Saturday, February 23, 2013

ያረቢ ኑ ባሲ!!!..ያረቢ ኑ ባሲ... ኢትዮጵያዊያንን ከነ ህይወታቸው እየቀበሩ መቅጣት..


ያረቢ ኑ ባሲ!!!..ያረቢ ኑ ባሲ...
ኢትዮጵያዊያንን ከነ ህይወታቸው እየቀበሩ መቅጣት..
በግሩም ተ/ሀይማኖት
    አንድ ወዳጄ ከወዳጅም የሞያ ጓደኛዬ የሆነው ጋዜጠኛ ግርማ እንድሪያስ የእህቱ ልጅ በባህር ወደ የመን ሲመጣ መያዙን ነገረኝ፡፡ ትንሽ ቆየ እና እህቱ ማለት የተያዘው ልጅ እናት ደወለች፡፡ እናት ጉዷን አላወቀችም፡፡ የመን መጥታ ችግሩን አላየች በምን ትወቅ? ደግሞስ ችግሩን ለማወቅ የግድ የመን መምጣት አለባት እንዴ? የለባትም፡፡ በየጊዜው ይጻፋል፡፡ ይነበባል፡፡ ግን ማንበብና ማስተዋል አንድ አይደለም፡፡ ልጇ ያን ነው የሆነው፡፡ ልጅ በሚውልበት እናት አትውል፡፡ በዛ ያለ ሰው እየሰማ እያየ ነው መልሶ በባህር የሚመጣው፡፡ ልጇ ደላሎች ጋር እንዳለና ወደ ሳዑዲያ ሊገባ እንደሚፈልግ ደላሎቹ ለማድረስ 3500 የሳዑዲ ሪያል መጠየቃቸውን ነገረችኝ፡፡
    ወዲያው የገባኝን ያህል ገባኝ፡፡ የተባለውን ገንዘብ ብትልክላቸው እንደማያደርሱት አውቃለሁ፡፡ በዛ ላይ ልጁ ገንዘብ የሚልክልህ ሰው ስልክ ቁጥር እያሉ ሲያዋክቡት፤ ሲያሰቃዩት እናቱ ጋር አስደወለ፡፡ ስልኩ ስላልተነሳ ግርማ እንድሪያስ ጋር አውሮፓ ደውሏል፡፡ አውሮፓና አሜሪካ ከተደወለ ደግሞ እንዲህ በዋዛ አይፋቱም፡፡ ለግርማም ሆነ ለእህቱ አጓጓዥ ደላሎች ጋር ሳይሆን ያለው አፋኞች መሆናቸውን ብናገር አረ አይደለም ደላሎች ናቸው ተባልኩኝ፡፡ ክርክሩን በዝምታ አልፌ ልጁ እኔ ወደ አለሁበት ሰነዓ እንዲመጣ በተሰጠኝ ስልክ ቁጥር ደወልኩ፡፡
   ‹‹እህ ማነህ ጃል..ምን ኮነክ ነው? ማንን ፈለክ..›› የሚል ገጠርኛ ቃና ያለው አማርኛ ተናጋሪ አወራኝ፡፡ ልጁን እንዲያቀርብልኝ ስሙን ነገርኩት፡፡ ማውራት ያለብኝን ያህል አወራሁ፡፡ አከል አድርጌ ሳዑዲ ሳይሆን የሚሄደው ወደ ሰነዓ እንዲመጣ ምን ያህል እንደሚጠይቁ ተነጋገርኩ፡፡ ሁኔታዎችን እኔ በማውቀው መንገድ ለማስኬድ ከአፋኞቹ ጋር ተደራደርኩ፡፡ 1500 የሳዑዲ ሪያል እንድልክ ነው የተስማማነው፡፡ የተባለው ገንዘብ ተላከልኝና ላኩኝ፡፡ ልጁን ለመልቀቅ ማንገራገራቸው ለምን እንደሆነ ስለማውቅ ታግሼ እጠብቃለሁ፡፡ ገንዘቡ ከተላከላቸው እንደማይደበድቡት በተደጋጋሚ በሰማሁት መረጃ አውቃለሁ፡፡ ወዲያው ባይሆንም አንገራግረው ከቀናት በኋላ ለቀውታል ይደውልልሀል ተባልኩ፡፡
