብኝ አሸለበኝ፡፡ አጠገቤ አንድ ሰው ቆሞ ያናግረኛል፡፡ የነቃሁት በዚህ ጊዜ ነው፡፡ የምችለውን ያህል ነገርኩት፡፡ በታክሲ ወስዶ ከሀበሻዎች ጋር አገናኘኝ፡፡ /ከተኙት ሁለት ሴቶች አንዷን አሳየችኝ፡፡ አፏን ገርበብ አድርጋው ያለ ሀሳብ ተኝታለች/ መጀመሪያ ካገናኘኝ ሁለት ልጆች አንዷ ናት፡፡ አዘኑልኝ አጥበውኝ የሚበላ ነገር አበሉኝ፡፡ ሳይጠየፉ ገላዬን አጠቡኝ፡፡ አይኗ ዳግም እንባ የማመንጨት ተግባሩን ቀጠለ፡፡ ሳግ ይተናነቃት ጀመር፡፡ ከተኛችበት ተነስታ ጫፉ ላይ ተቀምጣ ከነበረው አልጋ ላይም ሸርተት ብላ መሬት ሽርቁጥ ብላ ተቀመጠች፡፡ ግራ ገባኝ፡፡ አለመጠየፋቸው እንደሆነ ያስለቀሳት ገመትኩ፡፡ ሁኔታዋ ውስጤን ነካው እኔም የመን ውስጥ በእስር ሳሳልፍ አስታማሚ በሌለበት ታምሜ ለሽንት የሚያነሳኝ አጥቼ የተከሰተውን አስታውሼ እሷን በማባባል ፋንታ አጋዥ ሆንኩና ተገኘሁ፡፡ ሁለታችንም ባሳለፍነው መከራ ትዝታ ተሰንገን እንባዋን በእንባዬ አጀብኩት፡፡ አላቀስኳት ወይም አስለቀሰችኝ፡፡

    ‹‹..ገብቶሀል ግን ለምን እንደማለቅስ? ማንም ሰው ብሎ አያየኝም፡፡ ከእንግዲህ ተስፋ የለኝም ያልኩትን ሴት፣ ግማቱ ለራሴ ያስጠላኝን ሴት ሳይጠየፉ አጠቡኝ፡፡ እላዬ ላይ የደረቀ ቆሻሻዬን ላስቲክ ጓንት አድረገው አስለቀቁልኝ፡፡ የወቀስኩት ፈጣሪዬ ለካ አልረሳኝም፡፡ ለካ ወገንም ለወገኑ አይጨክንም አልኩ፡፡ አጣጥበውኝ ልብስ ሊለውጡልኝ ፈልገው ከእኔ ጋር አብረው የጣሉትን ፌስታል ሲከፍቱት ውስጡ ፓስፖርቴን አገኙት፡፡ ከገባሁበት ቪዛ ውጪ መኖሪያን አላሰሩልኝም፡፡ ልጆቹ ግን ያን ያደረጉት ይዛ ጠፋች እንዲባል መሆኑን አስጠጊዎቼ ነግሩኝ፡፡ ለምን ቆሻሻ መጣያው ጋር እንደጣሉኝ እና ምን እንዲህ እንዳደረገኝ ጠየቁኝ፡፡

    የደረሰብኝን ሁሉ እውነቱን ስነግራቸው አዝነው አይዞሽ እኛ አለን አሉኝ፡፡ በእርግጥም ብዙ ነገር ረዱኝ፡፡ ለሽንት መጸዳጃ በገባሁ ቁጥር አንደኛውን ለይቼ ማስተናገድ አቃተኝ፡፡ ሁሌ ተቅማጥ እንደ ያዘው ለአንደኛው ስቀመጥ ተቀላቅሎ ይወጣል፡፡ ህጋዊ ስላልሆንኩ በግልጽ ሆስፒታል ሄጄ መታከም ስለማልችል አንደኛዋ ልጅ የምታውቀው ዶ/ር ስለነበር ህክምና በድብቅ እንዲሰጠኝ አናገሩት፡፡ ትንሽ ካገገምኩ ከሳምንት በኋላ መረመረኝ፡፡ የፌስቱላ ችግር ስለተከሰተብኝ ህክምናው በቀላሉ ሊሰጥ እንደማይችል ነገራቸው፡፡ ለሰው ልጅ የተፈጠረውን መከራ ሁሉ ለብቻዬ ያሸከመኝ መሰለኝ፡፡ ከማልወጣው አረንቋ ውስጥ መዘፈቄን አስቤ ተስፋ ቆረጥኩ፡፡ መፍትሄው በድብቅ የግል ክሊኒክ ውስጥ ለጊዜው የሚሆን ከፍተኛ ህክምና መውሰድ እንዳለብኝ ተናገረ፡፡ ለዚህ የሚሆን ገንዘብ ደግሞ ማግኘት ከባድ ነበር፡፡ 4ወር ከ17 ቀን ብሰራም የሰጡኝ ገንዘብ ስለሌለ ምን ማድረግ ይቻላል? አልከስ ተጎጂዋ እኔ ነኝ፡፡ ባለቅስ አልወጣልሽ አለኝ፡፡

     የሚችሉትን ያህል እንደሚሞክሩ ካልሆነ ወደ ሀገር የምመለስበትን መንገድ እንደሚያመቻቹ ነገሩኝ፡፡ ከዛ በፊት ግን ለመታከሚያ የሚሆን ገንዘብ ለሰው ሁሉ እየነገሩ ቤተ ክርስቲያንም..በቻሉት ቦታ ሁሉ ለመኑልኝ፡፡ ዶ/ሩ ግን ገንዘቡን ብቻ በድብቅ ህክምናዬን ለሚከታተልበትም ሆነ በድብቁ ክሊኒክ ለሚደረገው ህክምና እንዲረዳኝ ብቅ ባለ ቁጥር ውለታ እንድውልለት ይጠይቀኝ ጀመር፡፡ ለስሜት ውጥረቱ..ሆጵ ላለ ገላው ማስከኛ አፌን ላበድረው ይፈልጋል፡፡ ያለኝ አማራጭ ፍቃደኛ ሆኖ መገኘት ብቻ ነው፡፡ አንድ ሊያሲዘኝ ይችላል፡፡ ሁለት ታክሜ ድኜ ለመስራት እፈልጋለሁ፡፡ ትለውጠናለች ብለው ያሲያዙትን የቤት ካርታም ለማስለቀቅ መዳን አለብኝ፡፡ ስለዚህ ይሄ ዶክተር ብቻ በመሆኑ ያለኝ አማራጭ እንቢ እንዳልለው ራሴ ለራሴ መከርኩት፡፡ ቀን እስኪያልፍ…ብዬ ጀመርኩት፡

      ከዚያ በኋላ ህክምናውንም እየተከታተልኩ ለእነሱ ሸክም መሆን ከበደኝ፡፡ ሁለት ወር ሙሉ ተሸከሙኝ፡፡ ከዛ በኋላ እነሱ ገላቸውን ሸጠው ቁጭ ብዬ መብላቱ ተናነቀኝ፡፡ ሰው ቤት ተቀጥሬ እየሰራሁ በየጊዜው ህክምናውን ማግኘት ከባድ መሆኑን ስረዳ እንም እነሱ የሰሩትን ለመስራት ሞከርኩ፡፡ ፈራ ተባ እያልኩ አንድ ቀን ከአንዱ ጋር ሄድኩ፡፡ ያልጠበኩት እና አሳፋሪ ድርጊት ፈጸምኩ፡፡ ወሲብ ሲፈጽም ሽንትና እንትኔ ከቁጥጥሬ ውጭ ሆኖ ፈሰሰ፡፡ አልጋውን አበላሸሁበት፡፡ ጠፍጥፎ አንሶላውን አሳጥቦ እንኳን ሊመልሰኝ ከጊቢው ብቻ አስወጥቶ ጣለኝ፡፡ ለጓደኞቼ ደወልኩላቸው፡፡ በታክሲ መጥተው ወሰዱኝ፡፡ አይዞሽ እያሉ አጽናኑኝ፡፡ ሌላ ጊዜ በአፍ ብቻ መፈጸም ለሚፈልግ አንድ ሰው መስራት ጀመርኩ፡፡ አንዴ ከገባህበት ደግሞ የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም ነው፡፡ሳንቲም ተርፎኝ ለቤተሰብ መላክ ጀመርኩ፡፡…..ደንበኞቼ በረከቱ፡፡ አፌ ተግባሩ በዛ መብያና መናገሪያ ብቻ ሳይሆን ተጨማሪ ስራ ተመደበለት፡፡ እንደማንኛውም ሰው ለሄዋን በተፈቀደው ቦታ ወሲብ መፈጸም አልችልም፡፡ ያን ካደረኩ ሽንትና ሰገራዬ ተቀላቅሎ…ይፈሳል፡፡  ይህ ሁኔታ በክሊኒክ ውስጥም በድብቅ ህክምና ቢደረግልኝም ሙሉ ለሙሉ አልቆመም፡፡ ድንገት አሁን ሀገሬ ስገባ የተሻለ ህክምና አገኛለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡     

    ታዲያ እንዲህ አይነት አስጠሊታ ህይወት እየኖርኩ አንተ አስጠሊታ ያልከውን ቃል ባወጣ ባላወጣ ምን ለውጥ አለው? እርግጥ ይህን በማድረጌ ታዝንብኛለህ? ይህን ባላደርግ የቤተሰቦቼን ካርታ አስለቅቅ ነበር፡፡ በልተው እንዲያድሩ አደርግ ነበር? እኔስ በምን አይነት…. አሁንም እንባ አቋረጣት፡፡ በመሀል በመሀል እንባዋን ባፈሰሰች ቁጥር እኔም አጃቢነቴን ሳላጓድል እዚህ ድረስ አወጋን፡፡
   ወደኋላ ተመልሼ ካለችኝ ላስታውስ ‹‹…ይሄ ባህላችን፣ ስርዓታችን.. ቅብርጥሴ ለምትሉት ነገር አስበህ ከሆነ ተወው፡፡ ባህል ስርዓት ቅብርጥሴ እያለ የሚጀነነው ማህበረሰብ አንገዋሎ ከተፋቸው ምስኪኖች ተወልጄ ነው ለዚህ ሁሉ መከራ የተዳረኩት፡፡ ታዲያ ወግ ስርዓት ለእኔ ምኔ ነው? ቁርስ አልሆነኝ ምሳ….›› ብላኝ ነበር፡፡ ይህ አባባሏ ለእኔ የተንጠፈጠፈ እውነት ነው፡፡ ልክ እንደ ኑግ ዘይት የጠራ…ምክንያቱም በርሃብ፣ በችግር ለተተበተበ ሰው ምኑ ነው? የሶስት ሺህ ዘመን ታሪክ አለን እያልን ሶስት ሺህ ዘመን ስናወራ ሳንሰራ ቀርተን ድህነት እጣፋንታችን ይመስል ተጎብሮብን እንደ ሸማ ለብሰነው፣ እንደኩታ አጣፍተነው አብሮን ከርሟል፡፡ ይህን ስል ታሪካችን ባህላችን አያስፈልግም እያልኩ አይደለም፡፡ ማዕረጋችንም ጌጣችንም ነው፡፡ ግን ማዕረግም ጌጥም የሚደምቀው ተርበው ተቸግረው አይደለም፡፡ ሲኖረን..ሰርተን ስንለወጥ ነው እንጂ በችግር ሰዓት ታሪክ፣ ባህል ወግ ስርዓት ችግር የሚቀርፍ ባውንድ አይደለም፡፡ አይሆንምም፡፡ የቸገረው፣ የራበው ሰው ያን መጠበቂያ ትዕግስትም አቅምም አይኖረውም፡፡ የዚህች ልጅን ትንፋሽም የተረዳሁት ከዚህ አንጻር ነው፡፡ እናንተስ ምን ትላላችሁ??? መስራቷ ልክ ናት? ወይስ መስራት አልነበረባትም? ምን ማድረግ ነበረባት?? 
             እንወያይበትና ወደ ቀጣይ እንሄዳልን
                 

ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በአረብ ሀገር
ክፍል ሁለት
የፌስቱላ ችግር የተከሰተብኝ በግፍ በተሰራብኝ…ነው
በግሩም ተ/ሀይማኖት

ወደንም ሳንወድም የምንሰራው ስራ ለሀገር ሊያኮራም ሊያሳፍርም ይችላል፡፡ ሊያኮራ የሚችለው የግድ ባንዲራ አውለብልበን አለያም በምርምር ግኝት አስመዝግበን ብቻ አይደለም፡፡ ስደት የወጡበትን አላማ አሳክቶ መመለስም ለቤተሰብ ማጉረስም አኩሪ ነው፡፡ ከሀገር፣ ከቤተሰብ፣ ከቀያችን አርቆ ያስወጣን አላማ ነውና ያኮራል፡፡ የሚያሳፍረው ደግሞ መጥፎ ቦታ ተሰልፈን ስንገኝ ነው፡፡ በአረብ ሀገር ያሉ ሴቶችም ሆኑ ወንዶች የሚሰሩበት ነገር ከዚህ የተለየ አይሆን፡፡ ያኮራል አለያም ያሳፍራል፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ ጥቂቶች ከደረሰባቸው መከራ ለመውጣት ያላቸው ብቸኛ አማራጭ ይሆንና እንደዋዛ መጥፎውን ድርጊት ይገቡበታል፡፡ ከ70% እና ከ80% በላይ የሚሆኑት ወደው እንዳልሆነ ለሽርሙጥናም ሆነ ለሌላ አስከፊ ስራ የሚዳረጉት ካነጋገርኳቸው ሰዎች ለማወቅ ችያለሁ፡፡ መጥፎ የሚባለው ህይወት ውስጥ እንዳይገቡ ማድረግ የሚቻለው እንዴት ነው? የሚለውን ማሰብ ግድ ይላል፡፡ ምላሹም ለስራ ሲሄዱ የሚፈጸምባቸው ግፍ እንዲቆም ማድረግ ብቸኛው አማራጭ ነው፡፡

ህይወት ጉዞዋ እኛ በፈቀድነው ብቻ ሳይሆን ባልፈቀድነውም ይሆንና ያላሰብነው አረንቋ ውስጥ ትዶለናለች፡፡ በአንድ ወቅት ዱባይ የመኖሪያ ፍቃድ የሌላቸውን ማፈስ ተጀመረ፡፡ ይህ ችግር ሲከሰት አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ስደተኛ መኖሪያ ፍቃድ አልነበረውም፡፡ ምክንያቱም በኮንትራት ስራ እየሄዱ በሚደርስባቸው ግፍ ተማረው ሲጠፉ ፓስፖርታቸው ቀጣሪዎቻቸው እጅ ስለሚቀር ነው፡፡ ታዲያ አፈሳው መኖሪያ ወረቀት ለሌለው ሱሪ በአንገት የማስወለቅ ያህል ምጥ አስምጧል፡፡ ከተያዙ የአይን አሻራ ይነሳሉ ወደ ሀገራቸው ይጠረዛሉ /ይላካሉ/፡፡ አይን አሻራ የመነሳቱ ነገር ደግሞ ዳግም ከስድስት አመት በፊት ወደ ዱባይ እንዳይገቡ ያስከለክላል፡፡ ስለዚህ ስደተኛው ያለው አማራጭ ሳይያዝ ሀገር ገብቶ በቪዛ ዳግም ወደ ዱባይ መግባት ነው፡፡ ሳይያዙ ወደ ኢትዮጵያ ለመግባት በየመን በኩል እንደጉድ ይጎርፉ ጀመሩ፡፡

ይሄ ደግሞ በህገ-ወጥ አጓጓዦች ነው የሚከወነው፡፡ ምክንያቱም ዱባይ ከየመን ጋር ድንበርተኛ ስላልሆነች ገና የኦማንን ድንበር ተጥሶ በጨለማ በጫካ ስለሆነ የሚጓዙት ነው፡፡ ላለመያዝ የነገ ህይወትን ችግር ውስጥ ላለመክተት ዛሬ መቸገር ግድ ሆነ፡፡ በዚህን ወቅት በየመንገዱ የተደፈሩ፣ የታሰሩ፣ የተዘረፉ እና የተለያየ አይነት ፈርጀ ብዙ ችግር ያስተናገዱ ሞልተዋል፡፡ በለስ ቀንቷቸው ምንም ሳይገጥማቸው የገቡም ብዙ ናቸው፡፡ በአፈሳው የተያዘ ሰው ከዱባይ ጋር ደህና ሁኝ ልበልሽ በእንባ እየታጠብኩኝ..ያባብለዋል፡፡ የአይን አሻራ ከተነሳ ዳግም ወደ ዱባይ መመለስ አይቻልምና፡፡ ከችግር እና ስራ አጥነት ጋር ሀገር ገብቶ ቤተሰብ ላይ መቀመጥም የማይታሰብ ነው..ስለዚህ የደረሰውን ግፍ ተቀብሎ የመን መግባት አማራጭ እና አማራጭ ብቻ ነው፡፡

በዛን ወቅት ወደ የመን የመጣችሁ ከህገ-ወጥ አጓጓዦቹ ጀምሮ በየመንገዱ እያንዳንዳችሁ የደረሰባችሁን መከራ ዛሬ ዱባይ ያላችሁ፣ ወደ ሌላ ሀገር የተዘዋወራችሁም ሆነ ኢትዮጵያ የገባችሁ ታስታውሱታላችሁ፡፡ በፖሊስ ተይዘው ሲደበደቡ የከረሙ ገንዘባቸውን የተነጠቁ ጥቂቶች የተደፈሩ ነበሩ፡፡ ጥቂቶቻችሁን ዛሬ ዳግም ፌስቡክ ስላገናኘን ምስክርነታችሁን ብታሰፍሩት ሌላው ቢማርበት ጥሩ ነበር፡፡ እዚህ የመን ውስጥ ጉዳያችሁን አስፈጽማለሁ ብለው አሳር መከራችሁን ያሳዩዋችሁ ብዙ አሉ፡፡ እዛ የምትሰሪውን እዚህ ስሪ ብለው አሳልፈው ለአረብ የሸጧችሁንም ታስታውሳላችሁ ብዬ አስባለሁ፡፡

አንድ ከእኔ ጋር የተያያዘ ክፍል ቤት የተከራየ ጥቂቶቻችሁን የማገት ያህል ለፖሊስ አሲዛችኋለሁ ብሎ እያስፈራራ ገንዘባቸሁን ነጥቆ፣ ሴትነታችሁን ጠልቆ የተጫወተበት አውቃለሁ፡፡ ወገኖቹን ያሰቃይ የነበረ በፊት የመን የኖረ ከዱባይ ከመጣ አረመኔ ጋር ተጠማምጄ ነበር፡፡ ጉዳይ አስፈጽማለሁ ብለው የወገናቸውን ደም ከሚመጡት አንዱ ይህ ሰው ሲሆን ጎረቤቴ በመሆኑ ሁሉን ለማየት ታድያለሁ፡፡ በአንዴ አርባ እና ሀምሳ ሰው እያመጣ የሁላችንም ቤት አቅሙ እስከፈቀደ አስተናግዷችኋል፡፡ በዛውም መረጃዬን ስብስቤያለሁ፡፡ ከስባት ልጆች ጋርም ቃለ-ምልልስ አድርጌያለሁ፡፡ ለዛሬ የአንዷን ላቅርብላችሁ፡፡

ደስ የሚል ቁመና ያላት ‹‹..ቁመትሽ ሎጋ ነው የእኔ አለም..›› የምታሰኝ ጠይም ናት፡፡ የደስ ደስ ያላት፡፡ ከጊዜያዊ ምቾት ውጭ ድህነት ሽንቁጥ አድርጎ እንዳሳደጋት ያስታውቃል፡፡ ይህ ደግሞ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ 95 ከመቶ የቀመሰው ጽዋ ነው፡፡ ከዱባይ በኦማን አድርጎ ያመጣቸው ሰው 16.000 ድርሀም ዘርፏታል፡፡ ሁሉም ሲሰሙ ደነገጡ፡፡ በኢትዮጵያ ወደ 35000 አካባቢ መሰለኝ በዛን ወቅት ምንዛሪ፡፡ እሷ ግን ምንም ሳይመስላት ‹‹ተዉት ተመልሼ ስሄድ በአንድ ሳምንት ጠባ..ጠባ ባደርግ የማገኘው ነው…›› አለች፡፡ ጠላታችሁ ድንግጥ ይበል አመዴ ቦነነ፡፡ ከየትኛው ዩነቨርስቲ የብልግና /መረንነት/ ዲግሪዋን እንደወሰደች እያሰላሰልኩ ብቻዋን የማናግርበትን ሁኔታ አቀድኩ፡፡

በዛ ያሉት ሺሻ ላይ አፋችሁን ለጉሙ የተባሉ ይመስል ተያይዘውታል፡፡ እርግጠኛ ነኝ የእናታቸውን ጡት እንኳን እንዲህ አልመጠጡም፡፡ ከጡጦ ቀጥሎ ሺሻ የጀመሩ ያስመስልባቸዋል፡፡ ዱባይ እንደ የመን ጫት ስለማይገኝ እንደ ጫት ሻይ ቅጠሉን ከካሮት ወይም ከመቅዶኒስ ቅጠል ጋር ጉንጫቸው ውስጥ ወጥቀው ተክዚና መያዝ ለምደዋል፡፡ የመን ጫቱ ስላለ ወጥቀውታል፡፡ ሁለቱ ልጆች ግን የለመዱትን ስላረጉ ነው እዛ የሚጠቀሙትን ያወኩት፡፡ ምስጢር ካወጣሁ ይቅርታ!!

ወደ ግማሽ የሚሆኑት ከምኑም ያልሆኑ የእህል እና ውሀ ሱስ ብቻ ያለባቸው አሉ፡፡ አጨዋወታቸው ደርዝ ያለው በእርጋታ የተሞሉም ናቸው፡፡ ከላይ የጠቀስኳት ልጅ ስልኳ እረፍት የለውም፡፡ እሷም ትደውላለች፡፡ ጎበዝ ደዋይ ነች፡፡ ያጠናሁት ነገሯ አንዱ ጋር ትደውልና ‹‹ያ-ባባ መንገድ ላይ እኮ ተዘረፍኩ፡፡ አንተ ነሀ እዛ ከደረስኩ በኋላ ላክልኝ ስልህ…›› ይሄ እኮ ያ ባለ ሆቴሉ ነው ትላቸዋለች አብረዋት ላሉት፡፡ ትንሽ ቆይታ ትቀጥላለች ‹‹..ወላ! ወላ! አሁን ካርድ መግዣ የሚሆን ሳንቲም እንኳን የለኝም፡፡ ዛሬውኑ ላክልኝ…›› ስልኩ ይዘጋል፡፡ ልጁ ገንዘብ እንደተላከላት ካወቀ እንደሚነጥቃት በእኔ መታወቂያ ላወጣላት በስሜ ከሁለት ሰው ተልኮላታል፡፡ የሚገርመው ግን አንዴ ካወጣሁት ላይ ሁለት ሺህ ድርሃሙን የሱዳኒ ባልዋን ስም ነግራኝ ላክለት ብላኛለች፡፡ ልኬያለሁም፡፡

