Thursday, January 17, 2013

ይድረስ የመን ላላችሁት የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች









     
ሀበሻ በየመን ክፍል 10
ይድረስ የመን ላላችሁት የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች
ሀገር መግባት ለሚፈልጉ መርዳት ከቻላችሁ…
በግሩም ተ/ሀይማኖት
የመን የተቀመጠ ሰው ወገን ወገኑን ሲባላ ወገን ወገኑን ሲረዳ ያያል፡፡ በሁለቱም መንገድ ተሰለፉም አሉ፡፡ አንዱን ይበላሉ አንዱን ይረዳሉ፡፡ ከሁሉ ከሁሉ ግን ወገን ወገኑን ማረዱ፣ ለማጥፋት መቸኮሉ የሚያሳዝን ነው፡፡ በተለይ ለኢትዮጵያዊያን ይሰራል የተባለው ስሙን ኤምባሲ ያደረገው የሆድ አደር ጥርቅም ግሩፕ ወገኑን ሲገፋ እና ሲደፋ ማየት አስጠሊታ ነገር ነው፡፡ ይህን ያልኩበት ምክንያት አለኝ፡፡ ይድረስ ስል ‹‹አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት..›› የሚሉትን አባባል ረስቼው አይደለም፡፡ ወይም ህሊናችሁን በሆዳችሁ እንደ ቀየራችሁት ዘንግቼም አይደለም፡፡ የህዝቡ ስቃይ ከእኔ የበለጠ እናንተ ጋር መረጃው እንዳለ አውቃለሁ፡፡ እስካሁን ባየሁት ለኢትዮጵያዊያን ከኤምባሲው ይልቅ የየመን መንግስት ያደረገው የተሻለ በጣም የተሻለ ነው፡፡ ከሳዑዲያ ታፍሰው ወደ የመን ድንበር የተጣሉ ከ30 የሚበልጡ ኢትዮጵያዊያን በስቃይ የየመን ዋና ከተማ ሰነዓ ገቡ፡፡

ኢትዮጵያ ኮሚኒቲ በር ላይ ሀገራችን አስገቡን በማለት ከሁለት ወር በላይ ሜዳ ላይ የሚተኙትን ልጆች እየአንዳንዳችሁ 250 ዶላር ካልከፈላችሁ ወደ ሀገር አትገቡም ተባሉ፡፡ እንዲያውም ኮሚኒቲው በየመን ወታደሮች አሳፍሶ ከከተማ ውጭ ጥሏቸዋል፡፡ ተመልሰው መጥተው አሁንም በር ላይ መተኛት ጀመሩ፡፡ ‹‹ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጠይቀን ነበር እየአንዳንዳቸው 250ዶላር ይክፈሉ ተብሏል..›› እንዳላችኋቸው ሲነግሩኝ ደነገጥኩ፡፡ ለራሳችሁ የምትበሉት እንደሆነ ኮሚኒቲውን የሚመሩት ሰዎች ከምን ተነስተው የት እንደደረሱ ህዝቡ አያውቅ ይሆን? ከሳዑዲያ ገብተው ወደ ሀገር የሚገቡትን የጉዞ ትኬት እኛ እንቆርጣለን ትላላችሁ፡፡ ከየቲኬቱ የሚያዘውን ኮሚሽን መጠን ህዝቡ አያውቅም ብላችሁ ነው? መንግስትን ከህዝብ ማቀራረብ ሲገባችሁ ማራራቁን በርትታችሁ እየሰራችሁ ነው፡፡ ቱ!...ቱ…ካይን ያውጣችሁ፡፡

የእነዚህ ልጆች ኢትዮጵያዊነታቸው የሚለካው በ250 ዶላር ነው? ሌላው ቀርቶ ማሪብ አካባቢ መኪና የገጨውን ልጅ እንደዚህ ቆስሎ ወር ሙሉ አስጠብቃችሁ 50000 የየመን ሪያል ወይም ሁለት መቶ ሀምሳ ዶላር ካልከፈልክ ወደ ሀገር አትገባም ማለታችሁ እውነት ሰብዓዊነት አላችሁ? ከነ ቁስሉ ከፈለክ ዞረህ አዋጡልኝ ብለህ ወገኖችህን ለምን /ምጽዋት/ጠይቅ ማለትስ ምን ማለት ነው? ያሳፍራል፡፡ የእናንተ ወገናዊነት፣ የእናንተ ተቆርቋሪነት ምኑ ጋር ነው? እስካሁን አላየንም፡፡

