Saturday, October 6, 2012

ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በአረብ ሀገር

  
ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በአረብ ሀገር
ክፍል 6ኛ
   እንደጅብ ቆዳ ቅኝቱ ሁሉ ‹‹እንብላው..እንብላው..›› ብቻ ሆንብኝ
በግሩም ተ/ሀይማኖት

   ሰላም ወዳጆቼ ነዛር የተባለ ወዳጄ የሰጠው አስተያየት ላይ ...ወዳጄ ግሩም ባለህበት ቦታ ሰላምታዬ ይድረስ፡፡ /እፍኝ ሙሉ ስላምታህ ደርሶኛል/ በጽሁፍህ መግቢያ የገለጽከውን የኩዌት የሞተውን ልጅ ሀዘን ጨምሮ እስከመጨረሻው ያለው ጽሁፍ በጣም ያሳዝናል፡፡ በእርግጥ የኩዌቱ ልጅ ሞት የቅርብ ጊዜ ሀዘን ነው፡፡ እኛም እስከመጨረሻው የማንረሳው ወንድማችን ነበር፡፡ በሀዘን በመረረ ቃልም ነው ሞቱ እውን አልመሰል ቢለኝ በጽሁፍ ያቀረብከውን የሀዘን እሮሮ የጻፍኩት፡፡ በሚያሳዝን መልኩ ወንድማችንን አጣነው፡፡ ይህ እንግዲ በኔ የደረሰ የቅርብ እውነታ ነው፡፡ ዛሬም ግን ኩዌት ውስጥም ሆነ የተቀረው አረብ ሀገር የዜጎቻችን ግፍ፣ በደል፣ ሞት፣ እንደቀጠለ ነው፡፡ እንዳለመታደል ሁኖ አንድም ጥሩ ነገር ለመሰማት ጆሮአችን አልታደለም፡፡ እኔማ አንዳንዴ በቃበሻ ዋጋው እንዲህ ሆነ፣ ማነው ይህንን በደል የሚያስቆም? መቼ ነውስ በየአረብ ሀገሩ ለሚንገላታው ዜጋ መላ የሚሰጠው? የውስጤ መልስ የሌለው ጥያቄ ነው፡፡

 ከመቼውም በተለየ መልኩ እርስ በእርሳችን ተጨካከንን ድህነታችንም ከፋ፡፡ማንም አረብ መጫወቻ ሆንን፡፡ ታዲያ የዚህ ችግር መፍቻ ቁልፉ ምንድነው፡፡ በ2004 ወደ አረብ አገር የተሰደደውን ሰደተኛ ብዛት ለአንተ አልነግርህም፡፡ /እሱ ለእኔ ባይነግረኝም እኔ ልንገራችሁ፡፡ በ2011 ብቻ 103.000 ኢትዮጵያዊያን ወደ የመን ገብተዋል፡፡ ይሄ አንድ ሀገር ነው በአጠቃላይ አረብሀገር አስሉት፡፡/ ለኔ ጉድ ያሰባለኝ ከወራት በፊት ከኢትዮጵያ እየተመለስኩ ኤርፖርት ያገኘኋት አንድ የቅርብ ወዳጄ ግን ውስጤን ይበልጥ እንዲሰበር ነበር ያደረገችኝ፡፡ ነርሰ ናት፡፡ በሙያዋም ተቀጥራ ትሰራ ነበር፡፡ አንድ ወቅትም የድግሪ ትምህርቷን ቀጥላ እንደነበረ አጫውታኛለች፡፡ በዛን ሰዓት ሳገኛት ግን በሀገሯ መኖር አማሯት ሳውዲአረቢያ የቤት ሰራተኛ ሆና ለመሄድ ስትል ነበር ኤርፖርት የተገናኝ ነው፡፡ ከዚህ በላይ እንግዲ ምንም የለም፡፡ መጪው ጊዜ ግን እንዲህ አይነት የዜጎች ሰቆቃ የማናይበት እንዲሆን የዘውትር ምኞቴ ነው………ብሏል፡፡ የሚያሳዝን ነገር ነው፡፡