አጋጣሚዎች ተገጣጠሙ እና ያስመጣቸው ጨካኝ ሰክሮ ከሚስቱ ሲጣላ ሸሽተው ሶስት ሆነው እኔ ቤት አደሩ፡፡ መኝታዬን ለቅቄላቸው አረቢያን መጅሊስ ላይ ጋደም ብዬ ከሁሉም ለየት ብላ ካየኋት ልጅ ጋር ያሰብኩትን ማውራት ቀጠልን፡፡ ሁለቱ ሸለብ አድርጓቸዋል፡፡ ሞባይል ስልኬ ሪከርድ የሚለው ላይ ሆኖ ተቀመጠ፡፡ ለምንድን ያንን መረን ቃል እንደተጠቀመች፣ ድርጊቱን ብታደርገው እንኳን እንደ ጀብድ በዛ ሁሉ ሰው መሀል ማውራቷ አግባብ እንዳልሆነ ነገርኳት፡፡ ሌሎቹንም ወደዛ ተግባር መምራት ነው፡፡ ፊቷ ልውጥውጥ አለ፡፡ አፈጠጠችብኝ፡፡ ሶስት አራት የተሻሻሉ የብልግና ስድቦችን ልትለጥፍልኝ ነው ስል አሰብኩ፡፡ ‹‹እኔነኝ ወደ ብልግና የምመራቸው? ራሱ መከራው ስቃዩ መሮጫ ማምለጫ ማጣቱ ነገሮች ሳይወዱ ወደዛ ይመሩዋቸዋል፡፡ ማንም መሸርሞጥ ፈልጎ አይሸረሙጥም…›› እንባዋ ተንደርድሮ የትራስ ልብሴን አጠመቀው፡፡ ላባብላት አልሞከርኩም፡፡ ስደት ላይ እያሉ እንባ ማፍሰስ እጣቢ ውሀ የመድፋት ያህል ቀላል መሆኑን አውቃለሁ፡፡ እስኪበቃኝ ቀምሼዋለሁም፡፡

ጋደም ካለችበት ቀና ብላ በአትኩሮት ስታየኝ ቁስል ኖሯት እንደነካኋት ታወቀኝ እና ተጸጸትኩ፡፡ ቢሆንም ቁስሏንም፣ ያቆሰላትን ታሪክም ለማወቅ ጓጓሁ፡፡ በአንዴ ቅላትን ባሰተናገደ ድፍርስ አይኗ ገልመጥ አድርጋኝ ‹‹ምን ማወቅ ፈለግህ? ለምንስ?..›› አስተያየቷ ያስፈራል፡፡ ቢሆንም ከጀመርኩ ወደኋላ የለም እና ወደፊት በሉለት ይለይለት የሚለውን እያቀነቀንኩ ቀጠልኩ፡፡ አስረዳኋት፡፡ ከነገርኩህ ትጠየፈኛለህ፤ እንደ ሰው አታየኝም….በፍፁም ወደሽ የምታመጪው ነገር እንደሌለ አውቃለሁ አልኳት፡፡ በእርግጥም አንባቢዎቼ የፈለገ ጸያፍ ድርጊት ላይ ተሰልፈው ስታገኟቸው ወደው እንዳላደረጉት አስቡ፡፡ አይኖቿ እንባ ጨርሰው እስኪደርቁ እያለቀሰች አወጋችኝ፡፡ እግዚአብሄር ይመስገን አገዝኳት፡፡ የእኔም እንባ እጢዎች ስራ አልፈቱም፡፡ እንዲያውም ኦቨርታይም ሁሉ ሳይሰሩ አልቀሩም፡፡ እዚህ ጋር አንዳንድ ጸያፍ ቃላትን በራሴ ያጻጻፍ ስለቀየርኳቸው……

‹‹ጠባ..ጠባ..› ስላልኩ ነው የገረመህ? ረጀም ታሪክ አለው፡፡ ግን ድርጊቱን እየፈጸምኩ ጠራሁት አልጠራሁት ምን ለውጥ አለው? ይሄ ባህላችን፣ ስርዓታችን.. ቅብርጥሴ ለምትሉት ነገር አስበህ ከሆነ ተወው፡፡ ባህል ስርዓት ቅብርጥሴ እያለ የሚጀነነው ማህበረሰብ አንገዋሎ ከተፋቸው ምስኪኖች ተወልጄ ነው ለዚህ ሁሉ መከራ የተዳረኩት፡፡ ታዲያ ወግ ስርዓት ለእኔ ምኔ ነው? ቁርስ አልሆነኝ ምሳ…የተንጠፈጠፈ እውነት ነው፡፡ ልክ እንደ ኑግ ዘይት የጠራ…ምክንያቱም በርሃብ፣ በችግር ለተተበተበ ሰው ምኑ ነው? የሶስት ሺህ ዘመን ታሪክ አለን እያልን ሶስት ሺህ ዘመን ስናወራ ሳንሰራ ቀርተን ድህነት እጣፋንታችን ይመስል ተጎብሮብን እንደ ሸማ ለብሰነው፣ እንደኩታ አጣፍተነው አብሮን ከርሟል፡፡ ይህን ስል ታሪካችን ባህላችን አያስፈልግም እያልኩ አይደለም፡፡ ማዕረጋችንም ጌጣችንም ነው፡፡ ግን ማዕረግም ጌጥም የሚሆነው ሲኖረን..ሰርተን ስንለወጥ ነው እንጂ በችግር ሰዓት ችግር የሚቀርፍ ባውንድ አይደለም፡፡ አይሆንምም፡፡ የቸገረው፣ የራበው ሰው ያን መጠበቂያ ትዕግስትም አቅምም አይኖረውም፡፡ የዚህች ልጅን ትንፋሽም የተረዳሁት ከዚህ አንጻር ነው፡፡

ቀጠለች እኔም የእሷን ታሪክ ቀጠልኩ…..ለኮንትራት የቤት ሰራተኝነት ነው ዱባይ የሄድኩት፡፡ ሴትዮዋ በስራ የምትሳቃየኝ አንሶ ለወሲባዊ ስሜቷ አሳሬን ታሳየኛለች፡፡ ስራዬን አስትታ ሻዎር እንግባ ትለኛለች፤ መኝታ ቤት አስገብታኝ በር ትዘጋለች፡፡ ምን ልታደርጉ የሚል እንዳይኖር መቼም ለጸሎት እንደማይሆን ይገባችኋል፡፡ ሰውየው በሌላ በኩል ፍዳዬን አበላው፡፡ ሌሊት ይመጣና ሴንጢ ደቅኖብኝ ‹‹..አርጄ ቆሻሻ ውስጥ እጥልሻለሁ..›› ብሎ ብልቱን አፌ ላይ ይደቅናል፡፡ ያለቻቸውን አንድ ጥሪት የቤት ካርታ አሲዘው ብር ተበድረው ሲልኩኝ ታሳልፍልኛለች ብለው ነው፡፡ የላኩኝ ቤተሰቦቼ ነገር ትዝ ይለኛል ብድራቸውን እንኳን ሳይከፍሉ ባለ እዳ አድረጌያቸው ቤታቸውን አስወርሼ ጎዳና ተዳዳሪ አድርጌያቸው ልሞት? እልና የፈቀደውን ያደርጋል፡፡ ማዳሟ በልምምጥም ገንዘብ በመስጠትም የተጣባትን መጥፎ አባዜ ትወጣለች፡፡ በአንድ ወቅት ለሳምንት ወደ አቡዳቢ ሊዝናኑ ሲሄዱ እሱም ለራሱ ሲል እሷም ለራሷ ስትል አብሬያቸው እንድሄድ ፈለጉ፡፡ ልጆቹ ደግሞ ለእኛ ማን አለን ሲሉ ቅሪ ተባልኩ፡፡ እግራቸው ወጣ እንዳለ እሱም በበኩሉ ያስቸግረኝ የነበረው ትልቁ ልጅ ሰባት ጓደኞቹን ለእራት ስለጠራ ምግብ እንዳዘጋጅ ነገረኝ፡፡ የቻልኩትን ሰራሁ፡፡

ልጆቹ ማታ ላይ ተሰባበሰቡ፡፡ በሉ ጠጡ ሙዚቃ ከፍተው ይጨፍሩ ጀመር፡፡ አንዴ እንዲህ አድርጊ ሌላ ጊዜ ደግሞ እንዲህ አድርጊ ሲሉኝ ስደክም አመሸሁ፡፡ እስካሁንም ያልገባኝ ነገር ያጨሳሉ፡፡ ሀሺሽ አልመሰለኝም፡፡ በኋላ ሲጠሩኝ ስሄድ መሀል አስገብተው ይጎነታትሉኝ ጀመር፡፡ እንደ ሻንጉሊት አረደጉኝ፡፡ አንደኛው ከኪሱ የሆነ ብልቃጥ አውጥቶ መሀረብ ላይ ሲያፈስ አየሁት፡፡ ሁለቱ እጄን ግጥም አድርገው ሲይዙኝ አፌ እና አፍንጫዬ ላይ አድርጎ አፈነኝ፡፡ ከዚህ በኋላ ምን እንደተፈጠረ አላውቅም፡፡ ከስንት ቀን በኋላ እንደነቃሁ እግዚአብሄር ይወቅ፡፡ ስነቃ የተኛሁበት ቦታ በደም፣ በሽንት እና የቀጠነ ሰገራ ተጨማልቋል፡፡ ሽቴንም ምኔንም እዛው እየለቀኩ ነበር ማለት ነው፡፡ ሰውነቴ ላይ ሁሉ ደርቋል፡፡ ሽታው ለራሴ አስጠላኝ፡፡ ለመነሳት አልቻልኩም፡፡ ጭኔ መሀል ያለው ቁስለት በዋዛ የሚያንቀሳቅሰኝ አልመሰለኝም፡፡ ያለሁበትን ቦታ ማወቅ አልቻልኩም፡፡ በጣም የቆሸሸ፣ አቧራ የጠገበ እና በአሮጌ እቃዎች የተሞላ ነው፡፡ ግራውንድ መሰለኝ፡፡ አደጋው እስከ ተፈጸመብኝ ሰዓት ድረስ አራት ወር ከአስራ ሰባት ቀኔ ነው፡፡ ቤቱ ግራውንድ እንዳለው አላውቅም፡፡

ሁለቱም እግሬ ስላልታዘዘልኝ እየተንፏቀኩ ደረጃውን እንደምንም ወጣሁት፡፡ ሁለቱ የሴትዮዋ ልጆች ሲያዩኝ እንደመዝናኛ ፊልም በእንፉቅቄ ይስቁብኝ ጀመር፡፡ አለቀስኩ በጣሙን አምርሬ አለቀስኩ፡፡ አይዞሽ ባይ በሌለበት ለእነሱ ለቅሶዬ ደስታ ፈጥሮባቸው ሲንከተከቱ እኔን ግን እንባዬ አጠበኝ፡፡ ሽንት ቤት መግባት ፈለኩ እና እንደምንም ገባሁ፡፡ ሽንቴ እና እንትኔ እኩል ተቀላቅሎ ወረደ፡፡ ቸግር እንደተፈጠረብኝ ተረዳሁ፡፡ ራሴን ማጥፋት ፈለኩ፡፡ ተመልሼም ወደ ነበርኩበት ግራውንድ ወረድኩ፡፡ መታነቅ ነው ፍላጎቴ….በሀሳቤ እናቴ ታየችኝ፡፡ አባቴ በዘበኝነት የሚያገኛትን ገቢ የሚጠብቁ ታናናሾቼ ታዩኝ፡፡ የበለጠ ደግሞ ወታደር እያለ የሰራትን ቤት ካርታ አሲዘው ስለሆነ የላኩኝ ቤታቸውንም እንደሚያጡ ሳስበው ሰቀጠጠኝ፡፡ ሞቴ ብዙ ነገራቸውን እንደሚያጨልመው በተቃራኒው ተስፋቸው፣ በልቶ ማደራቸው፣ መጠለያ ይዞ መቆየታቸው ሁሉ በእኔ ላይ የተጣለ ሀላፊነት እንደሆነ ሳውቅ ራሴን ጠላሁት፡፡

