Monday, April 23, 2012


 ስለሜተር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ የማውቀውን እውነታ ለማስጨበጥ አንድ ዙር ጫር..ጫር ያደረኩትን አቋድሻችኋለሁ፡፡ በቀጥታ ወዳቆምኩት ቃለ ምልልስ ከምሄድ ደጋግመን በመገናኘታችን ምክንያት በአንድ ወቅት አስቂኝ ገጠመኝ ነበረ፡፡ በገጣሚ እና የሴት ደራሲያን ማህበር ፕሬዘዳንት በወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን /አሁን ኢንተርፕሪነር ሽፕ ስራ ተሰማርተው በኢቲቪ የሚተላለፈው ስራ ፈጠራ እና ተነሳሽት ውድድሩ ላይ ዳኛ ናቸው፡፡ በነገራችን ላይ ወ/ሮ ሙሉ በዛን ወቅት ነው የሴት ደራሲያን ማህበር ፕሬዘዳንት የነበሩት፡፡ በሌላ አባባል ብዙም ቅርርብ ስለሌለን ነው አንቱ ማለቴ እንጂ የየጥበብ ሰው አንቱ የሚባል ሆኖ አይደለም፡፡/ እና በወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን አስተባባሪነት ለጋዜጠኞች ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት ፈቀዱ፡፡ በሰዓቱ የወ/ሮ ሙሉ አላማ አፈወርቅ ተክሌ ከመገናኛ ብዙሀን ብዙ የራቁ ስለሆነ ለማቀራረብ የተደረገ መንገድ ነው፡፡ ምን ያህል ስኬታማ ሆኗል የሚለውን አላውቅም፡፡ ስለ ስኬቱ እና አሁን ስለማቀርበው ገጠመኝ የሚያስታውሱት ካለ ወ/ሮ ሙሉ እዚህ ላይ ቢጨምሩበት እጠይቃለሁ፡፡

       ጋዜጣዊ መግለጫውን ሊሰጡን ተጠራን፡፡ በቪላ አልፋ ጊቢ ውስጥ ነው ጋዜጣዊ መግለጫው፡፡ በኢቲቪ የአውደሰብ ፕሮግራም አዘጋጅ የሆነ ስለሺ ይሁን ሽመልሽ..ስሙ ተረሳኝ በቴሌቪዥን ፕሮግራሜ ላይ ላቀርቦት ፈልጌ በደብዳቤ ጠይቄዎት እሺ አላሉም፡፡ ከመገናኛ ብዙሀን የሚርቁት እርሶዎ ነዎት አለ…፡፡ ለዘብ ባለ አነጋገር መጀመሪያም ከልብ አልነበረም አጠያየቅህ ጋዜጠኛ ቢጋበትም ያንኳኳል እኮ…አሁን ማነው ምኒልክ የሚባል ጋዜጣ አዘጋጅ አለ፡፡ ስለእኔ ተከታትሎ ነው የሚሰራው መረጃውን ከየት እንደሚያመጣ ሁሉ ይገርመኛል፡፡ አንተ ግን ..መቼ ስሜን እንኳን አስተካክለህ ጽፈህ ነው….እያሉ ሲናገሩ አቋረጥኩና አሁንም አለሁ ጥያቴ አለኝ ስላቸው ሁሉም በሳቅ አደመቁት፡፡

       ወደ ቀረው ቃለ-ምልልስ እናምራ እና በኋላ ትንሽ በሌሎች ጉዳች ላይ እመለሳለሁ፡፡  በዛን ወቅት ሳናግራቸው Great minds of the 21th century የሚል ሽልማት ነበር የተሰጣቸው የአለም ሎሬትነት ማዕረግ ቢሰጣቸውም በየትኛውም የመገናኛ ብዙሀን አለመነገሩ ይገርመኝ ስለነበር ‹‹የአለም ሎሬየት የሚለው ማዕረግ የተሰጠዎት ቅርብ ጊዜ ነው ሲሰጥዎትም ሆነ ከተሰጥዎት በኋላ በመገናኛ ብዙሃን የተሰማ ነገር የለም፡፡ ይታወቃል ብለው ነው ወይስ ያልተሰማበት መንገድ ይኖረዋል?..›› ስል ጠየኳቸው፡፡ መልሳቸውም ‹‹ይሄ ነገር ያልተሰማው እኔ እንደሚመስለኝ ከንቀት የተነሳ ነው፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ መንግስት ቴሌቪዥንና ሬድዮ የሚያስተጋባው የሚታዘውን መሰለኝ፡፡ ያዘዘው ሰው ይኑር አይኑር አላውቅም፡፡ የአለም ሎሬት ለመሆኔ ክሪዲንሺያሉ /ማረጋገጫው/ ያው እዚህ የምታየው ነው..››

    ተነስቼ ዲፕሎማው ወዳለበት በመሄድ አየሁት፡፡ ከበርካታ ሽልማቶች መካከል ልክ እንደ ሌሎቹ ለራሱ በተሰጠው ዙሪያው ወርቅማ ከለር ባለው መስታዎት ፍሬም ውስጥ ተቀምጧል፡፡ ሽልማቶቹን ሳይ ስለ እሳቸው እስክንድር ነጋ የነገረኝ መረጃ ታወሰኝ እና በፍጥነት ዞርኩ፡፡ መጠየቅ ያለብኝ ሰዓት ነበረ እና ጠየኳቸው፡፡ ‹‹ዓለም አቀፋዊ ጉባዔ ላይ ለመገኘት ከነገ ወዲያ ወደ እንግሊዝ ይሄዳሉ በዚህ ጉባዔ መዝጊያ ላይ በታወቁት የታሪክ ተመራማሪ በአርነስት ኪም ስም የተሰየመ ሽልማት አለ፡፡ ለእዛ ሽልማት እጩ ነዎት ይህ ሽልማት ምን አይነት ነው?›› አልኳቸው፡፡