ያን ተከትሎ አንዲት ልጅ ቻት ስታደርገኝ የመምህራን ኮሌጅ ዲፕሎማዋን ይዛ ታስተምርበት የነበረውን ትምህርት ቤት ተሰናብታ ወደ አቡዳቢ መንጎድዋን ስትነግረኝ መሪር ሀዘን ነው የተሰማኝ፡፡ ሀገር ውስጥ የተማሩት ስራ አጥተው ኮሊንስቶን ይሰራሉ ተብሎ በሚዲያዎች ገኖ መውራቱ ገርሞኝ ነበር፡፡ የገረመኝ መስራታቸውን ተቃውሜ አልነበረም፡፡ ሀገራቸው ሆነው ቢሰሩ ምናለበት በሚል ነው፡፡ ዲፕሎም እና ዲግሪ ይዘው እንደዚህ በሰው ሀገር መገረድን ሲሰማስ ምን ይባላል? በሀገር የተገኘውን መስራት ክብር መሆኑ ይሰመርበት፡፡ ጀምሬው የነበረውን ሀበሻዎች በሉብናን ያላቸውን ህይወት የሚዳስስ ታሪክ ልመለስበት ወደድኩ…. ከዛ በፊት ግን አዜብ የተባለች የፌዝቡክ አንባቢዬ ስልኬን አንኳኳች፡፡ ስከፍተው ጠላታችሁ ክፍት ይበል ልብ የሚያለሰልስ ብርጭቆ ወረቀት የሆነ ድምጽ በጆሮዬ ተንኳለለ፡፡ ‹‹ግሩም /ሀይማት ነህ?›› ስሜን ከእነአባቴ ግሩም /ሀይማት ብላ ስትጠራ../ቤት ክፍል ውስጥ የሚደረግ ስም ጥሪ መስሎኝ ‹‹አቤት!›› ብዬ በጩኸት ላደምቀው ስል ‹‹..ነህ..›› የሚለውን ጨመረችልኝ፡፡ አቤት የኔ ቆንጆ ቲቸር ማን ልበል? አልኳት፡፡ የተደወለልኝ ቁጥር ከየመን ስለሆነ የሚያውቁኝ ናቸው ብዬ ለመቀለድ፡፡

     የሆነ ደስ በሚል ቅላፄ ‹‹አታውቀኝም እዚህ የመን መጥቼ ነው፡፡ ችግር ገጥሞናል፡፡…›› ሳግ ነገር የተናነቃት መሰለኝ፡፡ ‹‹..ሸሽሽ…›› የሚል ድምጽ ተሰማኝ፡፡ ‹‹..የለ ተሀረኩ..የለ..›› የሚል ድምጽ ሰማሁ፡፡ ግራ ተጋባሁ፡፡ ‹‹አናግሪው ቶሎ በይ..›› የሚል ድምጽ ከጀርባ በደከመ ሁኔታ ይሰማል፡፡ ‹‹ሄሎ ከኤርፖርት ይዘውን ሚግሬሽ እስር ቤት ሊወስዱን ነው፡፡ ምን ትረዳናለህ..እባክህ እርዳን ወደ ሀገር ሊመልሱን ነው፡፡ መመለስ አልፈልግም እባክህ…›› በለቅሶ ታጀበ፡፡ አይኔ ባያነባም ውስጤ ግን አብሯት አነባ፡፡ ቢሆንም መጠየቅ ስለነበረብኝ ከየት ኤርፖርት ነው የያዟችሁ ወዴት ስትሄዱ..

   ‹‹ሰነዓ ኤርፖትርት ላይ ነው የያዙን ወደ ቤይሩት እየሄድን ነበር…›› ተቋረጠ፡፡ ሜግሬሽን ሄጄ ላገኛቸው ፈለኩ፡፡ ያለሁበትን ሱቅ የሚጠብቅልኝ ሰው ስፈልግ ቆየሁና አገኘሁ፡፡ በዚህ አገር አጠራር ጀዋዛት የሚባለው እስር ቤት ሄድኩ፡፡ አሁን ስላወኩት ከፊት ተጠቀምኩኝ እንጂ በሰዓቱ ስሟን ስላልነገረችኝ ማን ብዬ ላስጠራት፡፡ ተጠጋሁና ተደወሎልኝ ነበር ማን ነው የደወለልኝ ስል ‹‹አዜብ..›› አሉ እና ጠሯት፡፡ ትንሽዬ ልጅ መጣች፡፡ እድሜዋ ያለማጋነን 16 ወይም 17 ቢሆን ነው፡፡ ግራ መጋባትና ፍርሃት የተራኩቱት ፊቷን ሳይ አሳዘነችኝ፡፡ ተጨባበጥንና ‹‹ስሜ አዜብ….ነው፡፡ ፌስቡክ ላይ ጓደኛህ ነኝ፡፡ የምትጽፋቸውን ባይም ያለኝ አማራጭ ነው እና ቤይሩት ለመሄድ መጥቼ ኤርፖርት ላይ የእናንተ ቪዛ የተስተካከለ አይደለም ብለው 15 የምንሆነውን ያዙን አሁን ወደ ሀገር ሊመልሱን ነው እባክህ አግዘኝ ስንት ከስክሰን…›› እንባ ቀደማት፡፡ ለስደት ህይወት ማጀቢያው እንባ፣ ብስጭት፣ ፀፀት እና ጭንቀት ናቸው፡፡ የጀመረችውን ትጨርስ ብዬ በዝምታ ዝምታ ውስጥ ሰፍሬ አይኔን ከአንዳቸው አንዳቸው ላይ እያንቀዋለልኩ ጠበኳት፡፡ ብዙ አወራን፡፡