ሳዑዲ ውስጥ ህግ-ወጥ ሆነው የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ህጋዊ ሆነው ለመመለስ ይፈልጋሉ፡፡ እዛ ተይዘው ወደ ሀገር ሲመለሱ የአይን አሻራ ተነስተው ለአምስት አመት መመለስ የማይችሉ ስለሆነ አማራጭ በየመን ወደ ኢትዮጵያ ያደርጋሉ፡፡ ከሳዑዲያ ወደ የመን እየገቡ ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ የሚሞክሩትን ዜጎች የየመን መንግስት በነጻ ያስተናግዳቸው ነበር፡፡ ኢትዮጵያ ኤምባሲና ኮሚኒቲ ብላችሁ በሁለት ከፍላችሁ በሰበብ አስባቡ ስትበሏቸው ኤምባሲው ወገኖቹን ከበላ እኛስ ለምን ዝም እንላለን ብለው አሁን በቅርቡ እነሱም ክፍያ ጀመሩ፡፡ በልታችሁ ለበይ የምትሰጡት ዜጋችሁ መሆኑን ረሳችሁት እንዴ? እዚህ ሀረጥ፣ ባብል መንደብ እና ሞካ አካባቢ በባህር የሚገቡት ኢትዮጵያዊያን ላይ ኢ- ሰብዓዊ ድርጊት ሲፈጸም አላውቃችሁ ይሆን? በየቀኑ እንዲህ አይነት ጉዳት ደረሰብን ብለው የሚመጡትን በር ላይ ሆናችሁ ከማባረር ‹‹እህ…›› ብላችሁ ብትሰሙ ምናለበት፡፡

እርግጥ ነው በክህደት የተካናችሁ እንደሆናችሁ አላየንም አልሰማንም እንደምትሉ አምናለሁ፡፡ እውነት እውነት እላችኋለሁ እናንተ ጋር መጥተው የመለሳችኋቸውን እስከ ሰጣችኋቸው መልስ ማቅረብ እችላልሁ፡፡ የደላላዎቹን ማንነትም አናውቅም ብላችሁ ከዋሻችሁ ይሁንላችሁ፡፡ ወጣ በሉና ህዝቡን ጠይቁ…ቢሮ ታቅፎ በጎሳ ሸንትሮ ወሬ መሰለቅ ልማት አይደለም፡፡ ልማታዊው መንግስታችን ወሬንም በልማት መድቦት ይሆን? እኔ የማውቀውን ሁሉ ከህዝቡ ነው ያገኘሁት፡፡……. ለነገሩ ወሬና ውሸት ተግባራችሁ ላይ ጎልቶ የወጣ ለመሆኑ ጠ/ሚኒስትሩ የሞቱ ጊዜ ኤምባሲ ልታስለቅሱት ለጠራችሁት ሰው አበበ ገላውን አስገደልነው ሌሎቹም…ብላችሁ የተንጦረጦራችሁትን /ያወራችሁት/ በሞባይል ተቀርጾ ሰምቻለሁ፡፡ ታሳፍራላችሁ…ማፈሪያዎች ብዬ ግን አላናድዳችሁም፡፡ ድርጊታችሁን ለምን እደግመዋለሁ፡፡

ሌላው ቀርቶ የመኖሪያ ፍቃድ እዳ (ቀራማ) ያለባቸውን እናስቀንሳለን ብላችሁ ላባቸውን ጠብ አድርገው የሰሩበትን ገንዘብ ለመብላት ዘዴ ቀየሳችሁ፡፡ ተመዝገቡ ብላችሁ የአማራ ልማት፣ የትግራይ ልማት ማህበር…አባል ካልሆናችሁ አገልግሎት አንሰጥም እያላችሁ ከ2600-3000 የየመን ሪያል ከእያንዳንዱ በመብላት የጅብ ቆዳነታችሁን አስመሰከራችሁ፡፡ ‹‹የጅብ ቆዳ ቅኝቱ እንብላው እንብላው…›› ሲባል አልሰማችሁ ይሆን ኢትዮጵያዊነታችሁን ከረሳችሁት ማለቴ ነው፡፡

በኮንትራት የሚመጡትን ዜጎች ችግር ሲደርስባቸው ‹‹ለገረድ አልመጣንም..›› በማለት አሳልፋችሁ ለአሰቃዮች ከሰጣችሁ ምኑን ኤምባሲ ናችሁ? በስደት በየሰዉ ቤት ስቃይ አይተው ከሚያመጡት ላይ ለመንጠቅ በየጊዜው መላ መለዋወጣችሁ ዘራፊነቱን መቀያየራችሁ ለወገን ማሰብ ነው? አሁንም ጎዳና ላይ የወደቁትን ከ30 በላይ ኢትዮጵያዊያን መፍትሄ ልትፈልጉላቸው ይገባል፡፡ ሌሎች ወገኖችም ቢሆን ቢያንስ ሀረጥ የሚባለው የቀይ መስቀል ካምፕ ድረስ የሚጓዙበትን ያህል መርዳት የምትችሉ ተባበሩ፡፡ በተጨማር የመኪና አደጋ ደርሶበት ከወር በላይ ኮሚኒቲው በር ላይ ወድቆ ወደ ሀገር መመለሻ ላጣው ልጅ ሀገሩ መግቢያ ማገዝ የምትችሉ ከታች ባለው አድራሻ ደውሉልኝ፡፡
009677356401b or 00967713545566