    ‹‹ይህ ሽልማት ክብር ነው፡፡ በገንዘብ በኩል የገንዘብ ተሸላሚነት የለውም፡፡ ለምን አብዛኛውን ጊዜ በሰው አእምሮ ውስጥ የሚኖረው እንደ ኖቬል በብዙ ሚሊዮኖች እና በሺህዎች የሚገኝ ነገር እንዳለ ነው፡፡ አስተዋፅዖው ስምህ ሪኮግናይዝድ መሆኑ ብቻ ነው..›› አሉኝ፡፡ በዚህ ዙሪያ ባለኝ መረጃ መሰረት ‹‹..እርስዎ በዚህ ጉባኤ ላይ አራት ወጥ የፈጠራ ስራዎትን ከ40 ምርጥ የስላይድ ስዕሎች ጋር ይዘው ይሄዳሉ ተብሏል፡፡ ምን ያህል እውነት ነው? ከስራዎችዎ ውስጥስ ለዚህ ጉባኤ እንዲሆኑ ብለው የመረጡበት መስፈርት እንዴት ነው? ከታሪክ፣ ከፈጠራ ምሉዕነት፣ ወይስ ከእነሱ አላማ ጋር የሚሄዱትን አስበው ነው?...›› የሚል ጥያቄዬን ሰነዘርኩ፡፡

     ‹‹ስለአፍሪካ ምንድን ነው አስተዋጽኦ የማደርገው? ስለሀገሬስ ምንድን ነው አስተዋጽኦ የማደርገው? በምልበት ጊዜ መጀመሪያ የኢትዮጵያን ስነ-ጥበብ ታሪክን ማጎልበትና አንዲት ስራ ዛሬ ላይ እንደ ወሬ እንደጫዎታ ሆኖ እኛ ካለፍን በኋላ ስለ እኛ ዘመን አንድ አስተዋጽኦ አድርጌ ማለፍ፡፡ እንደ አክሱም፣ ላሊበላ እንደ ቅርሳችን የሚሆን አንድ ነገር ለማውረስ ነበር፡፡ በዚህ ትግል ውስጥ በዚህ ሂደት ውስጥ ደግሞ አጋጣሚ ሆኖ አፍሪካውያኖች ለነፃነታቸው የሚታገሉበት ጊዜ ነበር፡፡ እና በዚህ ላይ እኔ ምን አስተዋፅዖ አደርጋለሁ? በምልበት ጊዜ ያው በአፍሪካ አዳራሽ የሚገኘው የመስታዎት ስዕል (ዘስትራግል ኤንድ ኦስፕሬሽን ዘ አፍሪካ ፒፕል) የሚለውን ሰራሁ፡፡…›› ይህን አባባላቸውን አሁን ላይ ሆኜ ሳስበው እውነት ለታሪክ፣ ለሀገር የሚቀር ነገር ስርተው አልፈዋል የሚለውን በድፍረት መናገር ያስችላል፡፡

     ስለዚህ ስዕል እና ስለሌሎች ስራዎቻቸው ቀጥለው ያሉኝ ‹‹..በውስጡ ያለው ፍልስፍና፣ የትግሉን ወደ ፊት ተስፋ ምን እንደሆነ እንዴት ማድረግ እንዳለብን ያሳያል ብዬ ከማምነው ስራዬ አንዱ ነው፡፡ በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ እኔ በሰዓሊነቴ ምንድን ነው አስተዋተጽዖ የማደርገው? ይሄው ተማርኩ፣ ታለንትም አለኝ፡፡ ነገር ግን ተመልሼ ሀገሬ በምሰራበት ጊዜ ምንድን ነው አንዱ በሀገር ውስጥ መገኘት ነው፡፡ ሁለት የሀገርን ታሪክ አውቆ ከዚህ ውስጥ ምን መጨመር ይቻላል ብሎ መስራት ነው፡፡ ያንን እውን ለማድረግ መስራት እና በስራዬ መግለጽ ነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያን ታሪክ አንኳር አንኳሩን በዘመናችን መታሰብ ያለባቸውን ወደ 28 ያህል ቴምብሮች ህዝቡም የሚያየው የእኛን ታሪክ በውጭ የሚያሳይ ፣በቀላሉ ሰው እጅ የሚገባ እነሱን መስራት ጀመርኩ፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ ከሚታዩት አንዱ ይሄ ኮሌክሽን ስታምፕ ያለበት ነው፡፡

   ‹‹…ከዚህ በላይ ደግሞ አፍሪካን በሚመለከት ደግሞ እንደዚሁ የአፍሪካ ቅርስ ምንድን ነው? ምንድን ነው የወረስነው? እንዴትስ ነው የምናስተዋውቀው? ወደ ፊትስ ምን መጨመር አለብን? የሚለውን አክዬ የአፍሪካ ቅርፅ (አፍሪካን ሄርቴጅ) የተባለው ዋናው ስራዬ አሁን በብሄራዊ ሙዚየም የሚገኘው ነው፡፡ አፍሪካኖች የታሪክ ደሀ አለመሆናችንን በስራዎቼ ሊያዩ እንዲችሉ፤ የፀሀይ መብራት ሲበራበት የሚታየው ስራዬ ብዙ ሰዎች ከውጭ ሀገር እየመጡ የሚመለከቱት እሱን ነው፡፡
 