    ይመለከተዋል ያልኩትን ሰው ፈልጌ ላናግር ሞከርኩ፡፡ እንደጅብ ቆዳ ቅኝቱ ‹‹እንብላው..እንብላው..›› ብቻ ሆንብኝ፡፡ እዚህ ሀገር ግልጽ ሙስና ነው ያለው፡፡ ያበደረህን ገንዘብ የሚጠይቅህ ነው የሚመስለው፡፡ ‹‹ለአንድ ሰው 400 ዶላር ክፈል እና እፈታልሀለሁ..›› ተባልኩ፡፡ ኪሴ ያለችኝ 4000 ሪያል ናት፡፡ በዶላሪኛ ስትሰላ 20 ዶላር ማለት ነው፡፡ አስቡት ልዩነቱን፡፡ ተመለስኩኝ እና ያሉኝን ነገርኳት፡፡ የሚበሉ የሚጠጡት ነገር ገዛዝቼ አቀበልኳቸው እና ብር ከላኩልኝ ደውልላቸው ላለችኝ ሰዎች ደዋወልኩኝ፡፡ አንድ ብር ያሰከረው ጉንጩን በጫት የወጠረ ሰው መጣና ‹‹አንተነህ ያናገርከው?›› አለኝ፡፡ ቢጨንቀኝ እንጂ የማወጣበት ገንዘብ እንደሌለኝ ነገርኩት ‹‹…ሁሉን ከፍዬላቸዋለሁ ማታ ወደ ቤይሩት ይሄዳሉ…›› ማንም አይወጣም ሲል ድንፋታ የምትመስል ነገር ወርውሮልኝ ሄደ፡፡

   ውስጤ እያዘነ ተሰናብቻቸው ከሚግሬሽን እስር ቤት ወጣሁ፡፡ መቼ ነው ፈጣሪ የሚሰማን? መቼ ነው እንባችን ስፍሩን የሚሞላው? መቼ ነው በቃ! የሚለን? እውን መንግስት ቤይሩት መሄድን አስቦበት ነው የከለከለው? ከሆነ ይህን አይነት ድርጊት ሲፈጸም እንዴት አያውቅም? በኬንያ ቪዛ እንዴትስ የመን ሊመጣ ይችላል? የመሳሰሉትን አሰብኩ፡፡ ከማሰብ ውጭ ግን ምን አመጣለሁ? በቀረችኝ ሳንቲም ታክሲ ተሳፍሬ ጉዞዬን ስቀጥል ስለ ቤይሩት የሰማሁትን ማሰላሰል ጀመርኩ፡፡ ያሰላሰልኩት ብዙ ነው ባለፈው ወደጀመርኩት ታሪክ ልንጎድ…..     
          
   በተከታታይ በቻት ሳጥኔ ሳትታክት እየጻፈችልኝ ያለችውን እህታችን ደግሜ ላመሰግናት ወደድኩ፡፡ ቀጠልኩ.. ከላይ እንደገለጽኩልህ ልጅቷ የተሰጣት መልስ ጥሩ ስላልሆነ መፍትሄም ስላጣች ያላት አማራጭ መጥፋት ነበርና ጠፋች፡፡ ጠፍታም ለረጅም ጊዜ የተለያየ ቤት ሰርታለች፡፡ ካንዱ ስትወጣ ስራ አጥታ ረጅም ጊዜ ስትቀመጥ ብዙ ተቸግራለች፡፡ አሁን ያለችበት ቤት ሁለት አመቷ ነው፡፡ ሰውዬው ደስ ሲለው ይከፍላታል ሲያጣ ይከለክላታል፡፡ እንደዛም ሆና እንደነገረችኝ ልጅዋን በጥሩ ሁኔታ እያስተማረች ነው፡፡ ወላጆች ግን ልጄ ምን ሰርታ ነው ብሩን ያመጣችው አይሉም፡፡