ቀጣዩን ይዤ ብቅ ልል ቃል እገባለሁ፡፡ በጣም ስለረዘመብኝ መቁረጥ ግድ ብሎኝ ነው እና በስሱ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡


ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በአረብ ሀገር
ክፍል ሁለት
በግሩም ተ/ሀይማኖት

በዚህ ርዕስ የመጀመሪያውን ፅሁፍ እንደለቀኩ ኢ-ሜሌም ሆነ ስልኬ የግል መልዕክቶች በመቀበል ተወጠሩ፡፡ ከ142 በላይ ሰዎች ቻት ያደርጉኝ ነበር፡፡ የሚገርመው ግን አብዛኛዎቹ ያስተላለፍኩትን መልዕክት በትክክል ካለመረዳት የመነጨ ጭንቀት ነበር ያማከሩኝ፣ የወቀሱኝ፡፡ ካስተላለፍኩት መልዕክት ባፈነገጠ መልኩ የተረዱኝ የተረጎሙብኝ አሉ፡፡ ከዛም ተነስተው የሰደቡኝ ሞልተዋል፡፡ ስድብ ለብስልት መገለጫ አይሆንም፡፡ እውነታ የያዘ ሰው ይሄ ይሄ ነው እውነታው ቢለኝ የማልቀበልበት መንገድ የለም፡፡ አስተውላችሁ በማንበብ ወገን ላይ እየደረሰ ያለውን አሰቃ
ቂ ግፍ፣ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የሚሰሩ ስህተቶችን ብንነጋገር እና መፍትሄ ካገኘንም፣ መርዳት የምንችለውን ብንረዳ ቀና ወገናዊነት ነው፡፡

‹‹..ሴቶቹ በሴትኛ አዳሪነት ተሰልፈው አሰደቡን፣ አዋረዱን የምንለውን ያህል ወንዶችም በዚሁ መስክ ተሰማርተው መገኘታቸው ያሳፈራል፡፡ ኩሉን ተኩሎ ሊፒስቲክ ተቀብቶ ታይት አድረጎ ለገበያ የሚቆም፣ ተደውሎለት ፒክ የሚደረግ ኢትዮጵያዊ አለ መባሉ ምን አይነት ስሜት ይጭርባችኋል? ዱባይ ካሉ ኢትዮጵያዊያኖች ጋር በዚህ ዙሪያም አውርቻለሁ፡፡ እመለስበታለሁ፡፡ …›› ነው ያልኩት፡፡ ይሄ ማለት ዱባይ ያሉ ሴቶች በሙሉ ይሸረሙጣሉ ማለት ነው? በየትኛው ስሌት እና አባባል እንደተተረጎመ ዲክሽነሪ ላይ ቢፈለግ አይገኝም፡፡

ስለ ወንዶቹ ድርጊት ተወያይቻለሁ ነው ያልኩት፡፡ ቢሆን እንኳን ዱባይ ያሉ ጥቂት ሴቶቻችን የሚሰሩት ነገር የለም? ወገኖቻችን ላይስ ግፍ አልተፈጸመም? በቅርቡ ተጫውተውባት ዛፍ ላይ አንጠልጥለው ራሷን ሰቀለች የተባለች የለችም? በደረሰባቸው ግፍ አብደው ኮሚኒቲ ውስጥ የነበሩ የሉም? አሁንስ አይኖሩ ይሆን? ለሶስት ተጫውተውባት የፌስቱላ ችግር ገጥሟት አዋጡላት ተብሎ የታከመች የለችም? በስም ብቻ ሳይሆን በፎቶ ጭምር የማውቃቸው ወንዲኛ አዳሪዎች የሉም? /ለሴቶች ሴተኛ አዳሪ ከተባለ ለወንዶች ወንዲኛ አዳሪ የሚለውን ልጠቀም እንጂ እስከዛሬ ስላልተለመደ ቃል ያለው አልመሰለኝም፡፡/ ጥቂት በጣም ጥቂት እህቶቻችን ለሚያገኟት ሳንቲም ብለው በቪዲዬ ተቀርጸው መጠቀሚያ አልሆኑም?

እንዲያውም እዚህ ጋር አንድ ገጠመኜን ላሰፍር ወደድኩ፡፡ አንድ ፈረንሳያዊ ተጓዥ ጋዜጠኛ ነው፡፡ በአንድ ወቅት የመን የጋዜጠኞች ማህበር ስብሰባ ላይ እንድገኝ ተጋበዝኩና ስሄድ አገኘሁት፡፡ እሱም ተጋብዞ ስለነበር ሁለታችንም የተጋባዥ ወንበር ላይ ነው ያለነው፡፡ ከየት እንደመጣሁ የጠቀኝ እና ወሬ ተጀመረ፡፡ በወሬያችን መካከል እዚሁ እንደምኖር ተነፈስኩ፡፡ የመን ትንሽ ጊዜ ስለሚቆይ አብራው የምትዝናና ሀበሻ ሴት እንዳስተዋውቀው ጠየቀኝ፡፡ አንደኛ እኔ አቃጣሪ ደላላ አለመሆኔን ሁለተኛ ማንኛዋም ሀበሻ የእንደዛ አይነት ፍላጎት እንደሌላት እና ለስራ እንደመጣች ነገርኩት፡፡ የዛሬ ወር ዱባይ ነበርኩ ብሎ የያዛትን ዲጂታል ካሜራ ከነካካ በኋላ ፊልሙን ዝግጁ አድርጎ እንዳየው አቀበለኝ፡፡ አፍ እና ጭን ተጋጥመው /.../ በስሜት ጥድፊያ ይዋከባሉ፡፡ ፊልሙን ለማየት እንዳቀረቀርኩ ደረኩ፡፡ አንገቴን ቀና እንዳላደርግ ሀፍረት በግሩፕ ሰፍሮብኝ ሸብቦ ያዘኝ፡፡

ካሜራውን ስመልስለት መቅረጽህን ታውቃለች? ለነገሩ ይህቺ ልጅ ሀበሻ አይደለችም አልኩት፡፡ ለማምለጫ እንጂ ልጅቷን ኢትዮ ስፖት ዌብ ሳይት ላይ ተደጋጋሚ እርቃን ገላ በሚያጋልጥ ሁኔታ ፎቶ ተነስታ ስትለቅ ነው የማውቃት፡፡ በደንብ እንደምታውቅ እና ክፍያውን ጨምሮ እንዳደረገው ነገረኝ፡፡ የፈለገውን ያህል ቢከፍላት ከ1000 ዶላር በላይ አይከፍላትም፡፡ እሱ ግን የሚያፍሰውን ያፍሳል፡፡ እህቶቻችን ባለማወቅ ከወሲብ ውጭ ሌላም ንግድ መጠቀሚያ እየሆኑ ነው፡፡ እዚህ የመን ውስጥ አሁን ሳዑዲ ያሉ ሁለት እህትማማቾች አውቅ ነበር፡፡ ትልቅየዋ ጀርመናው ጓደኛ አላት፡፡ ከእሱ ጋር የምታደርገውን ነገር በህገ-ወጥ ሁኔታ ስትፈጽም ታናሽዬው ቪዲዮ ካሜራ ይዛ መቅረጽዋን ከራሷ አንደበት ሰምቻለሁ፡፡ እንደጀብዱ በተሰበሰብንበት ያወሩልን 500 ዶላር ሰጥቷቸው ነበር፡፡ እነዚህ አይነት ነገሮች በመጀመሪያ የራስን ሰብዓዊ ክብር፣ ሞራል ከማዝቀጥ አንጻር ቀጥሎ የወገንን ብሎም የሀገርን ስም....እያልን እንድናስብ ነው የሚያስፈልገው፡፡ እንዳሰው ችግራችንን እንነጋገር ነው አላማዬ፡፡ ባለማወቅም የሚሰራ ነገር መኖሩንም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

ሌላው በሞባይል ስልኬ ከደረሰኝ መልዕክት ውስጥ ስሟን ካስተዋወቀችኝ በኋላ ‹‹....እግዚአብሄር ይመስገን አለኝ፡፡ /አይ እታለም ቢኖርሽ ለምን ተሰደድሽ?/ ለራሴ እና ለቤተሰቦቼ እንጂ ጎረምሳ ልቀልብ አልወጣሁም፡፡/ቱ..ቱ..ቱ.. ያሳድግሽ፡፡ እኔም እኮ እያልኩ ያለሁት ለራሳችን ምን ያህል አውቀናል? ቤተሰብ በችግር ሲማቅቅ እኛ ለምን ስራ ጠልቶ እንደ ውሻ እጅ እጅ የሚያይ ሰው እንቀልባለን ነው፡፡/ እና አረብ ሀገር ያሉ በተለይ ዱባይ አያልክ ሰውን ባታጎሳቁል ደስ ይለኛል፡፡ ሌሎችን ወክዬ መናገሬ ግን አይደለም፡፡ ያለከውን የሚሰሩ አሉ፡፡ የሉም አልልም፡፡ እናንተ ጋርም እንዳሉ እህቶቼ ይነግሩኛል፡፡ እዚህ ዱባይ የብዙ ሴቶችን ትዳር እና ጓደኝነት እንደምትበጠብጥ ልብ ያልክ አልመሰለኝም፡፡..›› ይላል፡፡ ልብ እንዲባልልኝ የምፈልገው በተለይ ዱባይ ያልኩበት ቦታ የት ነው? እኔ ያልኩት ‹‹..ጥቂቶች ደግሞ በሉብናን /ቤይሩት/፣ ዱባይ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ባህሬን.. ኩዌት ያሉ ሴቶቻችን የሱዳን ወንዶች ሲሻሙ እና የለፉበትን አባክነው ቤት ተከራይተውላቸው ማስቀመጣቸው…›› ነው፡፡ ያውም ጥቂቶች እንጂ ሁሉም አላልኩም፡፡ እህቴ ቅድሚያ አስተውሎ ማንበብ ቢቀድምስ?

‹‹ዱባይ የማውቃቸው በርካታዎች ሞልተዋል፡፡ እህቴም /የአጎቴ ልጅ/ ጭምር አለች፡፡ በጅምላ የሰውን ሰብዓዊ ክብር የሚደፈጥጥ ነገር አልሰራም፤ አልናገርምም፡፡ ሞያዬም አይፈቅድም፡፡ የማንንም ህይወት መንካትም ሆነ ማጨለም ህልሜ አይደለም፡፡ የእኔ አላማ በአቅም ማጣት ካልተገደበ በስተቀር ችግር ለመቅረፍ ነው፡፡ ችግሩን መነጋገር እና መፍትሄ ለሚያስፈልገው ከእነ መፍትሄው ብንነጋገር የሚደርሰው ጉዳት የሚቀንስበት፣ ብሎም የሚቆምበትን መንገድ ለመፈለግ ነው ዋናው አላማዬ፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣው ፍልሰት በምን ዘዴ ይቁም ሳይሆን ይቀንስ? የሚለውን መነጋገር ስላለብን ነው የምጽፈው፡፡ በተጨማሪም ለብዙ ነገር አጋልጦ የሰጠን መጥፎ ተግባራችን ቢቻል ቢቀር ካልሆነም ቢቀንስ ያለው መሰደብ፣ መንቋሸሽ፣ መናቁ ይቀንሳል፡፡ መሰደዳችን በድህነት መሰደባችን አንሶ በመጥፎ ነገር ሀገርም ማሰደባችን ቢቀርስ ከሚል ነው፡፡ በአረቡ አለም ላይ ለሀበሻ ያላቸው አመለካከት ጥሩ አለመሆኑን ሁላችንም የምናውቀው እውነታ ሆኖ ሳለ በመጥፎ ስራችን አጠቃላይ ያ-ሀበሺያ፣ ሀበሻ ጋህባ../ሀበሾች ሸርሙጦች፣ ሀበሻ ሸርሙጣ/ የሚል የጅምላ ስድብ አትርፈናል፡፡ ይህን ስም መፋቅ ቢከብድ ቢያንስ እንዲቀንስ ማድረግ ብንችል ከሚል ሀሳብ ተነስቼ ነው ያሰብኩት፡፡

አይነቱ ይለያይ እንጂ ያሰደደን ችግራችን ነው፡፡ተሰደን በሰራንበት ቤተሰብ ለውጠናል ወይ? ለራሳችንስ ሆነናል? አዎ አብዛኞች የሰሩትን ሰርተው ለቤተሰባቸው እና ለራሳቸው የጠቀሙበት ሁኔታ አለ፡፡ ሌሎች ደግሞ ቤተሰብ የሚበላው አጥቶ ሲራብ አሸሸ ገዳሜን በረጅሙ ሲቀውጡት ከርመው ያለምንም ሳንቲም ታመው በአዋጡልኝ ሀገር የሚገቡ አሉ፡፡ ያልረዱት፣ የረሱት ቤተሰብ ላይ ሄደው ሸክም የሚሆኑ፡፡ ይሄ ምኑ ነው ውሸት?