     ከዚህ ቀጥሎ ምንድን ነው ሌላው ስራዬ ኮንሰርን ያደረገው የአፍሪካን አንድ መሆን፣ አንድ በመሆን ሰላምን አግኝተን፣ ራሳችን አውቀን፣ እያንዳንዱ ስራ ተገኝቶለት፣ በእኩልነት እና በህብረት፣ ፍቅር የሚጎለብትበት ዘመን ለማየት በስራዬ ጥረት ያደረኩበት ሁኔታ ነው፡፡ ይህ ስራዬ ኦ.ኤ.ዩ ከተመሰረተ በኋላ ኤምብለም ይውጣ በተባለ ጊዜ ያደረኩት ሶስት እጆች የጥቁሩ፣ የጠይሙ፣ የነጩ ተባብሮ አንድነትን ሲፈጥር የፀሀይ ብርሃን ይወጣል፡፡ የፀሀይ ብርሃን የህይወት ዋናው መንቀሳቀሻው ስለሆነ የሚል እሳቤ ነበረኝ፡፡ ከቆየሁ በኋላ ግን የአፍሪካ ህብረት ብቻ መች ይበቃል? የአለም ህብረት መኖር አለበት በሚል ያው እንደሚታየው አራቱ እጆች ተባብረው ሲተሳሰቡ አዲስ ብርሃን ይመጣል፡፡ ይህን እና ይህን የመሳሰሉትን ስራዎቼን በማየት ነው እነዚህ ሰዎች የጋበዙኝ፡፡›› የሚል ምላሽ ሲሰጡኝ ሌላ ጥያቄ አቀበልኳቸው፡፡

   ‹‹..እነዚህ አሁን የጠቃቀሱልኝ ስዕሎች ከእነሱ አላማ ጋር ይዳል ብለው ነው የመረጧቸው? ሽማቱንስ አገኛለሁ ብለው ያስባሉ? ብዬ ጠየኳቸው፡፡ በእርግጥ በነበረኝ መረጃ መሰረት ያ-ፋውንዴሽን በቂ ያለውን ሰው ያጫል ድምጽ ይሰጣሉ፣ ይሸልማሉ፡፡
 
    ‹‹እንግዲህ እዚህ ላይ ግልጽ ይመስለኛል›› አሉ እና በስላይድ ካዘጋጁት ስዕል ውስጥ የተወሰነውን አሳዩኝ፡፡ ቡርሽ ቤቷን አውቃ ገብታለች የሚል እሳቤ ውስጤ ተላወሰ፡፡ ልክ ነበርኩ፡፡ እሳቸው የተጠበቡት እያሉ እኔ ለማየት በመብቃቴ ኮራሁ፡፡ የምጣዱ እያለ የእንቅቡ ተንጣጣ ማለት ይሄኔ ነው፡፡ ውስጤ ያልነበረ ስዕል የመስራት ፍቅር ያኔ ተወልዶ አደገ፡፡ ለነገሩ የአለም ዋንጫ ሰሞን ሁሉ ኳስ ተጫዋች መሆን ያስብ የለ? የእኔም ሀሳብ ከዛ አልዘለለም፡፡ ያሳዩኝን ሲጨርሱ የሰጡኝ መልስ….

   ‹‹እነሱ እኔን ለመጋበዝ ያላቸው ምክንያት ስራዎቼ ከእነሱ አላማ ጋር የገጠመ በመሆኑ እና አሁንም ይሄ ሰውዬ ራሱ/አርነስት ኪይ/ የአለምን እንደዚህ አይነት ነገር አስተዋፅዖ የሚያደርጉትን ሰዎች በመብራት እየፈለገ ታሪካቸውን ይፅፍ ስለነበር እሱ በአረፈ ጊዜ በስሙ ይሄ ፋውንዴሽን ተመሰረተ፡፡ በኮንግተረሱ ላይ የሚገኙት አብዛኛዎቹ ኢንቨስትጌትድ ናቸው፡፡ በእነሱ መካከል ይሄን አላማ በፈጠራ ስራው ያራምዳል የሚሉትን የዛ ፋውንዴሽን ሴኔት ሽልማት ይሰጣል፡፡ እኔ ራሴም ኮንግረሱ ላይ እሄዳለሁ እንጂ ለዚህ ሽልማት እበቃለሁ ብዬ በሀሳቤ የለም፡፡›› አሉኝ፡፡ ቢሆንም ግን ሽልማቱን ተቀብለው ከመጡ በኋላ ተገናኝተን ‹‹ይበልጥ እንድሰራ ያበረታታኛል እንጂ አያሰንፈኝም፡፡›› ብለውኛል፡፡ ቃለ-ምልልሱን በደረግንበት ወቅት እስካሁን ከተሸለሙት ውስጥ የትኛውን ይበልጥ ይወዱታል? የትኛው ነው የበለጠ ክብርስ ያለው? ብያቸው ነበር፡፡ ማበላለጥ ይከብዳል ሁሉም የሚሸልሙህ ስራህን ወደው አክብረውህ እስከሆነ ድረስ አንተም የሸለሙህን ልታከብረው ግድ ይላል፡፡ ቢሆንም ግን ዋጋቸው /ክብራቸው ይለያያል፡፡ እኔ በመሸለሜ ይበልጥ ደስ ያለኝ.. The International Biographical Center of Cambridge በስነ ሙያ ጥበብ የመጨረሻ ሽልማት የሆነውን Davinci Diamond የደቬንቺ አልማዝ የተባለው ሽልማት ለእኔ ልዩ ነው።