   የእኔውን ቤት ጉድ ደግሞ ልንገርህ…እኔ የነበርኩበት ቤት 3 ሰው ብቻ ነው ያለው፡፡ ቀን ቀን አይውሉም፡፡ ሴትዮዋ መጥፎ የምትባል አይደለችም፡፡ ልጁ ተማሪ ነው፤ እሷ ስራ አላት፡፡ ወንድሟ ደግሞ የቤተሰብ ድርጅት ውስጥ ይሰራል፡፡ ታዲያ ግን ቤት ውስጥ ስራው ማለቂያ የለውም፡፡ የምተኛው ሌሊት 7 ሰዓት ነው፡፡ የቀኑን ወደ ሌሊት ገልብጠውታል፡፡ ቀን ቀን ቤት ስለማይውሉ ስራ ብዙም አያስቸግረኝም፡፡ ከ10 ስዓት በኋላ ግን መቀመጥ እስኪያቅተኝ በስራ ያጣድፉኛል፡፡ በዛ ላይ ከ7 ሰዓት በኋላ ያለውም ቢሆን መተኛት አትበለው፡፡ ልጇ ቀበጥ ነገር ነው፡፡ የ11 አመት ልጅ ቢሆንም አጠገቡ ያለውን ውሀ ማንሳት አይፈልግም፡፡ መጥሪያውን ተጭኖ ይጣራል፡፡ እንደሰው መተኛት ያለብኝ አይመስለውም፡፡ እሱስ ባልከፋ እንቅልፍ ነው የነሳኝ ሱሰኛ የሆነው ወንድሟ ሌላ ፈተናዬ ነበር፡፡ ፍላጎቱ የተወጠረ ስሜቱን ማርገብ ነው፡፡ ለእኛ ያለው አመለካከት በንቀት የተሞላ ነው፡፡ በቃ! ለስሜት ማስከኛ የተፈጠርን እቃዎች ነው የምንመስለው፡፡

    አንዳንዶቹ በፍርሃትም ይሁን በፍላጎት ፍቃደኛ ስለሚሆኑላቸው መሰለኝ ‹‹..አንቺ ከሌሎቹ በምን ትበልጫለሽ? በፊት ከነበሩት ውስጥ እከሊትን..እከሊትን እንዲህ አደርግ ነበር ይለኛል ስማቸውን እየጠራ፡፡ እሺ እንደማልለው ሲያውቅ ሁሌም ይዝትብኛል፡፡ ለሴትዮዋ የሆነ ያልሆነውን ይነግራታል፡፡ በዚህ ምክንያት ከማንም ጋር እንዳልገናኝ ቤት ትቆልፍብኝ ነበር፡፡ በዚህ በጣም ስማረር ቢሮ ሌላ ቦታ እንዲቀይሩኝ ነገሬ ተቀየርኩ፡፡ የተቀየርኩበት ቤት የሚገርምህ ጥቁር አትወድም፡፡ የወሰደኝ ባልዋ ነበር፡፡ ከእኔ በፊት የነበረችው ማዳጋስካራዊ ቀላ ያለች ነበረች፡፡ ከእኔ ጋር አንድ ፊሊፒኒሳዊ ተቀጥራለች፡፡ ሁለት ነን ማለት ነው፡፡ እኔ 4 ልጆቿን እይዛለሁ ፊሊፒንዋ ቤት ታጸዳለች፡፡ ምግብ ቤት ውስጥ አይሰራም፡፡ እዛ ፎቅ ላይ ያሉት ሁሉ ቤተሰቦች ናቸው፡፡ ልጆቹ አያቶቻቸው የሰሩትን ነው የሚበሉት፡፡ አባትየው የት እንደሚበላ አናውቅም፡፡ እሷ ከልጆቹ ጋር ትበላለች፡፡ እኔና ፊሊፒኗ በመሀል ፍዳችንን በላን፡፡ አንድ ሴጣናም ልጅ አላቸው እሱን ይዤ ስንቀዋለል ነው የምውለው፡፡ ከፊሊፒንስዋ እንዲያውም እኔ እበላለሁ፡፡ ምክንያቱም ልጆቹ አያት ቤት ያለችው ሀበሻ ነች፡፡ እስዋ ትሰጠኛለች፡፡ የምግቡ እና የልጁ ሁኔታ ሲመረኝ ጠፋሁ፡፡

    ከመጥፋቴ በፊት እሰራበት የነበረው ቦታ ከፊት ለፊት ያለው አፓርትማ ላይ ያለችው ደግሞ ጠዋት11 ሰዓት ተነስታ ስራ ትጀምር እና ሌሊቱን ሁሉ አትተኛም፡፡ ስራ ባይኖር እንኳን እህቶቿ ጋር ትወስዳታለች፡፡ ሌላም እታች ያለች ኢትዮጵያዊት አለች፡፡ እሷ ደግሞ ከማንም ጋር እንድትገናኝ አትፈቅድላትም፡፡ መውጫ ሰዓታቸውን ጠብቃ ነው ወደ እኛ የምትመጣው፡፡ የእሷ አሰሪ ደግሞ ሌላው ቀርቶ ፓንቷን እንኳን ማውለቅ አትፈልግም፡፡ ለሁሉ ነገር ጥሪ ነው፡፡ ቤቱን ካጸዳች በኋላ ሴትዮዋ ቼክ ታደርጋለች፡፡ በዚህን ጊዜ አውቃ ግርግዳው ላይ ወይም ሶፋ ስር ቆሻሻ ታደርግና አልጸዳም ብላ ታሰቃያታለች፡፡ ከጨረሰች እኛ ያለንበት አፓርትማ ላይ እህቷ ስላለች እሷም ጋር ታሰራታለች፡፡ ከጠፋሁ በኋላ ግን ምን ላይ እንዳለች አላየኋትም፡፡