በዋነኛነት ግን ከላይ የጠቃቀስኳቸው እንዳሉ ሆነው በመታሰር፣ በመደብደብ፣ ኢ-ሰብአዊ ድርጊት እየተፈጸመባቸው በየቦታው አካላቸው እየጎደለ እና እየተገደሉ ስላሉ ወገኖቻችን ድምጽ እናሰማ፡፡ ለመፍትሄ የሚሆን ሀሳብ እንወያይ....ችግራችን ነው እንነጋገርበት ያልኩት፡፡ አስተውሎ መራመድ ብልህነት ነው፡፡ የወገን ሰቆቃ መቆሚያ ጊዜው እስኪደርስ የሚቀንስበትን መንገድ እንፈልግ፡፡

ዋናውን ታሪክ አልጀመርኩም በዋናው ታሪክ እንገናኛለን
ቸር እንሰንብት

ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በአረብ ሀገር
ክፍል አንድ
በግሩም ተ/ሀይማኖት
ሴቶቻችን ለሱዳን ወንዶች ይታገላሉ….

ኢትዮጵያዊያን እንደ ጉድ እየጎረፉበት ስላለው የአረብ ሀገር ስደት እና እየተፈጸመባቸው ስላለው ግፍ ሁሌም አስባለሁ፡፡ እጨነቃለሁም፡፡ ግን ምንም ማድረግ የምችል አይነት አይደለሁም፡፡ አቅም የሌለኝ ልክ ክንፍ እንደሌላት ወፍ የምፍጨረጨር እኔም አረብ ሀገር ገብቼ ገፈቱን፣ የሚደርሰውን አሰቃቂ ግፍ እያየሁ፣ እየቀመስኩም ያለሁ ስደተኛ ነኝ፡፡ ቢሆንም ወገናችን ላይ እየደረሰ ያለውን በደል ለወገኔ አድርሼ የሚረዳ እንዲረዳቸው ከማድረግ በተጨማሪ የሚሰደደውን ቁጥር በአምስትና አስር ሰው ቁጥር እንኳን ብቀንስ ብዬ እጫጭራለሁ፡፡

በዚህ ዙሪያ ሁለት መጽሀፍትን ባዘጋጅም የማሳተም አቅሜን እስካደራጅ እና አቅሜ ፈቅዶ አስካሳትም የስደተኛው ቁጥር በእጥፍ እየጨመረ መጣ፡፡ የሚደርስባቸውም ግፍ አሰቃቂነት አሳሳቢ እየሆነ፣ ሞት በየቦታው እየጠረጋቸው፣ የአካል መጉደል፣ መደፈር..የመሳሰሉት በእጥፍ እያደገ በመሆኑ ጊዜ ላለመስጠት በኢንተርኔት ጽሁፎቼን መልቀቁን አማራጭ አድረጌዋለሁ፡፡ እባካችሁ የሰማችሁ፣ ያነበባችሁ ለሌላው አሰሙ..አስነብቡ አንድም ቢሆን ወገን ይትረፍ፡፡ አረብ ሀገር ሆናችሁ የምታነቡም ለጥንቃቄም ሆነ ከአላማችሁ እንዳትዘናጉ ይሁናችሁ፡፡

በስደት ካሉ በጣም ከተለያዩ ሰዎች ጋር በደብዳቤ፣ በኢሜል፣ በስካይፒም የተለያየ ሀሳብ አካፍሉኝ እላለሁ፡፡ በርካቶች የማቀርብላቸውን ጥያቄ አቅም በፈቀደ ይመልሱልኛል፡፡ ከብዙዎቹ የምሰማው ግን አንገት የሚያስደፋ ነው፡፡ ሀገር እያለን እንደሌለን ሆነን የሚፈጸምብንን ኢ-ሰብአዊ ድርጊት ችለን ያለንበት ህይወት ሰቅጣጭ ነው፡፡ ታንቀው የሚገደሉ፣ የሚደፈሩ ሴቶቻችን፣ ወንዶች እና ህጻናት ቁጥር የዋዛ አይደለም፡፡ ታንቀው፣ ተደብድበው፣ በእሳት ተቃጥለው፣ የሞቱ ወገኖቻችን በየአትክልቱ ስፍራ ተቀብረው በየቆሻሻ መጣያው ተጥለው ቀርተዋል፡፡ ቀባሪ አጥተው በየሆስፒታሉ ፍሪጅ ውስጥ በስብሰዋል፡፡ በህገ-ወጥ አጓጓዦች አጓጉል መንገድ ስንቶች ለሞት ተዳርገዋል? በየእስር ቤቱ ያሉ ወገኖች መጨረሻቸው ምንድን ነው? በየእስር ቤቱስ የሚደርስባቸው በደል ምንድን ነው? በዚህ ዙሪያ በተከታታይ እናወራለን፡፡ የስደት መንገዳችን እንዴት ነው? ተሰደንስ ምን አፈራን?

ዋናው ደግሞ እኛስ በስደት ሀገር ምን እየሰራን ነው? ወገን ወገኑን አሳልፎ የሚሸጥበት፣ ለአደጋ የሚያጋልጥበት፣ ጥቂቶች በሚሰሩት መጥፎ ተግባር ሁሉም የሚወቀስበት፣ የሚታሰርበት ሁኔታ የለም? አለ፡፡ ይህንንም ለማየት እንሞክራለን፡፡ በተያያዥነት እንዲረዳይ ወይም መገለጽ አለበት የምትሉት ሀሳብ/መረጃ/ ካለ ላኩልኝ፡፡ መረጃ ልትሰጡኝ የምትፈልጉ ለአማራጭ ኢሜል መጠቀም ከፈለጋችሁ girum_tekl@yahoo.com ብላችሁ ተጠቀሙ፡፡

የምንሰራው መጥፎ ስራ ከእኛ አልፎ ሀገር ዜጋ የሚያስወቅስ፣ የሚያሰድብ የሚሆንበት ጊዜ የለም ወይ? የሚለውን ለማየት ስንነሳ ሴቶቻችን በሴተኛ አዳሪነት ተሰማርተው፤ ወንዶች በመጠጥና በሀሺሽ ንግድ በሌላም ህገ ወጥ ድርጊት ተሳትፈው የሚታዩበት ሁኔታ አለ፡፡ ሴቶቹ በሴትኛ አዳሪነት ተሰልፈው አሰደቡን፣ አዋረዱን የምንለውን ያህል ወንዶችም በዚሁ መስክ ተሰማርተው መገኘታቸው ያሳፈራል፡፡ ኩሉን ተኩሎ ሊፒስቲክ ተቀብቶ ታይት አድረጎ ለገበያ የሚቆም፣ ተደውሎለት ፒክ የሚደረግ ኢትዮጵያዊ አለ መባሉ ምን አይነት ስሜት ይጭርባችኋል? ዱባይ ካሉ ኢትዮጵያዊያኖች ጋር በዚህ ዙሪያም አውርቻለሁ፡፡ እመለስበታለሁ፡፡

ከዚህ ወጣ ብለን ተሰደን የሰራንበትን ቤተሰብ ለውጠናል ወይ? ለራሳችንስ ሆነናል፣ ጥሪት ቋጥረናል? የሚለውን ለማየት ስንሞክር ደስ የሚል እና የሚያሳዝን ነገር ልንሰማ እንችላለን፡፡ ጥቂቶች ደግሞ በሉብናን /ቤይሩት/፣ ዱባይ ሳዑዲ አረቢያ፣ ባህሬን.. ኩዌት ያሉ ሴቶቻችን የሱዳን ወንዶች ሲሻሙ እና የለፉበትን አባክነው ቤት ተከራይተውላቸው ማስቀመጣቸው እየተለመደ የመጣ ጉዳይ ነው፡፡

በዚህ ዙሪያ እንዲያውም አንድ ቤይሩት ያለች ጓደኛዬን ሳዋያት ሁሉን ነገር ነገረችኝ፡፡ አከለችናም ‹‹ በአጠቃለላይ የኢትዮጵያ ሴቶች ለሱዳን ወንዶች ይታገላሉ ማለት ያስችላል፡፡ ቤተሰቧ በርሃብ የሚቆላ ችግረኛ ሁሉ ስራ የጠላ በሴት ገንዘብ መቀመጥ የወደደ ሱዳናዊ ይዛ ቤት ኪራይ ከፍላ፣ አብልታ፣ አጠጥታ….አለችኝ ያሳፍራል፡፡ እዚህ የመንም ያለውን ሳይ በመውለድና በጋብቻ በኩል ሲታሰብ ከሀገር ያስወጣቸው የባል ችግር እስኪመስል ያገኙትን ሀገር ዜጋ አግብተው የሰሩበትን እያበሉ የሚኖሩ ያጋጥማሉ፡፡ አላማ መሳት ነው፡፡

ሰው ቤት፣ ድርጅት ውስጥ በጽዳት ተቀጥረው፣ አይገቡ ገብተው ገላቸውን ሸጠው ያገኙትን ለቁም ነገር ካላዋሉት ለምን መሰደድ አስፈለገ? ስትለፋበት የኖረችውን ገንዘብ ደግሳበት የሚበላው የሌለው ናይጄሪያዊ፣ ሶማሊያዊ..ህንድ፣ፓኪስታን…! ያገቡ እና ተያይዘው የእከክልኝ ልከክልህ ህይወት ሲመሩ ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡ ደግሞ የሚገርመው የፎቶ እና ቪዲዮ ትዝታ ለማስቀረረት ያላቸውን አንጠፍጥፈው ደግሰው ማግባታቸው፡፡ የተሻለ ሲያገኝ አመት ሳይሞላው ጥሏት የሄደ ሞልታለች፡፡ በዚህ ዙሪያ ብዙ እናወራልነአሁን የአፍሪካ ህብረትን አዲስ አበባ ላይ አድርገናል፡፡ ጎበዝ ከትንሽ አመት በኋላ ምን የአፍሪካ ህብረት ብቻ የተባበሩት መንግስታት ጽ/ቤትም ኢትዮጵያ እንዲሆን የምንጠይቅበት ሁኔታ እየተከሰተ ነው፡፡ ከአለም ያልወለድንለት ዜጋ ይኖር ይሆን? ቱቱ!!!...ቱቱ!.. ሴቶቻችን ማህፀናችሁ ይለምልም፡፡ አሜን በሉ!!