    ከዛ በላይም The United Cultural Convention of the United States of America የተባለው ማዕከል International Peace Prize ልዩ ሽልማትና፣ የክብር የሰላም አምባሳደርነትን ሰጥቶኛል፡፡ Great minds of the 21th century የሚል ሽልማት አግኝቻለሁ፡፡ ይህም ትልቅ ክብር ያለው ነው፡፡ በተቀረ የምጠላው ሽልማት የለኝም፡፡ ቢኖር አልቀበልም ነበር፡፡ ይህች አባባላቸው ፈገግ አድረጋኛለች፡፡

    እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ እንደ ጥበብ ሰውነታቸው በጥንታዊት ኢትዮጵያ ታሪክ፣ ነጻነት፣ ባሕልና ሥልጣኔ እንዲሁም በግዕዝ ቋንቋ፣ በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖታቸው አስተምህሮ፣ ትውፊትና ስርዓት በእጅጉ የሚኮሩ ናቸው፡፡ ለኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖታቸው የነበራቸውን ጥልቅ ፍቅርና ክብር ከገለጹባቸው መካከልም የአራዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የመቅደሱ፣ ግድግዳዎች የሌሎችም በርካታ አድባራት የእሳቸው የጥበብ ትሩፋታቸውን ያረፉባቸው እንደሆን ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት ባሳተሙት የህይወት ታሪካቸው ላይ ሰፍሮ ይገኛል፡፡
           እግዚአብሄር ነፍሳቸውን በገነት ያኑራት


ልጅነትና ትዝታውን ማንሳት ከጀመርኩ የፓስቲ /የጉራጌ ብስኩት/ ለሰባት አመቴ ጥርስ መነቀል አስተዋጽኦ ያደረገውን ከተናገርኩ ለዛችው ፓስቲ ብዬ ሳንቲም ሰርቄ መገረፌን ሳላነሳት ማለፍ አልፈልግም። ቀበሌ ህብረት ሱቅ ግዛ ተብዬ ስላክ ሳንቲም መቀርጨጭን ስለለመድኩ ሁሌ እንድላክ የማላደርገው ጥረት የለም። ተሳክቶ ስላክ ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ ጋር ወጣት አበባ ሻይ ቤትን የሚያውቅ እዛ ያለ ብስኩትን ያውቃል። ታዲያ አንድዋን ቀድሜ አጣጣምኩና ሄድኩ። ህብረት ሱቅ ግን የዛን ቀን ብጥብጥ ስለተነሳ ለልጆች አንሰጥም ተባለ እና መለሱኝ። ከተሰጠኝ ገንዘብ ደሞ አጉድያለሁ።

ነገር መጣ።

ቤት እንደገባሁ ከተላኩበት ብር ላይ ልጆች አንዱን ነጠቁኝ አልኩና የቀረችውን ደበኩዋት። ትንሽ ቆይቼ ወጣሁ እና ብስኩቴን ገዝቼ ሳሻምድ እናቴ ለካ ቀበሌ ህብረት ሱቅ ለመሄድ ወጥታለች። አየችኝ። ዱላው የጠበቀኝ ግን ማታ ነው።

እንደወናፍ ቆዳ ታሸሁ።

ከዛ በሁዋላ አልሰረኩም ማለት አይደለም። ብሰኩት ጠባሹ አረቦ እስከሞተበት ጊዜ ድረስ የዛ ቤት ቋሚ ተሰላፊ ነኝ። ክርስትና ስነሳ እንጃራ ይውጣልህ ተብዬ ሳይሆን የጉራጌ ብስኩት ይውጣልህ ተብዬ ነው መሰል የተመረቅሁት -እወደዋለሁ። አሁንም እወዳለሁ። የምትችሉ ላኩልኝ።

ትላልቅ ሴቶች ህጻናት ወንዶችን እንደሚያባልጉ ያወኩበት አጋጣሚ ደግሞ እነሆ፦ የምስራች ትባላለች ዛሬ..ዛሬ ትዳር ይዛ መውለድዋን አውቃለሁ። እሷ ትረሳው ይሆናል። እኔ ግን አልረሳትም። ጠባሳ የጣለብኝ ነገር አለውና ነው። አስታውሳለሁ ያኔ ገና ስምንት አመቴ ነበር እና ልላክህ ስትለኝ ቤታቸው ገባሁ። እኔ መግባቴን ያየው ዳንኤል እየጠራኝ ተከትሎኝ ገባ። ዳኒ የያኔውን ነገር ታሰታውሳለህ?/ዳኒ ሽኒ ዝተፈጠረ ትርሰኦ አይመስለን/ ቂጣ በዘይት እና በርበሬ የታሸ ለሁለታችን አበላችን። እያጫወተችን ያደረገችውን ነገር ዛሬ እዚህ ቦታ ላይ ባልጽፈውም ለሁላችሁም የሚገባ ነገር ነው። ድርጊቱ አስጠሊታ ስለሆነ ነው የደፈንኩት።

እኔ፣ ባይከዳኝ፣ ዳዊት፣ ተካልኝ፣ታምራት…ሌሎቹም በየጊቢው ያሉትን የኮክ እና የፖም ፍሬዎች በማደን ለራሳችን ደስታ እንፈጥር ነበር። ቅንጨ ጊቢ..አዳነች ጊቢ..የቀበሌው መዋለ ሀጻናት ጊቢ..ናዘሬት ት/ቤት አካባቢ ያሉ የሀብታም ጊቢዎች በየተራ እናዳርሳቸዋለን። ታዲያ አንዴ አዳነች ጊቢ የምንለው ጋር በአጥር ተንጠላጥለን ኮክ ዛፍ ላይ ወጣን። በርካታ ውሻዎች አሉ። እየጮሁ አስቸገሩን አንዱን ትል የበላው ኮክ ቀጠፍኩና ውሻው ላይ እወረውራለሁ ብዬ ካለሁበት ዛፍ ላይ ስቼ ወደኩ።