     አሁን የምሰራው ከከተማ ወጣ ያለ ቦታ ነው፡፡ ያለሁበት አካባቢ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን አሉ፡፡ ስራቸው ግን ያስጠላል፡፡ ሴትነታቸውን ይሸቅጣሉ፡፡ ከተማውን እንደጨረስክ ያለው ቦታ ነው የሚሰሩት፡፡ እዚህ ያሉት ሶሪያዊያን ሲነግሩኝ በ50.000 የሉብናን ገንዘብ ነው የሚሰሩት፡፡ ይህ ማለት 27 ዶላር አካባቢ ባለ ዋጋ ራሳቸውን ይሸጣሉ፡፡ አንዳንዴ ግን ቢዝነስ ቢሰሩ አይገርመኝም፡፡ ምክንያቱን ቤት ሰራተኛነት ከጀርባው ያለውን ችግር ስታይ የግድ የሚገፋቸው ነገር ታያለህ፡፡ የዛኑ ያህል የሚያናድዱኝ በነጻ ቪዛ መጥተው በሴተኛ አዳሪነት የሚተዳደሩት ናቸው፡፡ አሁን የምሰራበት ቦታ ሶስት ወንዶች ናቸው የሚሰሩት እኔ ብቻ ነኝ ሴት በየአመቱ ለሶስት ወር የሚያግዛቸው አንድ ሴት ይቀጠርላቸዋል፡፡ ልክ አሁን እኔ እንደተቀጠርኩት፡፡ ታዲያ ከባንግላዲሾች እና ሶሪያዎች ጋር በማይረባ ብር ይተኛሉ፡፡ ሁሉ እንደ እነሱ ስለሚመስላቸው በእርካሽ ትገኛላችሁ ይላሉ፡፡

   ይወራ ከተባለ ለጉድ ይወራል፡፡ እዚህ የመን ውስጥ ካሉት መካከል ወገናቸውን የሚሸጡ የመኖራቸውን ያህል ለሰው ችግር ቆዳቸውን የሚገፈፉ ጥሩ ሰዎች አይቻለሁ፡፡ ኤቢ ደመቀ በአብዛኛው የመን ባለ እና የመን በነበረ ሰው ዘንድ የሚታወቅ በበጎ ተግባር ላይ የተሰማራ ነው፡፡ ዮሀንስ ተስፋዬ /ጆኒ/ የሚባል ልጅ አለ፡፡ ከረንቦላ ቤት ስለነበረው ጆኒ ከረንቡላ ይሉታል፡፡ ከባህር የመጡትን ከረንቡላ የሚያጫውትበት ቤት ውስጥ ከማሳደር አንስቶ የማይሰራው በጎ ስራ የለም፡፡  በተጨማሪ ኩሩቤል የሚባል ኢትዮጵያዊ UNIDOM የተባለ ድርጅት አዋቅሮ ብዙዎችን ለመርዳት ሞክሯል፡፡ ስለእነዚህ ሰዎች በሰፊው እመለስበታለሁ፡፡ አሁን ያነሳኋቸው ቀጣይ ለማቀርበው ታሪክ ምክንያት ስለሆኑኝ ነው፡፡ በሚቀጥለው በቀጠሮ እንገናኝ
                        ሰላም ሰንብቱ 

Tuesday, August 28, 2012

የአቡነ ጳውሎስን ሞት ስሰማ ሶስት ነገሮች ታወሱኝ
የአምላክስራ ግሩም

ከፈጣሪያቸው ይልቅ ቀጣሪያቸው መለስን ይፈራሉ የሚባሉት የአቡነ ጳውሎስን ሞት ስሰማ ሁለት ነገር ትዝ አለኝ፡፡ ቀጣሪያቸውን ያልኩት በአንድ ወቅት ጳጳሱ የሲኖዶሱን ህግ ሊቀይሩ ፈልገው በተነሳው ውዝግብ ዙሪያ አለቃ አያሌውን ቃለ-ምልልስ ስሰራ ከኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቀኖና ውጭ ጳጳስ በህይወት እያለ በመንግስት የተቀጠሩ ቀኖና የሻሩ ናቸው ስላሉኝ ነው፡፡