ጥቁሯ ቦርሳዬ
ክፍል 9
በግሩም ተ/ሀይማት

ሰላም ናችሁልኝ? ስላም ያድርጋቸሁ፡፡ የምመኝላችሁ ሰላም ነው፡፡ የዚህ ክፍል መልዕክት ‹‹አራዳ ለመሆን ከመፈንዳት ሰርቶ ይዞ መገኘት..›› የሚል ነው፡፡ አንኳር መልዕክቱን ወደታች ስንወርድ ፈረካክሰን እናያለን፡፡

አንድ በሉልን ፍቅር ልብስ የሚያስወልቀን አንሶ ሙቀትም ልብሳችንን እያስወለቀን ነው-የመን፡፡ ለስንቱ አውልቀን እንችላለን? ለፍቅር የምናወልቀው አንሶ ስል አሳብዶን እንዳይመስላችሁ..ያው ህብረ-አንሶላ ለመፍጠር..አይ እናንተ አሳፈራችሁኝ፡፡ ታዲያ በዚህን ሙቀት ቁም ነገር ብቻ ማውራት ሲያልብ በብርጭቆ ወረቀት እንደመጥረግ ይቆጠራል፡፡ ለነገሩ ብዙ ሲሪየስ ወግ አወጋኋችሁ፡፡ ድክም ያላችሁ ባይመስልም አረፍ እንድትሉ ፈለኩ፡፡ ምን መፈለግ ብቻ ከተመቻችሁ እና ጥርሳችሁ ከመጣ መሳቅ ይችላል፡፡ ታዲያ አደራ ሲትስቁ ንገሩን እኛም እናጅቦት፡፡ ምናለበት ዘንድሮ ሁሉን ነገር ቀየር አድርገን ባልተለመደ ሁኔታ ብንጓዝ? ብቻ ከማግጠጥ በአጃቢ መሳቅ ደስ ይላል፡፡ ከተቻለ አጀባውን በባንድ እናደርገዋለን፡፡ እንዳልኳችሁ ዘንድሮ ባልተለመደ መንገድ ብንጓዝ ምን ይመስላችኋል? ሀበሻ ምቀኛ ነው የሚለውን ለውጠን ሀበሻ የሚተጋገዝ፣ የሚረዳዳ ነው ለመባል እንጣር፡፡ ሀበሻ ምቀኛ ነው፣ ወሬኛ ነው፣ ተንኮለኛ ነው...እያለ የሚያወራው ራሱ ሀበሻ መሆኑ ደግሞ ይበልጥ የሚያስገርመኝ ነው፡፡ እንዴት ሰው ራሱን ይሰድባል? ደሙን አላስወጣ፣ አላስለወጠ አፉን ሞጥሞጥ አድርጎ ብቻ ሀበሻ ሲባል…ይላል፡፡ ራሱን መስደብ ራሱን ማዋረድ የለመደ ህሊና እንዴት ራሱን ከፍ ማድረግ ያስብ..ባልተለመደ መንገድ እንጓዝ ያልኳችሁም ለዚህ ነው ይሄን ሰንካላ አባባል ጥለን እብስ….

ታዲያ ይህን ጥለን ስንጓዝ የአራዳ ልጅ ነን እያልን በባዶ መኮፈስንም አስቀምጠናት እንለፍ፡፡ ተግቶ በማስራት ስለሆነ መለወጥ የላጪን ልጅ ቅማል በላው እንደሚባለው ያራዳን ልጅ ፋራ በላው እንበል? ጎበዝ እንዳትጃጃሉ ግጥም አድረጎ በልቶታል፡፡ ፋራ የተባለው አቀርቅሮ ሲስራ አራዳ የተባለው ሙድ ሲይዝ ሙዱ ጉዱ ሆኖት ቀርቷል፡፡ አራዳ ማለት በልጦ መገኘት ነው፡፡ አራዳ ማለት ሰርቶ ማግኘት ይሁን እስኪ..አራዳ ማለት ይዞ መገኘት ነው፡፡ አራድነታችሁን ካልተጠቀማችሁበት እንደ እኔ ኑሩበት፡፡ እኔን ብታዩ በኑሮዬ አራዳ ነኝ፡፡ ያውም ሴንተሩ ላይ…ቤቴን ነው ያልኳችሁ፡፡ ማለቴ አራዳ ክ/ከተማ ነኝ፡፡ አሁን አራዳ ለክፍለ ከተማነት መጠሪያ ብቻ ቢያገለግል ነው የሚመረጠው፡፡ ልብስ ማንኳተት ቃላት ማንጋተት ጥቅም የለውም፡፡

አቤት ይሄን የሚያነቡ የአራዳ ልጅ ተብዬዎች…ልመቻችሁ ብሎ…ማለታችው አይቀርም….በቃ አኩርፈውኝ አጠገባቸው ሆኖ ላጤናቸው ፊታቸው ለጉድ ተዘፍዝፎ ይታያል፡፡ ይህቺ ፊትህን ዘፈዘፍከው፣ ጣልከው የአንድ ሰሞን ቋንቋ ነበረች፡፡ የአራዳ ልጆች የተሻሻለች ስድብ ናት፡፡ አሁንም ትሰራለች፡፡ በቃ! እነዚህ እነ እንትና አራዳ ነን ብለው ሞራላችን ላይ እቃ..እቃ ተጫወቱብንኮ የምሬን ነው፡፡ እርድና ቋንቋ ማበላሸት ነው እንዴ? አንዱ አንድ ቀን ምን አለኝ መሰላችሁ? ምነው ጣልከው አለኝ፡፡ ዞር ብዬ የጣልኩት ነገር እንዳለ ስፈልግ ሳቀ፡፡ እምቢኝ ብሎ ከከንፈሩ አምልጦ ውጪ ያደረ ጥርሱን የበለጠ አስገጥጦ ተንከተከተ፡፡ እንሹካ የተገተረ ጥረሱን ለመሰብሰብ እየሞከረ ‹‹ፊትህን ጣልከው ነው ያልኩህ..›› አለኝ እና አረፈው፡፡

በእውነት ፋራ አይደለሁ ጣልከው ሲለኝ ላነሳ መዞሬ? አሁን በእናታችሁ የእኔ ፊት ጣልከው የሚባል ነው? መደመሪያውኑ የሰላሌን ሜዳ መስሎ ወድቆ የለ? የፊቴን ስፋት ልብ አላለውም እንጂ ከመስፋቱ የተነሳ ግማሹን አሳርሼ ግማሹ ላይ የሪል ስቴት ግንባታ መጀመሬን ቢያውቅ ጣልከው ባላለ፡፡ ውይ የእኔ ነገር ፊቴ የሚታያችሁ መስሎኝ ነው እኮ፡፡ እውነትም ፋራ ነኝ አይደል? እኔ የምለው ከምር እንነጋገር እስኪ ፀጉር ካላሳደኩ፣ የተንጀላጀለ ሱሪ ካለበስኩ፣ መርገጫው ሸክም የሆነ መጫሚያ ካልተጫማሁ፣ ቋንቋ ካላንሸዋረርኩ አራዳ አልባልም ማለት ነው?

አንድ ሰሞን ብቅ የሚሉ አባባሎችን እንመልከት እስኪ..ይመችህ ይመችሽ፣ አይ-ደል? የራስሽ..የራስህ ጉዳይ፣ ንገረው ለእገሌ ንገሪው ለእገሌ፣ ሲላጥ ሲላላጥ../ሰው እንደ ድንች እንደ ሽንኩርት ሲላጥ ይታያችሁ../ ደሞ እነሱ እንደሚያደርጉት ቃላትን ያለቦታቸው ሸጉጠን የአነጋገር ፋሽን ካልተከተልን አራዳ አይደለንም ማለት ነው? እኔን የፈለገ ፋራ ይበለኝ እንጂ አልጠቀምም፡፡ ከዚሁ አንድ ሰሞን ብቅ ከሚሉ ሰሞነኛ ቃላት ዙሪያ ሳልወጣ ‹‹ፍንዳታ›› ስለምትለው ቃል አስባችሁ ታውቃላችሁ? ፈነዳ፣ ፈነዳች..ፍንዳታ! ሆሆይ..በቃ! ፈነዳ የሚለው ቃል እኮ ትርጉም አጣ ማለት ነው፡፡ የተስፋዬ ካሳ ቀልድ ላይ ፈንዱ..የምትለውን የእንግሊዘኛ ቃል ታካ ‹‹..ካልፈነዳን አትረዱንም?..›› የምትል አባባል አለች፡፡ አስቃን አልፋለች፡፡ የአሁን ፍንዳታ ትርጉም ግን የተለየ ነው፡፡

እስኪ በእናታችሁ አንድ ነገር ላስቸግራችሁ፡፡ ብዙ አይደለም የማስቸግራችሁ አይናችሁን ጨፈን አድርጉ እና በምናባችሁ ሰው ሲፈነዳ ለማየት ሞክሩ፡፡ አያችሁ? ቆይ አረ እኛም ፈንድተን ነበር እንዴ? ወይ ጉድ ለካ ሳናውቀው ፈንድተን አልፈናል፡፡ ንገሩኝ እስኪ ፍንዳታ የሚለው ፊቱ ላይ ቡግር ወጥቶ የፈነዳለት ነው? ያኔ ነው ሀገሬ እያለሁ ፍንዳታ የሚባሉት ምን አይነቶች እንደሆኑ ለማወቅ ዳዳሁና አንድ የሰፈሬን ጎረምሳ /በእነሱ አጠራር ፍንዳታ ልበለው?/ ጠየኩት፡፡ የተለያዩ ምልክቶችን እና የሚያሳዩትን ባህሪ ነገረኝ፡፡ ለምሳሌ እንደ እገሊት ብዬ የሆነች ልጅ ጠቀስኩለት፡፡ ‹‹ውይ እሷማ ፈንድታ ጨርሳ ስትፈነዳ ያዝረከረከችውን አሁን እየሰበሰበች ነው..›› አለኝ፡፡ ድንቅ አነጋገር ነው፡፡ ሲፈነዱ ያዝረከረኩትን ሲያልፉ መሰብሰብ መቻሉም ጥሩ ነው፡፡ ግና እንዴት?

እዚህ ጋር ከአንድ ቴያትር ላይ የመዘዝኩትን አባባል ላዳምቅበት፡፡ ‹‹ከዘጠኝ ቀሚስ ለበስ ፈላስፋ ጋር ቁጭ ብሎ ከማውራት ኩንታል ድማሚት ላይ ተቀምጦ መፈንዳትን እመርጣለሁ…›› ከዳንዲዬ ጨቡዴ ቴያትር ላይ ነው የወሰድኩት፡፡ ከፈለገ እሱ ይፈንዳ እንጂ ፈንዱ ለማለት ሳይሆን መዝዤ ያወጣሁት መፈንዳት ድማሚት ላይ ተቀምጦ እንጂ እንዲሁ እንዴት ይፈነዳል? የሚለውን እንድታስቡት ነው፡፡ ጃክ ኤንድ ፋት ማን ፊልም ላይ የሚሰራው ፋትማን ፈንድቶ ነው የሞተው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ እሱስ ውፍረትም ነበረው የእኛን እኮ ዝም ነው፡፡ የምር ቋንጣም ይፈነዳል እንዴ? ነገሩ እንደዛ ነው የሆነብኝ፡፡

እዚህ የመን ግን ነገር ተገልብጧል፡፡ ፍንዳታውንም፣ ማፈንዳቱንም፣ መፈንዳቱንም በደንብ ያውቁታል፡፡ ትላንት እንኳን አንዱ የታጠቀውን አፈንድቶ እሱም ፈንድቶ አስር ሰዎችን አስከትሎ ነጎደ፡፡ አሸባሪዎቹ ይህን ፍንዳታ እና ማፈንዳት ይዘውታል፡፡ ፍንዳታ ማለት እንሱ ናቸው፡፡ የፈነዱ የሚፈነዱ….ሜይ 21 ቀን ወታደሮች ሰልፍ ልምምድ ላይ እያሉ ያፈነዳው 103 ወታሮችን በታትኗል፡፡ ስጋቸው እንደ አሸዋ ክምር በአካፋ እስኪዛቅ፡፡ ግሩም ፈነዳ ቢሏችሁ ጎረመሰ መስሏችሁ ዝም እንዳትሉ፡፡ አንድ ፎቅ የሚበታትን ፈንጂ የታጠቀ ከገጠመኝ ነው፡፡ አይግጠም ነው፡፡ እዚህ እውነተኛው ፍንዳታዎች ናቸው፡፡