   ሁለት ሶስት ቀን ምንም የለም፡፡ የሚያደርሱት ሀረጥ የተባለው ቦታ ድረስ ነው፡፡ ካለሁበት ሰነዓ 750 ኪሎ ሜትር አካባቢ ስለሚርቅ ይህን ያህል ርቀት ብቻውን ከመጣ ድጋሚ በሌሎች እንዳይያዝ እና ለእነሱ ስለተከፈላቸው ለሌላ እንዳያሳልፉት ተነጋግረን መክፈል ያለብኝን መሰዋእትነት ከፍዬ ለማምጣት ጉዞ ሀረጥ ወደሚባለው ቦታ አደረግሁ፡፡ ይህ ቦታ በግሩፕ የተደረጁ መሳሪያ የታጠቁ ሰዎች ኢትዮጵያዊያኑን ስደተኞች ባህር ሲሻገሩ አፍነው ብር አስልኩ ብለው የሚያሰቃዩበት ቦታ እንደሆነ በተደጋጋሚ ዘግቤያለሁ፡፡ ወገኖቻችን ወደሚሰቀዩበት ቦታ ሀሙስ እለት(የካቲት 7 ቀን) እንደሚፈልጉኝ እያወኩ ስለሆነ የምሄደው ካልድ ከሚባል ጓደኛዬ ጋር ነው አካሄዴ፡፡ የእናትንም ሆነ የጓደኛዬን ጭንቀት ስላወኩ ስራዬን ትቼ፣ ካለችኝ ሳንቲም ላይ ቀናንሼ፣ ራሴን ለውጬ..ነው ችግር ቢገጥመኝ ብዬ ካልድን አስከትዬ ጉዞዬን የጀመርኩት፡፡ አሳዛኙ ነገር እኔ እናት ተግባብተን አልተግባባንም፡፡ ወይም አልተማመንም መሰለኝ፡፡ ያለምን ጥቅም ይህን ያህል መሰዋዕትነት ለመክፈል መዘጋጀቴ፣ ትንስፖር ማውጣቴ፣ ስራዬን ጥዮ መሄዴ..ምን ቢጠቀቀም ነው ያሰኝ ይችላል፡፡ ከዚህ በፊት ብዛ ያለ ሰው ጥቅምህ ምንድን ነው? የሚሉኝ ስላሉ አይገርመኝም፡፡ ግን ከህሊና እርካታን መን አይነት ጥቅም እንለካው ይሆን? የጀመርኩት ጉዞ ትዕዝ የሚባለው የየመን ሶስተኛ ከተማ ላይ ተገደበ፡፡
     ትዕዝ ላይ ያገኘኋቸው ሰዎችና የሰጡኝ መረጃ ግን ኢትዮጵያዊያን ምን እየጠበቅን ነው? ከዚህ በላይ ጭካኔስ በአለማችን ላይ ይኖር ይሆን? ያሰኛል፡፡ ትዕዝ የሚባለው ቦታ ተቅብሎ ያስተናገደን ልጅ ጋር የመጣ አንድ እንግዳ..ውይ እንግዳ አልኩ እንዴ? እኛው አስጠርተነው መሆኑን ዘነጋሁ፡፡ ታክሲ ስላለው እና ወደዛ መንገዱን ያውቃል ስለተባለ ያስጠራነው እኛ ነን፡፡ በጫዎታ ጫዎታ ስላየው እና ስለሚደረገው ያወጋን በስንተኛው ዙር ወግ ላይ እንደሆን በማላስታውሰው ጊዜ ‹‹..እነዚህ የሚያግቱት ጋር እኮ ሰው በቁሙ እየቀበሩ ማሰቃየት ጀምረዋል፡፡…›› ሰውነቴን ውርር አደረገኝ፡፡ እስካሁን ያልሰማሁት በመሆኑ ደነገጥኩኝ፡፡ በእርግጥ በአንድ ወቅት ወደ እዛ ስሄድ የሞተ ኢትዮጵያዊ የሚቀብሩበትን ቦታ አይቼዋለሁ፡፡ በጣም በጣም ሰፊ ነው፡፡ ግን እንዲህ በህይወት ያለ ሰው ይቀብራሉ ሲባል አልሰማሁም፡፡
  ‹‹ቅብር!..ቅብር?…በምን አወክ አንተ አይተሀል?›› ስል ጠየኩት፡፡ አላንገራገረም፡፡ አብሮት የመጣውን ልጅ እሱ ከባህር እንደመጣ ይዘውት ከእነሱ ጋር ለመስራ ሞክሮ ነበር፡፡ አሁንም ሄድ መለስ ይላል፡፡ አለና ልንቁስ ያለ ልጅ አሳየኝ፡፡ ወገኑን ከሚያሰቃዩ ጋር በመስራቱ ከሱ ጋር ማውራት ተጠየፍኩት፡፡ በጠላትኛ አየሁት ግን የሚሰጠኝን መረጃ እፈልገዋልሁ እና ሞባይል ስልኬን የተደወለልኝ አስመስዬ ነካካሁና ሪከርድ የሚለው ላይ አደረኩኝ፡፡ እንዲነግረኝ ጠየኩትም፡፡