የአቡነ ጳውሎስም ሞት ስሰማ ትዝ ያሉኝ ሶስት ነገሮች…አንደኛ ተወልጄ ያደኩበት ሰፈር ቅ/ማሪያም ቤተክህነት ፊት ለፊት በመሆኑ ሲወጡ ሲገቡ ወታደራዊ ሰላምታ እየሰጡ ‹‹ታጋይ ጳውሎስ!..›› የሚሉዋቸው ሁለት ልጆች ታወሱኝ፡፡ ሁለተኛው በሳቸው ጠባቂዎች እንደተገደሉ የሚነገረው ባህታዊ እና እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን መጥተው ከፊቴ ድቅን አሉ፡፡ ሶስተኛው በጎንደር ሀገረ ስብከት ውስጥ የተሰራውን ሙስና አጋልጨ በእሳቸው እና በዲያቆን ደሳለኝ ፈንቴ ከሳሽነት ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ እኔና ጓደኛዬ ላይ የተፈጸመብን ግፍ ታወሰኝ፡፡ ለሶስቱም ትዝታዎቼ ምክንያት አለኝ፡፡ በተለይ ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ የተደረገብኝ ኢ-ሰብአዊ ድርጊት ከህሊናዬ የሚፋቅ አይደለም፡፡

በዕለተ ሀሙስ አረብ ሳይት ላይ ብቅ ጥልቅ የሚጫወተው ኢቲቪ ድብብቆሽ ጫዎታውን ስለቀጠለ ሀገሪኛ መረጃ የሚያቀብለን ብቸኛው ኢቢኤስን እያየሁ ነው፡፡ የቀብር ስነ-ስርዓታቸው በተፈጸመበት ወቅት ብዙ እውነት የማይመስሉ ሙገሳዎች ከአስተያየት ሰጪዎች ሰማሁ፡፡ እውነት ለእሳቸው ነው ሌላ የማላውቀው አቡን ሞተዋል ያስብላል፡፡ መቼም ከተጠናወተን መጥፎ አመል ውስጥ ሰው ሲሞት ጨካኙን ደግ ሌባውን ንጹህ ማድረግ፣ ሰው ያልሆነውን ነው ብሎ መካብ ዋነኛው በሽታችን ነው፡፡ ምናለ ዋሽተን ያልሆኑትን ከምንቀባጥር ዝም ብንል በዝምታ፡፡ መቼ ይሆን አካፋን አካፋ የምንለው? ‹‹..ካልሆነም ዝም አይነቅዝም..›› ይባላል እኮ፡፡ በተለይ አንድ መምህር/ሰባኪ/ ነኝ ያለ ሰው አድርባይነቱ ሳይሆን በዚህ ውሸትን ባዘለ አንደበቱ የሚሰብከው እንዴት ይሆን? የሚል እንዳስብ አድርጎኛል፡፡ በቲቪው ፕሮግራም ላይ ቅሬታ የለኝም፡፡ መሰራት ያለበትን ነው የሰሩት፡፡ የሰዎችን ሀሳብ መገደብ የለበትምና..ስለሳቸው ግን ከተባለው ውጭ መሆኑን ሁላችንም እናውቃለን፡፡ እኔ ግን የማስታውሰው እና የማውቀው እውነታ ተቃራኒ ነው….

ትዝታ አንድ፡- በቅጽል ስማቸው ፑሲ እና ነጬ በመባል የሚታውቁት ልጆች በይፋ ወታደራዊ ስላምታ እየሰጡ ‹‹ታጋይ ጳውሎስ!!›› ይበሉ እንጂ የአካባቢው ሰውም ሆነ የቤተክርስቲያኗን ቀኖና የሚያውቁ በድብቅ ይህን ከማለት ወደኋላ አላሉም ነበር፡፡ በወያኔ መመረጣቸው ብቻ ሳይሆን በፖሊስ ዲፌንደር መኪና ከፊት ከኋላ መሳሪያ ባነገቡ ጠባቂዎች ከመታጀባቸው ጀምሮ ታጋይ ጳውሎስ የተባሉበትን ነገር ከዘረዘርኩት ጊዜም ቦታም አይበቃም፡፡ በቲቪ ካየኋቸው አስተያየት ሰጪዎች መካከል ‹‹..ለሀይማኖታቸው ተቆርቋሪ፣ ለጋስ፣ ደሀ ረጂ..፣..›› ምንትሴ..ቅብርጥሴ የሚሉ ግነት የሞላቸው ነገሮች ናቸው ይህን እንዳስታውስ ያደረገኝ፡፡ በተለይ ‹‹..ለሀይማኖታቸው ተቆርቋሪ…›› የምትለው ነገር አልዋጥልህ አለኝ፡፡ ገዳማት ሲፈርሱ የታገሉት ትግል ስለመኖሩ መረጃ ስላጣሁ ነው አልዋጥልህ ያለኝ፡፡ ለቅዳሴ ጧፍ የሚያጡ ደብሮች ባሉዋት ኦርቶዶክስ ባጀት ጥይት የማይበሳው ፍሪጅና ስቶቭ ያለው ሶስት መኪና ከአራት ሚሊዮን ብር በላይ አውጥተው ሲያስመጡ ይህም ሀይማኖትን መውደድ ነው፡፡ ፈሪሀ እግዚአብሄር ያለው በእሱ ቤት ያደረ አገልጋይስ በጋርድና መሳሪያ መጠበቁ ሀይማኖቱን ወይስ ራሱን መውደዱን ያሳያል? ለነገሩ ራሳቸውን መውደዳቸው አይደል የራሳቸውን ሀውልት ሲኖዶሱ ሳይፈቅድ እየተቃወማቸው ያቆሙት?