ውሻው ነከሰኝ።

ህክምና ስሄድ ውሻው ተገድሎ ለምርመራ እንዲመጣ ተባለ። ተደረገ። ለካ በሽተኛ ነው። ሆዴ ላይ 43 መርፌዬን ጠጣሁ። ለኮክ ተብሎ..አይ ልጅነት? ደስ ይላል። ሆዴን ሳይ ሁሌ አስበዋለሁ። ሌላው ደሞ እንደ ልጅ ሆያ ሆዬ መጨፈርም ሆነ ለአበባዮሆሽ አበባ መስጠት እከለከል ነበር። እናቴ ለምን እንደሆነ አላውቅም አትወድም። አንዴ ተደብቄ ስጨፍር ቆየሁና የተካፈልነውን ሳንቲም እንደሌላ ጊዜው በወረቀት ጠቅልዬ ሳልደብቅ ረስቼ ገባሁ። ሳንቲሙ ተገኘብኝና ተደበድቤ ሲበቃ በርበሬ ታጠንኩ። መቼም የደረሰበት ያውቀዋል። አቤት ስቃይ!! ከዛ በሁዋላ ሆያ ሆዬ የሚል ዘፈን እንኩዋን ሰሰማ ያቅለሸልሸኛል። በርበሬዋ ትዝ ትለኛለች።

ብዙውን ጊዜ እናቴን በስራ እረዳታለሁ። አባቴ ከሞተ በሁዋላ እንጀራ ሸጣ ስለሆነ ያሳደገችኝ አዝንላታለሁ። እንጨትና ቅጠል እገዛላታለሁ፤ እህል ገዝቼ አሰፈጫለሁ፤ እንጀራውን ተሸክሜ ያኔ ሺረጋ ሆቴል ይባል የነበረው አራት ኪሎ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት አጠገብ እወስድላታለሁ። ጉሊትም አደርስላታለሁ። በዛ ያለ ጊዜዬን እስዋን ስራ ሳግዛት ደስ ይለኛል። ይህን በስራ ማገዝ እንጀራ መሸጡን እስካስቆምኩዋት ድረስ ዩንቨርስቲ ተማሪ ሆኜ ሁሉ አላቋረጥኩም።
ልጅነት፣ አይናፋርነት እና ፍቅርን በተመለከተ በክፍል 4 እመለስበትና እንሰነባበታለን።
ስላም ለእናንተ፣ ሰላም ለእኔ፣ ሰላም ለፌስ ቡክ ወዳጆቼ፣ ሰላም ለማውቃችሁ፣ ሰላም ለማላውቃችሁ…ሰላም ገና ወደፊት ለማውቃችሁ ሁሉ እንዲሆን እመኛለሁ።
ቸር እንሰንብት
 

ፍል ሁለት
አቦ ተመቸኝ

<<የአንተ አባት ምን አይነት ነው? የእኔ አባት ቀይ ረጅም ሽበታም ነው..የአውራ ጎዳና መኪና ይነዳል ትልቅ የነዳጅ ቦቲ..>> በጥሞና ሲያዳምጠኝ ቆይቶ <<የእኔም አባት አንተ እንደምትለው ነው ብዙ ጊዜ ክፍለ ሀገር ነው።ግን ትላንት ማታ መጥቶ ነበር።..>> አለና የቲቸር ሳያንስ እሱም ጥርጣሬ አርሶ ስለዘራብኝ ቤቴ ልወስደው አሰብኩ። ወደቤት ስወስደው ነገር ተገለብጦ ..ለእሱ እኔ ውጭ የተወለድኩ ወንድሙ ነኝ። እሱ ለእኔ ከውጭ የተወለደ ወንድሜ ነው። አራዳው ፋዘር አራርቆ መውለድ ሲባል ተሸልቅቆ አቀራርቦ አንድ ሰፈር በስድስት ወር ልዩነት ከች አርጎናል። ታላቅነቴን ግን አልተነጠኩም። ብራቮ አባቴ ብኩርናዬን ስላላስነጠከኝ።
በቃ!! ተዋደድን ምንስ ቢሆን ወንድሜ አይደል? የአንዱ ሲገርመኝ እሱስ ታናሽ ወንድምም አለው።አንድ ብቻ የነበረው ታላቅ ወንድሜ ታናሾቹ በረከትንለት።ያኔ ነው አሁንማ ታላቅ ወንድሜ በስደት እያለሁ በሞት ተለየኝ።ድምጻችሁን ዝቅ አድርጋቸሁ ነፍስ ይማር በሉ። ውሎዬ ከጓደኞቼ ይልቅ ከወንድሜ ጋር ሆነ። ከወንደሜም ጋር ሆኜ ተካልኝ ተክሌ፣ታምራት ተክሌ፣ባይከዳኝ..የአባቱን ስም አላውቅም እሱም ሲናገር ሰምቼው አላውቅም። ቅዳሜ..ቅዳሜ መርካቶ እንሄድና ሲኒማ አዲስ ከተማ እንገባለን። በ50 ሳንቲም ሶስት ፊልም እናያለን፤ብዙ ስቃይ እንቅብላለን። ወረፋ ላይ ዱላ እንቀምሳልን፤መሬት ተቀምጠን ሽንት በቂጣችን ስር ሲሽኳለል ይውላል። የሲጋራ ትርኳሽ ሲወረወር ላያችን ካረፈ እንቃጠላለን። ብቻ ሁሉም ያኔ አሁን ያራዳ ልጅ ትሪፕ እንደሚለው ነው።