  ‹‹አዎ! ግን ያየሁት ልጁ ራሱን ነው፡፡ የተቀበረውን፡፡››
  ‹‹ከተቀበረ ከየት አየኸው?››
  ‹‹እስከ አንገቱ ድረስ ቀብረውት አሰቃይተውት ከዚህ ከወገቡ በታች አልታዝህ ብሎት እየተንፏቀቀ ህክምና እንዲያገኝ ሀረጥ ካምፕ ሲገባ አይቻለሁ፡፡›› አለኝ፡፡ አላናገርከውም? ብዬ ለየጠኩት የሰጠኝ መልስ ግን በጣም ሰቅጣጭ ነበር፡፡ ልጁ በተፈጥው መስማት የተሳነው ስለሆነ እንዴት ላውራው አለኝ፡፡ ከዛ ወዲህ ወይም ከዛ በፊት እንዲህ አይነትነ ነገር አይቶ ሰምቶ እንደሆነ ስጠይቀው ከዛ በኋላማ እዚሁ ትዕዝ ውስጥ ትላንት የገባ ልጅ አለ፡፡ እዚህ ማር መሸጫ መደብሩ ጋር መኪና ከሚያጥቡ ልጆች ጋር አሁን ስመጣ ራሱ አይቼዋለሁ፡፡ ቀብረውት አሰቃይተውት አንድ አይኑን አጥፍተው ለቀቁት፡፡
አስቡት አይኑን አጥፍተውት ሲበል የሚሰማውን ስሜት አስቡት…
   ጫዎታውን አቋርጦ መሄዱ ተሰማኝ እንጂ የተባለው ቦታ ሄጄ ልጁን ማናገር ፈለኩ፡፡ ቀልቤ ፈጽሞ ከእነሱ ዘንድ አልነበረምና ካልድን ጠቅሼው መጣን ብለን ወጣን፡፡ ልጁን አፈላልጌ  ለማግኘት ቢከብድም ከብዙ ድካም በኋላ አገኘነው፡፡ ሊያወራልን ፍቃደኛ አልሆነም፡፡ እንዲያወራልን በተደጋጋሚ ያደረኩት ሙከራ ስላልተሳካ ተቃራኒውን አውርቼ ሀቁን እንዲነግረኝ ማድረግ አማራጭ ነውና አደረኩት፡፡ ‹‹እንዴት አይንህን ሊያጠፉህ ቻሉ? ገንዘብ እንድታስልክ ሲሉ በጣም ይንከባከባሉ ሲባል ነው የሰማሁት፡፡ 
    ‹‹ምንድን ነው የምታወራው? የምታወራውን ታውቃለህ? እብድ..እነሱ ናቸው የሚንከባከቡት?..›› ሲል ጀመረ፡፡ እኔም የምፈልገው ይሄን ነውና ስድቤን ጠጥቼ ለመስማት ጆሮዬን በተጠንቀቅ አደረኩ፡፡ ቀጠለ…‹‹..እንኳን ሊንከባከቡህ ገና ጊቢው ውስጥ ስትገባ ነው ዱላው የሚጀምረው፡፡ አስደውሎ የሚያስልክበት ቦታ ያለው አስደወለ፡፡ እኔ ደግሞ ማንም የለኝም፡፡ ቡዙ ተደበደብኩ፡፡ ከየትም አምጥቼ አልሰጠኋቸውም፡፡ እይ!..ይንከባከባሉ ያልካቸው ናቸው ያቃጠሉኝ፡፡
    ደረቱ ላይ በሲጋራ ያቃጠሉትን አሳየን፡፡ የበለጠ እንዲጨምርልኝ ፈልጌ ‹‹ለመጀመሪያ ጊዜ ካንተ ሰማሁ፣ አየሁ..›› አልኩት፡፡
    ‹‹ሂድና ሀረጥ እይ ምን ታደርቀኛለህ? ይሄን ታዲያ ራሴ ነኝ ያጠፋሁት? ምን ማለት ፈልገህ ነው?..›› አለና አይኑን አሳየኝ፡፡ ‹‹እንዴ ይህን እነሱ ናቸው እንዲህ ያደረጉኝ እንዳትል?..›› ሰምቼ ቢሆንም ፍለጋ የጀመርኩት እንዳላወቀ ሆንኩኝ፡፡ ‹‹እየነገርኩህ? ገንዘብ የሚልክ ዘመድ የለኝም፡፡ በሲጋራ አቃጠሉኝ፡፡ መቀመጫዬ ላይ ላይተር ለኩሰው አቃጠሉኝ፡፡ የሌለኝን ዘመድ ከየት ላምጣ ጉድጓድ ቆፍር ብለው አስቆፈሩኝ፡፡ እስከ አንገቴ ድረስ ቀበሩኝ፡፡ እኔስ ተርፌያለሁ ዝም ብለው ሙሉ ለሙሉ የቀበሯቸው አንድ ሴት እና ሶስት ወንዶች ልጆችን አያቻለሁ፡፡