ልጄ ለአቅመ ሔዋን ደረሰች፣ ልጄ ለአቅመ አዳም ደረሰ በማለት ፋንታ ልጄ ፈነዳ/ፈነዳች/ ልንል ነው? ስለ ፍንዳታዎች ባህሪ የምታውቁ እስኪ ጻፍ ጻፍ አድረጉና አስነብቡን፡፡ በአንድ ወቅት የቡሄ ሰሞን በየመንደሩ ርችት የሚያፈነዱ በዝተው ነበር፡፡ ሽማግሌው ኪስ፣ ጫማ..ውስጥ እየከተቱ ‹‹ጧ!..›› ያደርጋሉ፡፡ ያፈነዳሉ እንጂ አይፈነዱም፡፡ ሰው ያስደነግጣሉ፣ ጆሮ ያደነቁራሉ፡፡ ታዲያ ማን ይሙት እነዚህን ልጆች እደጉ ተመንደጉ አመት አመት ያድረሳችሁ ብሎ የሚመርቃቸው ይኖራል ብላችሁ ታስባላችሁ ? ወይድ በአጭር ያስቀርህ፣ ያፈንዳህ ከማለት የዘለለ ማን ሊቸራቸው? ያፈንዳህ እየተባሉ ይሆን ፍንዳታ የሆኑት? እንጃ ብቻ እንጃ፡፡ ‹‹ከመፈንዳት አካባቢን ማጽዳት›› የምትል ጽሁፍ አካባቢያቸውን ያሳመሩ ልጆች ጽፈው አይቻለሁ፡፡ አሪፍ አይደለች? አራዳነት በስራ የሚለውን አይጠቁምም ብላችሁ ነው? ድሮ ድሮ አራዳ ማለት ያለውን የሚያካፍል እንጂ ቁጭ ብሎ የሰው እጅ የሚጠብቅ አይደለም፡፡ እንደዛማ ከሆነ በልመና የተሰማሩ ሁሉ አራዳ ናቸው ማለት ነው፡፡ የሰው እጅ ከማየት ሰርቶ ማግኘት፡፡ አራዳነት ይዞ መገኘት፤ ሰርቶ መለወጥ ከሆነ ቆየ ያላወቃችሁ አራዶች ንቁ!!!!...
ሰላም ሁኑ!!..

ጥቁሯ ቦርሳዬ ክፍል 8
‹‹..ፍቅርን በአረቢኛ እንዴት ታነንሾካሹክለት ይሆን?.. ››
ወግ በግሩም ተ/ሀይማኖት

‹‹ሀሎ! ጤና ስጥልኝ!...›› አልኩ ሞባይል ስልኬን ከፍቼ፡፡ የደወለልኝን ሰው ቁጥር ከዚህ በፊት ባላውቀውም ተገቢው ሰላምታ ይድረሰው ብዬ ነበር ሰላምታ ማቅረቤ...

‹‹ምን ጤና ይሰጠኛል ጤና የነሳኝን ወሬ ላቀብልህ ነበር..›› ብስጭት የታከለበት ጎርናና ድምጽ ነው፡፡

‹‹ደስ ይለኛል ወዳጄ መቼ ላገኝህ እችላለሁ?›› ላልኩት ጥያቄ የሰጠኝ ምላሽ አሁኑኑ የሚል ሆኖ የት እንዳለሁ ጠየቀኝ፡፡ ነገርኩት፡፡ ሩቅ ቦታ ስለሆነ ከአንድ ሰዓት በኋላ እኔ ጋር እንደሚደርስ ነግሮኝ ተለያየን፡፡ እሱ እስኪመጣ ሰላምታዬን ለእናንተ ላድርስ፡፡ ሰላም ጤና ፍቅር ይስጣችሁ፡፡ የእዚህ ክፍል መርህ /መልዕክት/ ‹‹አስተውሎ መራመድ ብልህነት ነው..›› የሚል ነው፡፡ በእርግጥም አስተውለን የምናደርገው ነገር ፀፀት፣ ጉዳት፣ መጥፎ ስም፣ ህሊና የሚያስወቅስ ጭፍንነት.. የመሳሰሉትን ጉድፎችን አያስከትልም፡፡ አስተውሎ መራመድ ከግባችን መድረሻ አቋራጭ መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ ምርጫችን ይሁን፡፡

ሀበሻ እና ቀጠሮ ፀባቸው የከረረ ይመስል እስካሁን አልታረቁም፡፡ በቀጠሮ ሰዓት መገኘት ክብር የሚቀንስ እየመሰለን ይሁን እንደ በሽታ ተጠናውቶን በማርፈድ ታውቀናል፡፡ ‹‹የሀበሻ ቀጠሮ..›› እያልን ተጠናውቶናል፡፡ ለነገሩ ‹‹ማርፈድ የስንፍና ምልክት ነው..›› እየተባለ የሚጻፍበት ግንብ እና በር ያለው ትምህርት ቤት ብንማርም ማርፈድ አርቆ የማሰብ ውጤት ነው የተባልን ይመስል በርትተን ተያይዘነዋል፡፡ አንዳንዱማ ለሁለት ሰዓት ቀጠሮ አራት ሰዓት ከቤቱ የሚነሳ አለ፡፡ ይህ ሰው ራሱን ይመርምር ዓለም ከሚጓዝበት ምህዳር በሁለት ሰዓት የዘገመ ሊሆን ይችላል፡፡ ጎበዝ ቀጠሮን እናክብር በሰዓት /በጊዜ/ ስንቀልድ በተገላቢጦሽ እየቀለደብን ነው፡፡

ከአንድ ሰዓት በኋላ ያለኝ ቀጣሪዬ ሶስት ሰዓት ከሀያ ደቂቃ ያህል ቆይቶ መጣ፡፡ ለምን አረፈድክ ብሎ መጠየቅም መቆጣትም አይቻልም፡፡ የሀበሻ ወጉ ማርፈድ ነውና ወግ ጠባቂ ብሎ ‹‹እንኳን ደህና መጣህ›› ብቻ ማለት ነው፡፡ ለነገሩ ያለሁት ሱቅ ውስጥ ስለሆነ ቢመጣም ባይመጣም እዛው ነኝ የት መሄጃ አለኝ? ቁጭ ብለን አወጋኝ፡፡ ስስቅ፣ ሳዝን፣ በስራችን ሳፍር አዳመጥኩት፡፡ የሰማነውን በልቦናችን ያሳድርልን…የሚለውን ቀየር አድርጌ የሰማሁትን በፌዝቡክ ላይ ያኑርልኝ ብዬ አሳረፍኩት እነሆ፡-

ፌዝቡክ ላይ የምትፅፋቸውን እከታተልሀለሁ፡፡ የመን ያሉ አስገራሚ እና አሳዛኝ ታሪኮችን ስታነሳ የእኔ ቢቀርብ ብዬ ነው አለኝ፡፡ ወደ ዋናው ወሬ ሲገባ ደግሞ ‹‹..ከሚስቴ ጋር የተዋወቅነው ቤት ልትከራይ መጥታ ነው፡፡..››ሲል ትረካውን ጀመረ፡፡ ያው ወሬው አደባባይ ሊውል ከተጀመረ ወደኋላ ምን ያደርጋል? ፍርጥርጥ እንዲያደርገው የሚል እሳቤ መጣብኝና ‹‹እንዴት?›› የሚል ጥያቄ አቀረብኩለት፡፡

ያው ታውቀዋለህ እዚህ ሀገር ሶስት ክፍል ቤት ነው የምትከራየው ከዛ የምትይዘውን ክፍል ትይዝና ቀሪውን ለሌላ ማከራየት ነው፡፡ ለደላላዎች ነግሬ ስለነበር ለኮንትራት ስራ መጥታ ሁለት አመት ሳትሰራ በሚደርስባት በደል ተማራ የጠፋች ልጅ በደላላው አድራሽነት እኔ ጋር ያለውን ቤት ልትክራይ መጣች፡፡ ተስማማን እና ኪራዩን ከፍላኝ እቃ ልግዛ ብላ ስትሄድ ሀገሩን ስለማታውቅ ላጋዛት ሄድኩ፡፡ ፍራሽ ብቻ ነው የገዛችው፡፡ ማደሪያ ስለ ሌላት ልታድርበት ነው ፍላጎቷ፡፡ አንሶላ የለ ብርድ ልብስ..አሳዘነችኝ፡፡ እዚህ ላይ እንዴት ትተኛለሽ እኔ ጋር ግቢ እና አልጋው ላይ ተኚ እኔ መሬት እተኛለሁ አልኳት፡፡ ተስማማን አደረች፡፡ በማግስቱ ስራ ስለሌላት ቁልፉን ሰጥቻት ሄድኩ፡፡ ምክንያቱም ቴሌቪዥን እንኳን እያየች ትዋል ብዬ ነው፡፡ ጊዜው ባዶ ቤት ውስጥ እንዴት ይሄድላታል? ምግብም አብስላ ብትበላ ትንሽ እቃ ስላለኝም ብዬ ነው፡፡ እኔው ቤት ዋለች ከስራ ስወጣ ምሳ የምትበላው ነገር እና ጫቴን ይዤ ሄድኩ፡፡ ቡና አፈላችልኝ…እኔው ጋር ዳግም አደረች፡፡ አሁን ግን አልተላለፍንም፡፡ በዛው ገባች በቃ!..ኪራዩ ቀረና ሌላ ሰው ተከራየው…ስራፈልጌ አስገባኋት፡፡

አልጋ ላይ ደስ የሚል ወሲብ ጣር አላት፡፡ በስሜ እየጠራች ‹‹ኡህ..ውይ..››በሚል ይጀመርና የእኔ ፍቅር፣ የእኔ ማር፣ የእኔ አንበሳ…ፍቅር ነህኮ ኡህ…ደስታን ካንተ አገኘሁ…›› ብዙ ብዙ ትላለች፡፡ ይህ ነገሯ ከለስላሳ ሙዚቃ የበለጠ ተመቸኝ፡፡ በጣምም ወደድኳት፡፡ ለሁለት አመት አብረን ኖርን፡፡ ጭፍን ያለ ፍቅር ውስጥ ገባሁ፡፡ ነገሩ የመጣው ከዚህ በኋላ ነው፡፡ ከምትሰራባቸው ሰዎች ሴት ልጅ ጋር ሲላመዱ ምስጢር ይገላለጡ ጀመር፡፡ የወንድ ጓደኛዋ ትውልደ ኢትዮጵያዊ እንደነበረ እና እንደተጣላት ነገረቻት፡፡ በባህላቸው ሴት ስታገባ ልጃገረድ ሆና ካልተገኘች ‹‹ጃንቢያ›› በሚባለው ሆዳቸው ላይ በሚታጠቁት ስለት እንዲገላት የሚፈቀድለት ወንድሟ ስለሆነ..እንዴት ጓደኛ ልትይዝ እንደቻለች የእኔዋ ልጅቷን ጠየቀቻት፡፡ በዛ ላይ ወንድና ሴት አንድ ላይ መሄድ አይቻልም እንዴት ትገናኛላችሁ? አለቻት፡፡