ፊልሙ አልቆ ስንወጣ ስለፊልሙ አክተሩ እንዲህ አለና እንዲህ ብሎት..አይደለም እንዲህ ነው ያለው/ትርጉም በራሳችን ክርክር ለመንገዳችን/ እየተዳረቅን በሲኒማ ራስ ቴያትር በኩል አቋርጠን ወደ ሰፈር በእግር እንጓዛለን።ሁሌም ከፊልም መልስ በሲኒማ ራስ በኩል የምንሄደው በአምስት ሳንቲም የምትሸጥ ሳንቡሳ ስላለ እሱዋን ለመብላት ነው። የቻልነውን ያህልም እንሰርቃለን። እኔ ግን ከሳንቡሳ ስርቆት ይልቅ አራዳ ጊዮርጊስ ጋር የመጽሐፍ ስርቆት ይቀናኝ ነበር። አነብና መልሼ ሸጨ ለቅዳሜ ፊልሜ እና ለሳንቡሳ አውለዋለሁ። ሳንቡሳ መብላት ውድድርም አለ። ግን የሪኮርዶ ባለቤት ባይከዳኝ ነው።የበላውም መጠን ብረሳውም 20 ይመስለኛል።ካሳነስኩት ግን ይቅርታ ባይኬ…ይህን ስላችሁ አፉን ሸፈፍ ድርጎ <<ኤኔ ሲሜ ባይኬ..>> የሚላት አባባል ታወሰችኝ።

አንድ ጊዜ ቀኑ ቅዳሜ ስለሆነ ተካልኝ እና ወንድሙ ታምራት እናታቸው ለፊልም ሰጥታቸው ሊሄዱ ነው። እኔ፣ባይከዳኝ፣ዳዊት..የምንገባበት የለንም። ቅዳሜ..ቅዳሜ ድሞ ሰፈራችን ያለ ሻፊ የሚባል ከሰል ነጋዴ ንፍሮ አስለምዶናል። ንፍሮው ዝም ብሎ እንዳይመስላችሁ። ዘይት አለው ስንኩርት አለው። ከፈለጋችሁ እናንተ ነፍሮ ወጥ በሉት። እኛ ጥሞን ተጋፍተን ነው አንዳንድ ጭልፋ በሹራባችን ተቀብለን ድጌ ሁላ የምንሄደው። ችግሩ ሻፊ አይሸለቀቅም።

ውይ የእኔ ነገር ንፍሮው ታወሰኝ እና ተዘናጋሁ። እናላችሁ የለመድነውን ንፍሮ እሱ ሊሰጠን አኛም ልነቀበል የሰጪና ተቀባይ ፕሮሰስ ላይ እያለን ገንዘቡን ፊት ለፊት በጣሳ ተቀምጧል። ለባይከደኝ እኔ ሸፈንኩለት አነሳው። ሸኛ ፊልም ገብተን ሻፊ ምን ተረፈኝ ታንቄ እሞታለሁ ብሎ እንደነበር ስሰማ ተጸጸትኩ።

ያኔ አባቴ በህይወት እያለ ነው። ጓደኞቼ ሞጋ/በረባሶ/ የሚባለውን ከጎማ የሚሰራ ጫማ ፊት በር ገበያ እየሄዱ ያሰራሉ። እኔም ቀናሁና አሰራሁ። አቤት የተመታሁት? ለስፖርት ሸራ ጫማ አስገዝቼ አባቴ እናቴን የተቆጣትን አልረሳውም። ሌላ ጊዜ ግን እሱ ሞቶ አድርጌያለሁ። የጉራጌ ብስኩት ነብሴ እስከወጣ እወዳለሁ፡፡ሳንቲም እሰርቅና እገዛለሁ። ከዚህ ጋር የተያያዘ ገጠመኜ ሰባት አመቴ ላይ እንደ ልጅ በወግ ጥርሴ ተነቃንቆ በክር ተጎተቶ አይደለም የወለቀው ፓሰቲ የሚባለውን ደቡልቡል ኳስ የሚመስል የጉራጌ ብስኩት ስገምጥ ስክት ብሎ ቀረ። ጣጣ የለ ፈንጣጣ ውልቅ..ብቻ ብስኩቴን ደም ነካውና ጨርሼ ላጣጥም አልቻልኩም::እሷ ትቆጨኛለች::
ወደ ት/ቤት ገጠመኜ ስመለስ
አንድ ጊዜ ከምንቀርባቸው ውስጥ አንዷ እወድሀለሁ ብላኝ አስታውሳልሁ ሁለት ቀን ከት/ቤት ቀርቻለሁ። ብትስመኝ ኖሮ ከት/ቤት ከናካቴው ሳቋርጥ አይታያችሁም? በጣም አይናፋር ነበርኩ-የዛሬን አያርገውና። ዛሬ እሷ በውጭው አለም ታዋቂ ሞዴሊስት ሆና ፌስቡክ ዳግም አገናኝቶናል። ለነገሩ ከልጅነት ጓደኞቼ መካከል ከጌትሽም፣ከተካልኝም፣ከካሳሁን የሺጥላ ጋርም ፌስቡክ አገናኝቶናል። ተካልኝ ስዊዲን፣ካሳሁን አሜሪካ ከትመዋል።
ወደ ያኔ ወጌ ስመለስ…ያኔ ጓደኛ እንባባላለን እንጂ ምንም የምናውቀው ነገር የለም ነበር። ሳባን የእህቴ ያህል እወዳታለሁ። ዛሬ የልጆች እናት መሆኗን ከመስማት ውጭ የት እንዳለች አላውቅም። ኮኮበ ጽብሃ ከገባን ጊዜ ጀምሮ አላገኘዋትም።
ኮኮበ ጽበሃ ስንማር ለአውቶቡሰ የሚሰጠንን ቀበና ያለችው ሻይ ቤት የጉራጌ ብስኩት እንበላባትና በእግር <<እሰኪ ልወዝወዘው ልወዝወዘው በእግሬን..>> አያንጎራጎርን እናስነካዋለን፡፡ እኔና ጌትሽ ያችን ብስኩት ለመብላት ብቻ ሳይሆን ከሳምሶም ዳቦ ቤት ባለ 20 ሳንቲም ዳቦ ገዝተን ልክ እንደኬክ በወረቅት ይዘን እያጓመጥን መንገዱን እናስነካዋለን::ዳቦ በሙዝ..ሎሚ በከረሜላ..የማይታወሰው አለ ይሆን?