    እኔን አንገቴ ድረስ ቀብረውኝ እነሱ ጫታቸውን እየቃሙ በእኔ ስቃይ ይዝናናሉ፡፡ በመጨረሻም ለ22 ቀን አስቃይተውኝ እንደነገ ሊለቁይ እንደዛሬ የሀይላንድ ውሀ ላስቲኩን ክዳኑን ከፈተው እና አፉን አይኔ ላይ አደረገው፡፡ በቀዳዳው እይ አይንህን ግለጽ አለኝ፡፡ ያው ያዘዙህን ማድረግ ግዴታ ነው ገለጥኩ፡፡ በቂጡ በኩል በሀይል ሲመታው ራስን ስቼ ወደኩ፡፡ ምን ያህል ጊዜ እንደቆየሁ እንጃ ፌቴ ሁሉ ደም ለብሷል፡፡ እንዲሁ አሞኝ ዋልኩ፡፡ አይኔ ግን መውጣቱን ያወኩት ስነቃ ነው፡፡ በማግስቱ ሲለቁኝ መሄድ በሙሉ አልችልም ነበር፡፡  የወጣው አይኔ የሀይላንዱ እቃ ውስጥ እንደተቀመጠ ከድኖት ‹‹አላስልክም ባልከው ብር ታከምበት..›› ብሎ ሰጠኝ፡፡
    ምን እንደተሰማኝ አላውቅም፡፡ የነበረኝን ስሜት አሁን መናገር አልችልም፡፡ አጥወልውሎኝ የምወድቅ መሰለኝ እና ካልድን ለገሰን ለመያዝ ዞር ስል በሁለት እጁ ራሱን ይዞ ያለቅሳል፡፡ እኔ ግን ማልቀሱም ሆነ ማሰቡ አልሆነልኝም፡፡ እዚህ ጋር በአንድ ወቅት ሶማሊያ እያለሁ የሚሰቃዩትን አይቼ የጻፍኳትን ግጥም ዳግም ብጠቀማት ወደድኩ….
  ዋ!! ማንባት ብችልማ
  ያሉትን ይበሉ ብልማ
  ጥንድ..ጥንዱን አንዠቅዥቄ
  ህቅ!!! ባልኩ ተንሰቅስቄ
  ሀዘኔ በወጣ በታወቀ ለሰው
  አምቄ ከማልመሰምሰው
  እርዱኝ…እርዱኝ እባካችሁ
  ትርፍ እንባ ያለችሁ
   አልቅሱልኝ ለእኔ አሮ ሞተ ብላችሁ….ከማረርም በላይ ሆኖብኛል፡፡
 አፌን ሁሉ ደም ደም አለኝ፡፡ ምሳ እንብላ ብለውም እሺ አላለም፡፡ አሁን ምን አሰብክ? ወደ ሰነዓ ከሆነ የምትሄደው አብረን እንሄዳለን አልኩት፡፡ ረድዓ የሚባለው ቦታ ሄዶ ባለ እርሻ ሰዎች ጋር ተቀጥሮ ትንሽ መስራትና ወደ ሳዑዲ አረቢያ መሄድ እንደሚፈልግ ነገረኝ፡፡ እንዴት ረድዓን የምትባለውን ቦታ እና እዛ ስራ እንዳለ እንደወቀ ካልድ ጠየቀው፡፡ ከዚህ በፊት እንደመጣና ሳዑዲ አንድ አመት ቆይቶ ተይዞ ድጋሚ እንደተመለሰ ነገረን፡፡ ወዳለው ቦታ ለመሄጃ ከዛሬው ጋር ሁለት ቀን መኪና እንዳጠበ ነግሮን ሳንቲም ከቻልን እንድንሰጠው ጠየቀን፡፡