እናቷ በአደጋ ምክንያት አይናቸውን ሲታወሩ ትውልደ ኢትዮጵያዊው የሚፈልጉበት ቦታ እንዲያንቀሳቅሳቸው በሾፌርነት ተቀጠረ፡፡ ገብቶ ሲላመዱ እንደ ጀመሩ ነገረቻት፡፡ እናቷ አይኗን በመታወሯ ምክንያት አባትየው ስለፈታት ለብቻዋ ነው የምትኖረው፡፡ ልጅትም እሷ ጋር እሄዳለሁ ብላ ትሄዳለች፡፡ እሱ እዚያ በሾፌርነት ስለሚሰራ እዛው ይገናኛሉ..ሌላውንም ሌላውነም ብቻ ምስጢሯን ሁሉ አጫወተቻት፡፡ አያይዛም ሀበሻ ለፍቅር እንደሚሆን በትውልደ ሀበሻው እንዳየችና አንድ ሀበሻ እንድታስተዋውቃት ጠየቀቻት፡፡ ከመሳሳም ውጭ ምንም ማድረግ እንደማትፈልግ አሳወቀቻት፡፡ ወሮታውን 200 ዶላር ልትከፍል ለውንዱም የፈለገውን ልታደርግለት ስለተስማማች የእኔዋ ሚስት እድሉ ለሌላ እንዳይወጣ ፈልጋ አማከረችኝ፡፡ እኔም በጽዳት ሰርቼ የማገኛት ከሲጋራ፣ ጫት ሱሴ እና የቤት ኪራይ የማትዘል ሳንቲም ይልቅ በዚህ ጥሩ ልጠቀም እንደምችል ገምቼ ተስማማሁ፡፡..አለኝ ታሪኩን የሚያወጋኝ ወጣት፡፡

እዚህ ጋር የፍቅርን ህልውና እንድጠራጠር አደረገኝ፡፡ ሰው የሚወደውን ሰው እንዴት ለጥቅም ብሎ አሳልፎ ከሌላ ሰው ጋር እንዲሳሳም ያቀራርባል? የምወደውን ሰው እንኳን ለሌላ ማሳለፍ ቀርቶ ቅንጣት የጸጉሯን ስባሪ እንዲነኩብኝ አልፈልግም፡፡ ለነገሩ እዚህ አረቡ አለም ላይ ያሉ ጥቂት በጣም ጥቂት ኢትዮጵያዊያን ወንዶች ሴቷ ገላዋን ሸጣ የምታመጣውን ጠብቀው የሚኖሩ አሉ፡፡ እነዚህ ጥቅም ፈላጊዎች እንጂ ፍቅር ናፋቂዎች አይደሉም፡፡ ወይ ፍቅር…..

ከሱ ጋር ወዳወራሁት ስመለስ…. በስምምነታችን መሰረት የልጅቷ እናት ጋር በሳምንት ሶስት ቀን የጊቢውን አትክልት መንከከባከብ በሚል ሰበብ ተቀጠርኩ፡፡ ከልጅቷም ጋር እንደ ተባልኩት ተግባባን፡፡ ተጀመረ፡፡ ህሊናዬ ባይቀበለውም ከሚስቴ ጋር የማደርገው እያስመሰልኩ ህሊናዬ እየተሟገተ ገባሁበት፡፡ ከመሳሳም ያልዘለለ ግንኙነታችን ለትንሽ ጊዜ እንደተጓዘ መግባባት ስንጀምር በማይሆን ሁኔታ እንድንወስብ ጠየቀችኝ፡፡ ይህን አይነት ድርጊት እኔ ተጠቅሜ አላውቅም አንቺ ለምን በኋላ ማድጉን ፈለግሽ አልኩ፡፡ ስታገባ ድንግል ካልሆነች እንደሚገሉዋት እና በፊት ከነበረው ጓደኛዋ ጋር እንደዚህ እንደነበር የሚጠቀሙት ነገረችኝ፡፡

ከድርጊት በኋላ ተጋድመን ስታውራኝ ከእኔ ጋር ደስ የሚል ጊዜ ልታሳልፍ እንደፈለገችና የጠየቀችኝን እንቢ ማለቴ እንዳስከፋት ነገረችኝ፡፡ ስትቀጥልም..ሀበሻ ለፍቅር አመቺ እንደሆነ እሷ ብቻ ሳይሆን አባቷም ያውቃሉ፡፡ ሚስታቸውን የእሷን እናት መሆኑ ነው ከፈቱ ጀምሮ ከሰራተኛቸው ጋር እንደሚቀብጡ ታውቃለች፡፡ እንደተመቸቻቸውም ነግረዋታል፡፡ ልቤ ቀጥ አለ፡፡ የምሰማው ቅዠት እንጂ እውነት አልመስልህ አለኝ፡፡ ጆሮዬን የመስማት ጉጉት አርገበገበው፡፡ ለነገሩ በየቤቱ ሁለት ሶስት ሰራተኛ ሲለሚኖር ሌላዋን ይሆናል እንጂ የእኔዋን ውድ አይሆንም ሲል ውስጤ ውስጤን አጽናናው፡፡ ጠይቄ ቁርጡን ማውቅ ፈለኩኝ፡፡ ልቤ ግን ምቱን ጨምሮ ጉሮሮዬ ስር ተወተፈ፡፡ የሚገርም ነው በተፈጥሮዬ ለመጀመሪያ ጊዜ በመከዳት እንባ ተናነቀኝ፡፡ አላለቅሰው ምኔ ናት ልበላት? በምን አለቀስኩስ ብዬ ሰበብ ልስጥ? የእኔን በዝምታ ተለጉሜ መቆየት ሰብራ ወደ ወሬያችን እንድንመለስ ስትል ሳልጠይቃት ዘረገፈችው፡፡

ከሰራተኛቸው ፋጡማ ጋር ግንኙነት እንዳላቸው እና በጣም እንደተመቸቻቸው የነገሯትን አወራችኝ፡፡ ግንባሬ ላይ ችፍ ያለው ላብ ይሁን አይኔ፤ ላይ ታቁሮ የነበረው እንባ አላወኩም ጉንጬን ሰንጥቆ ወረደ፡፡ እልህ ተናነቀኝ፡፡ ግጥም አድርጌ መሳም ሳይሆን የመንከስ ያህል ትንፋሽ እስኪያጥራት ሳምኳት፡፡ በሁኔታዬ ግራ ተጋብታለች፡፡ ለፍቅሬ መታመን ስል ከመሳሳም ውጭ ሌላ ነገር ውስጥ እንዳልገባ ስታገል መቆየቴ አናደደኝ፡፡ ለፍቅሬ መታመን ስል ነበር ጠቀም ያለ ገንዘብ ልትሰጠኝ እናድርግ ያለችኝን እንቢ ያልኩት፡፡

ውስጤ ሌላ ሀሳብ አፈለቀ፡፡ ያለችኝን እንቢ ስለላኩዋት ሌላው ሀበሻ ያደርጋል ብላ ለማሳመን ውሸቷን ቢሆንስ? ደግሞ አባትስ ከእናቷ ውጭ ሌላ ሴት ማድረጋቸውን እንዴት ሊነግሩዋት ቻሉ? ውሸቷን ነው የሚል ሀሳብ ነበር፡፡ ምነው እንዳሰብኩት ውሸት በሆነና እፎይ ባልኩ፡፡ ያሰብኩትን ሀሳብ አቀረብኩላት፡፡ ምን አቀጣቅጧት እቴ…ምን ታድርግ ቁስሌ አልገባት..የፍቅሬ መናድ አያሳዝናት….ለምኗ ብላ ትሸሽገው? እንኳን እኔ አንዱ ደካማ ሰው ይቅርና ወገኔ ያልኩት ሁሉ የማይችለውን ጉድ ዘረገፈችልኝ፡፡ ከሀያ ቀን በፊት እሷ ራሷ በዚህ ተግባር ላይ እያሉ ይዛቸው ስትቆጣ አባቷ ከእናቷ ፍቺ በኋላ ፋጡማ ስለተስማማቻቸው እንደሆን ቶሎ ማግባት ያልፈለጉት እንደነገሯት ጭምር ስትነግረኝ የምይዝ የምጨብጠውን አጣሁ፡፡ እሷ ግን ቀጠለች፡፡ እንዳይወልድ መጠንቀቅ እንዳለበት ለስሙ ጥሩ አንዳልሆነ ስነግረው ‹‹..ከዚህ በኋላ እጠነቀቃለሁ፡፡ ባለፈው አርግዛ እንድታስወርድ አደረኩኝ..›› አለኝ፡፡ እሱ ወንድ ስለሆነ ነው የሚናገረው እኔ ብሆን ግን ይገሉኛል ለዚህ ነው…እያለች ታወራልች፡፡ እኔ ግን አስብ የነበረው ሳንደራጅ፣ ተቀማጭ ሳይኖረን፣ በዚህ ኑሮ መውለድ የለብንም ብላ አሳምናኝ ያደረገችው ውርጃ የአባቷ ጽንስ ቢወለድ ኖሮ የሚከሰተውን ነው፡፡

ክዳቷ ውስጤን በቁጭት አርመጠመጠው፡፡ የጠየቀችኝን ተቀብዬ ስንተኛ ወዴ ፍቅሬ በ200 ዶላር አሳልፍ እንደሸጠችኝ እያሰብኩ ነበር፡፡ በእልህ የጀመርኩት ነገር ግን ባላሰብኩት ሁኔታ ቀጠለ፡፡ ከኋላ ትቼ በተፈራው ቦታ ገባሁበት፡፡ ከዚህ በኋላ ህይወቴ አደጋ ላይ እንደሆነ አውቃልሁ ያወቁ ቀን ይገሉኛል፡፡ ያለኝ አማራጭ ወደ ሳዑዲያ መጥፋት ብቻ ነው፡፡ ሀገሬ የምገባበት ፓስፖርት የለኝ፡፡….አይኖቹ እንባ አቅርረው ስለነበር ጥያቄ ቢኖረኝም የባሰ ሆድ ማስባስ ስለሆነብኝ ተውኩት፡፡ እሱ ግን ‹‹..እሷ እኔ አለሁ አይነኩህም ብላ እንደሰጠችኝ ተስፋ በተስፋ ተሰንጌ መኖር አለበለዚያ በተለያየ መንገድ ከዚህ የምውጣበትን መፈለግ ካልሆነም ሞት መጠበቅ ነው እጣዬ…ይሄው ነው ከፈለክ ጻፈው፡፡ ካፈለክ…›› ብሎኝ ሊሄድ ተነሳ፡፡ ሚስትህስ አሁን በምን ሁኔታ ናት? መለስ ብሎ ስልኬን ከእጄ ወሰደ እና ቁጥሯን ጽፎ ‹‹..ያን ዜና ከሰማሁበት ቀን ጀምሮ አላየኋትም፡፡ ከፈለክ ደውልና ጠይቃት፡፡ ላንተም ይደርስህ ይሆናል..›› ብሎኝ ወጣ፡፡ ስርዓት ያጣው አነጋገሩ ቢያናድደኝም ምላሽ አልሰጠሁትም፡፡ ሆድ የባሰው በመሆኑ የሚናገረውን አያውቅም ወይ ስሜታዊ ሆኖ ነው ብዬ አለፍኩት፡፡

ባለፈው ልጇ እና ባሏ ላይ የፈላ ዘይት የደፋችው ሴት በፍርድ ቤት የተፈረደባትን ፍርድ በቀጣዩ አሳውቃለሁ ብዬ ነበር፡፡ ፍርዱ ሞት ነው፡፡ ግን ፍርዱ የሚፈጸመው ህጻኑ ባለበት መሆን ስላለበት ልጁ 18 አመት እስኪሞላው እስር ቤት እንድትቆይ ተውሰኗል፡፡
በቀጠይ ዘና በሚያደርግ ጽሁፍ እንገናኛለን፡፡
ቸር ይግጠመን፡፡