ትዝታን ትዝታ ሲስበው ከእሳቸው በፊት በነበሩት በአቡነ ተ/ሀይማኖት ጵጵስና ዘመን ለዘመን መለወጫ ገብቶ ገንዘብ ያልተቀበለ የአካባቢው ልጅ የለም፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ጳጳስ ምን እንደሆነ እንኳን በማላውቅበት ሰዓት ነፍሳቸውን ይማረውና ልጆች እንግባ…እንግባ ብለውኝ ቤተክህነት ገባን፡፡ አሁን ስማቸውን የማላስታውሰው..ዘበኛ አሰላፊነት ተሰልፈን አቡነ ሰላማ ይመስለኛል ስማቸው ይዘውን ገቡ፡፡

ክስት ባለ ሰውነታቸው ላይ ልዩ ግርማ ሞገስ የተላበሱት ብፁዕ ወ ቅዱስ አቡነ ተ/ሀይማኖት መስቀል እያሳለሙ የክርስትና ስም ይጠይቁን ጀመር፡፡ ተራዬ ደርሶ ክርስትና ስሜን ተናግሬ መስቀል ተሳለምኩ፡፡ ከእየሩሳሌም የመጣ መስቀል በክር በክር ተደርጎ አንገታችን ላይ እያጠለቁልን አስር አስር ብር ሰጡን፡፡ እንደ ሀይማኖት አባትነታቸው..እኛም እንደ ልጅነታችን ማን እንደጀመረ ባላስታውስም ዝቅ ብለን እግራቸውን እየሳምን ወጣን፡፡ በዚህ ጊዜ ያስተዋልኩት አሁንም የማስታውሰው ጫማ አለማድረጋቸውን እና እግራቸው ልስልስ ያለ መሆኑን ነው፡፡ ታዲያ ይሄ ነገር ሲገርመኝ ስላደኩ ነው መሰል በአንድ ወቅት ቤተክህነት ይሰሩ የነበሩ የጓደኛዬን እናት ጠየኳቸው፡፡ ደርግ ይሰሩልኛል ብሎ ቢመርጣቸውም እንደፈለገው ሳይሆን እንዳልፈለገው ሆነው ተገኙ፡፡ የአራት ኪሎው ቅዱስ ስላሴ ካቴድራል ቤተክርስቲያን ደውል ፓርላማ ውስጥ ስለሚበጠብጥ ተብሎ እንዳይደወል ታገደ፡፡ ቀጠለናም መውጫ በሩ በግንብ ተዘጋ፡፡ ለማስከፈት ያደረጉት ትረት ሰሚ አጣ፡፡

በዚህን ጊዜ ያ-የተዘጋ የቤተክርስቲያን በር እስኪከፈት ጫማ ላለማድረግ እና ከጥራጥሬ ውጭ እህል ላለመብላት ቃል ገብተው እስከሞቱበት ዕለት የተዘፈዘፈ ሽንብራ እና ጥራጥሬ እየበሉ ኖሩ፡፡ ታዲያ ትዝታዬ ብቅ ያለው የአሁኑ ደግ ለሀይማኖታቸው ተቆርቋሪ የተባሉት ዋልድባን የሚያክል ገዳም ሲጠረመስ እንኳን ድምጻቸውን አልሰማሁም፡፡ አቡነ ተ/ሀይማኖት በደሞዛቸው የሚያስተምሯቸው ወደ ሁለት መቶ የሚጠጉ ልጆች ነበሩ፡፡ በአካባቢያችን ልጁን ማስተማር ያልቻለ ሰው ማመልከቻ አጽፎ ሲሄድ ይረዱ ነበር፡፡ አሁን ደግ፣ ለጋስ ሲባሉ የሰማሁት አቡነ ጳውሎስ ግን ደሞዛቸውን ከአቡነ ተክለሀይማኖት በሶስት እጥፍ ቢያሳድጉም ባጀት የለም በሚል ግንፍሌ ድልድይ ጋር የነበረው የልጆቹን መኖሪያ የአቡነ ገሪማን ፊርማ ባዘለ ደብዳቤ ከረቸሙት፡፡ ቦታው ለቢሮ እና ለተለያየ ነገር እንዲውል ሆነ፡፡