   ይሄ በባህር የሚደረግ ጉዞ ስቃዩን እለት ከእለት እየጨመረ መምጣቱ ብቻ ሳይሆን አፋኞቹን ለማስቆም ምንም አይነት ጥረት አለመደረጉ አሳሳቢ ነው፡፡ እነሱም በማን አለብኝነት ጭካኔያቸውን እየጨመሩ የፈለጋቸውን እያደረጉ ነው፡፡ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ አካባቢ ከየመናዊያን ጋር በጥምረትም ሆነ በተናጠል ሰውን ወደ ሳዑዲያ የሚያጓጉዙትን ኢትዮጵያዊ ደላሎች ለማስያዝ አዲስ እንቅስቃሴ እንደተጀመረ ተሰምቷል፡፡
   በ2012 ከ85000 በላይ ኢትዮጵያዊያን በባህር ተሻግረው ወደ የመን እንደገቡ ብሎም ግማሹ ወደ ሳዑዲ አረቢያ እንደተጓዙ አለም አቀፉ የስደተኞች ጽ/ቤት IOM የሚባለው ድርጅት መግለጹ ይታወቃል፡፡ እኔም በተደጋጋሚ ይህንን መግለጫ ጠቅሻለሁ፡፡ አብዛኛውም ከወሎ፣ ከአርሲ፣ ከሀረር እና ባሌ አካባቢ ነው የሚሰደዱት፡፡ ይህን ያህል ኢትዮጵያዊ የሚሰደደው በኑሮ ችግር ምክንያት መሆኑ እሙን ነው፡፡ ለዚሁም እማኙ በወሎ ቦረና ወረዳ መካነሰላም የሚባል አነስተኛ ከተማ ውስጥ ከዋለልኝ መኮንን ትምህርት ቤት ከ9 እና 10ኛ ክፍል ብቻ በዚህ አመት ከ500 ተማሪዎች በላይ አቋርጠው ስደት ወተዋል፡፡ ካቋረጡት እና ስደት ከወጡት ውስጥ አብዛኛዎቹ ቤተሰቦቻቸው በዝቅተኛ ኑሮ ላይ ያሉ ናቸው፡፡ በኩር የተባለው የአማራ ክልል ጋዜጣ በዚህ ወር እትሙ ያሰፈረውን እንደቀልድ የማይታይ ነው፡፡ የፍልሰታችን አስፈሪ ሂደት ወዴት እየተጓዝን እንደሆነ ያመላክታል፡፡
    ሰዒድ ሙሳ አህመድ የተባለ ወዳጄ ከገጠር ትምህርት ቤቶች በየአመቱ ትምህርት የሚያቋርጠው ተማሪ ብዛት አስደንጋጭ መሆኑን ጽፎልኛል፡፡ በጽሁፉ ላይ ሀይ ግሩም በደቡብ ወሎ ምዕራባዊ ዞን በረና ዋለልኝ መኮንን ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ከ9-10 ካለው ክፍል ብቻ በ2004 ከ500 በላይ ተማሪዎች እንዳቋረጡ ታውቋል፡፡  ይሄው ወዳጄ ከጻፈልኝ በተጨማሪ አያይዞ የላከልኝ በኩር ጋዜጣ ላይ ከወረዳው አስተዳደር በተገኘው መረጃ በ2004 በአጠቃላይ 4000 በላይ እንዳቋረጡ ዘግቧል፡፡ ወሎ አርባ ወረዳዎች ስላሏት ስሌቱን 40X400 ማባዛት ነው፡፡160.000 አካባቢ መሆኑ ነው፡፡ ጋዜጣው ትምህርት የሚያቋርጡበት ምክንያት መንግስትን የያዘው ብልሹ ፖለቲካ እንደሆነ ላለመጥቀስ ወላጆች ልጆቻቸውን ወደ አረብ ሀገር ልከው ገንዘብ የማግኘት ፍላጎታቸው ማየል ነው ሲል ዘግቧል፡፡
     የዋለልኝ መኮንን ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ርዕሰ መምህር አቶ ተስፋው ደመቀ ከአምናው ችግር ዘንድሮም የባሰ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ጋዜጣውን ማየት ይቻላል፡፡