የልጅነት ታሪካችን ቢውራ..ቢወራ የሚያልቅ አይደለም። ቀጣዩን ክፍል ሶስት እመለስበታልሁ። ከደበራቸሁ ግን አስተያየት መስጫው ላይ x ምልክት አስቀምጡ::ከተመቻቸሁ ጭብጨባችሁን አሰሙኝ። ወደፊት እንላለን።
ቸር እንሰንብት
 —
ስለ ልጅነቴ እውነት እውነቱን እናውራ ካልኩ ብዙ ደስ የሚል ባይሆንም በድህነታችን ላይ የተመረኮዘ ጦሽ..ጧ../ባያስቅም ለሞራሌ ስትሉ ሳቁ/ የሚያደርግ ወግ አወጋችሁዋለሁ።ጆሮዎትን ለመስማት አቀባብሉና አበድሩኝ። ተኖረና ተሞተ ያሉት የአለቃ ገ/ሀናን አይነት ህይወት ባይሆንም አኛም ሰፈር ተኖሯል። ምን ይጠበሰ እንዳይሉ..አሳ እንዳልል ተወልጄ ያደከበት ሰፈር አሳ በስህተት ካልሆነ አይገባም። ወንዝ የለ ሀይቅ የለ ከየት ይመጣል?የአሳ ስዕሉን እንኳን ይዞ መገኘት ሰው በማጓጓት እና ምራቅ በማሰዋጥ ወንጀል ያሰከስሳል። 4ኪሎ እና 6 ኪሎ መሀል 5 ኪሎ ብለው ይጠሩታል፡፡ ማን መዘነው እንደትሉኝ ተወለድከበት አልኩ እንጂ መሰረትኩት አላልኩም።

ዘውዱ አዲስ፣ነብዩ ሀይሉ፣ወንደሰን ሰብስቤ፣ ዳንኤል መሀሪ..ተወልጄ ያደኩበት ጊቢ ያሉ ልጆች ናቸው። የረሳሁዋችሁ አትቀየሙ። አንተነህ ፑሲን ግን አልረሳሁም።ዛሬ ዘውዱ አሜሪካን በዲቪ ሰበብ ከትሟል። ነብዩ እና ወንደሰን የት እንዳሉ አላውቅም። የት ናችሁ ከሰማችሁ አለን በሉኝ። ዳንኤል ግን ኤርትራዊ ስለሆነ መውጣቱን አውቃለሁ እንጂ የት አንዳለ ምንም መረጃ የለኝም። ዳንኤል ይህችን መጣጥፍ ካገኘሀት ሰላምታዬን ማድረሴ ብቻ ሳይሆን ዘውትር እንደማስብህ ተረዳ። /ማኸዛይ ኩሉ ጊዜ ይዝክረካ-ሰላም ንዓካ/ ብዙ ትዝታ ያለኝ ግን ከጌታሁን መሳፍንት፣ከተካልኝ ተክሌ፣ከቀìላ ሲሳይ፣ከካሳሁን የሺጥላ፣ሳሙኤል ብስራት..ታዩ…ሽፈራሁ ሀብቴ፣ካሳሁን መኮንን.. ሰይፈ ጌታቸው….ብዙ ነን። ሰይፈ ነፍሱን ይማር በሞት ተለይቶናል።

ከነዚህ ውሰጥ ጌታሁንን ከሁሉም ይበልጥ እወደዋለሁ። ጌትሽ አጭር እና ቀጭን በመሆኑ እንዝርት የሚል ቅêል ስም አለው። እኔ ድንጋይ ስወረውር ባለመሳቴ ጠጅቱ የምትባል የሰፈር ሰው ቦምቤ አለችኝ። ይህች ቅêል ስም ከራሴ መተለቅ ጋር ተያያዘችና ቦምብራስ የምትል ታፔላም ሆና ነበር። ትንንሽ ቦምብ መኖሩን ቢያውቁ ስያሜውን ይፍቁልኝ ነበር። አባቴ ሁሌም ሱፍ ሱሪና ኮት ያሰፋልን ስለነበር ከበተር ፍላይ ከረባት ጋር ስለማደርግ እና ካቆሸሽኩ ሰለምገረፍ ጓደኞቼ ኳስ ሲጫወቱ እኔ ቁጭ ብዬ ስለማይ አካሄዴንም ጨምሮ ባንታለም ሰብስቤ ሚኒስቴር የሚል ቅêል ስም አውጥቶልኛል። ሁለት በሉ።

ከጌታሁን ጋር ትምሀርትም አብረን ነው የምንማረው። አርመን/አሁን ብሔራዊ ቤተመንግስት/ የሚባለው ት/ቤት ነው የተማርነው። ብሩክታይት አሰፋ..አሁን ካናዳ አለች የፒያሳ ሰራተኛ ሰፈር ልጅ፣..ፍሬህይወት አጥላባቸው.. ሳባ ተርዲ የሚባሉ የምንቀርባቸው ልጆች ናቸው። ሳባ ተርዲ ለጌትሽ ሴት ጓደኛው ነበረች። ሁለተኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ የገጠመኝን መዓት ላውጋችሁ ፦ ቲችር አበበ የምንላቸው አንድ እግራቸው አጠር ያለ የክፍል ሀላፊያችን በአንደኛ ሴሚስተር አንደኛ መውጣቴን ገልጠው ሰርተፊኬቴን ሲያቀብሉኝ አሰጨበጨቡልኝ። እግዚአብሔር ይስጣቸውና ያኔ ባያስጨበጭቡልኝ ኖሮ ሳይጨበጨብልኝ እሞት ነበር። ከዛ በሁዋላ ጭብጨባን ዳግም አላገኘሁትም። ለማየት እንኳን ምክር ቤት እሱንም በቴሌቪዥን ነው የማየው። ቀጠሉና ሁለተኛ ለወጣው መስፍን ተ/ሀይማኖት ሰርተፊኬቱን ካቀበሉ በሁዋላ አጫሽ ስለሆኑ ሁሌ ያስላሉ። በሳል የታጀበ ጥያቄ መረቁለት።

<<..ወንድማማቾች ናችሁ?>> ጢም የከበበው አፋቸውን ሞጥሞጥ አድርገው ሲያፈጡብኝ ፈራሁ እንጂ <<..በአማርኛ ክፍለ ጊዜ ላይ ያስተማሩንን አዛምድ እኛ ላይ ሊሞክሩት ነው እንዴ?እኛ ቤተ ሙከራ ያለ አይጥ ነን >> ልላቸው አሰብኩ። ምን ያደርጋል ስለምፈራ ፍርሃቴን ተሸክሜ ቀረሁ። እሳቸው ግን ድፍረት አገኙና በአንካሳ እግራቸው ከፍ ዝቅ እያሉበት ብላክቦርዱ ጋር ቆመው እያስተዋሉን <<..ደሞ በመልክም ትመሳሰላላቸሁ..>> ሲሉ ሽርደዳ የሚመስል ቃላት መረቁልን። አሁን የማላስታውሰው ስድብ በውስጤ ሰደብኳቸው። ለነገሩ እንኳን አላስታወስኩት የስድብ ጥሩ የለው። ነብሳቸው ይማረውና በመጥፎ ድርጊት ስለሚታሙ በሱው የሰደበኩዋቸው መሰለኝ። ሁሌም አውቶቡስ ላይ ከሴቶች ሁዋላ ቆመው ይተሻሹና..አንድ ጊዜ አንድ ሴትዬ እንትናቸውን ይዛ ስትጎትታቸው በዓይኔ አይቻለሁ። ከዚህ የራቀ አልሰደበኩዋቸውም። ከፈለጉ ራሳቸው አያስታውሱ እኔ ምን አቀጣቀጠን? አባቴን ዋልጌ አድርገው ከእናቴ ውጭ እንደወለደ ለምን አሰቡ ብዬ ነው መሳደቤ።

ከውስጥ ኔትወርካችን ተገናኝቶ ይሁን ተጠላልፎ ድንገት ሳናውቀው እኩል <<አይደለንም>> አልናቸው። አልተዋጠላቸውም። እንኳን ሊዋጥላቸው ከጆሯቸውም የገባ ሳይመስሉ << ለማንኛውም ተጠያየቁ>> የሚል ማሳሰቢያ ቢጤ ወርውረው ሰርተፊኬት ማደል ቀጠሉ። አጠገቤ የተቀመጠው አላዛር ነጋሽን ቢሉ የሁለታችንም ራሰ ጠበደል በመሆኑ ሊያመሳስሉን ይችላሉ የሚል እሳቤ ከማሰቢያዬ ውስጥ ስንቅር አለ። እስክንወጣ ተነቆራጥጨ ጠበኩ። ስንወጣ መስፍንን በጥያቄ አጣደፍኩት።
<<የአንተ አባት ምን አይነት ነው? የእኔ አባት ቀይ ረጅም ሽበታም ነው..የአውራ ጎዳና መኪና ይነዳል ትልቅ የነዳጅ ቦቲ..>> በጥሞና ሲያዳምጠኝ ቆይቶ <<የእኔም አባት አንተ እንደምትለው ነው ብዙ ጊዜ ክፍለ ሀገር ነው።ግን ትላንት ማታ መጥቶ ነበር።..>> አለና የቲቸር ሳያንስ እሱም ጥርጣሬ አርሶ ስለዘራብኝ ቤቴ ልወስደው አሰብኩ።

የልጅነት ታሪካችን ቢውራ..ቢወራ የሚያልቅ አይደለም። ቀጣዩን ሳምንት እመለስበታልሁ። ከደበራቸሁ ግን ገትረው በሉኝ።እገትረውና ቴዘር ትጫወቱብታላችሁ። ከተመቻቸሁ ጭብጨባችሁን አሰሙኝ። ወደፊት እንላለን።
ቸር እንሰንብት