ትዝታ ሁለት፡-እለቱ ሀሙስ መሆኑን አስታውሳለሁ፡፡ ቦሌ ማተሚያ ቤት ጋዜጣ ለማሳተም ልሄድ ስል ግርግር እስጢፋኖስ ጋር አየሁ፡፡ ዕለቱ የእሲጢፋኖስ በዓል የሚከበርበት በመሆኑ ብዙም ትኩረት ሳልሰጠው ነበር ያለፍኩት፡፡ ቦሌ ማተሚያ ቤት ስደርስ ግን ጳጳሱ አንዱን ባህታዊ ገደሉ የሚል ግነት የተሞላበት መረጃ ደረሰኝ፡፡ ለማተሚያ ቤቱ ካሜራ ክፍል የምሰጠውን ሰጠሁና ለማጣራት ወደ እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን ተመለስኩ፡፡ ሰዉ ሁሉ የሚያወራው የተምታታ ሆነብኝ፡፡ ቦታው ላይ ከነበረ ሰው ትክክለኛ መረጃ ማግኘት አቃተኝ፡፡ አንዱ የሚናገረውን ሌላው አይደግመውም፡፡ ጠባቂያቸው እንጂ እሳቸው አይደሉም የሚለው ሀሳብ ደጋግሞ ደረሰኝ፡፡ ወደ ቦሌ ማተሚያ ቤት ተመልሼ የጋዜጣውን ህትመት እየተከታተልኩ ሳለ ድካም ተሰማኝ እና ማሙሽ የሚባል ልጅ፣ ጌታመሳይ ገ/መስቀል ማራቶን የሚባል የስፖርት ጋዜጣ የሚከታተል ልጅ ወደ ተቀመጡበት ተቀላቀልኩ፡፡ ወሬው ስለዚሁ ጉዳይ ነበር አንድ በትክክል ቦታው የነበረ ልጅ ስለነበር ትክክለኛ መረጃ ሰጠን፡፡ በጠባቂዎቻቸው ነው ባህታዊው የተገደሉት መባል ብቻ ሳይሆን የብረት አንካሴያቸውን እየወዘወዙ ወደ ጳጳሱ በማምራታቸው እንደሆነ ችግሩ የተከሰተው ሰማሁ፡፡

ዋናው ነገር ግን ይህ አልነበረም፡፡ የተገደሉትን ባህታዊ ማንኛውም ቤተክርስቲያን ለቀብር ቦታ እንዳይፈቅድ ተወገዘ፡፡ እኝህ ባህታዊ ጳጳሱን እንኳን ሊገድሉ አስበው ቢሆን በቀልን ምን አመጣው? በቀል ካልሆነስ የሚቀበሩበትን ቦታ መከልከሉ ምን ይሆን ጥቅሙ? ፈረንሳይ ለጋሲዮን እየሱስ ቤተክርስቲያን አካባቢ ራስ ካሳ ቤት ተገኝቶ ህዝቡ በዘልማድ ጭቁኑ ሚካኤል የሚለው ቤተክርስቲያን የቀብር ቦታ ፈቀደ፡፡ የደብሩ አስተዳደር ተወገዙ፤ ቤተክርስቲያኗ ከሲኖዶስ ትዕዛዝ አፈንግጣለች ተባለ፡፡ በመወገዝ ብቻ አልበቃም አመታዊ የጥምቀት በዓልን ታቦቱ ከሌሎቹ ታቦታት ጋር ጃንሜዳ እንዳይወጣ ታገደ፡፡ ሐምሌ አስራዘጠኝ ማናፈሻ ጀርባ በቀበሌ 22 መዝናኛ ገባ ብሎ የማርያም ፀበል ያለበት ቦታ ከአድባራቱ ተነጥሎ አደረ፡፡ የሚገርመው ግን የኢየሱስ ደብር ታቦት ሚካኤልን ጥሎ ከሌሎቹ ጋር ጃንሜዳ አላደረም፡፡ እዛች አነስተኛ ቦታ ላይ አብረው አደሩ፡፡ ህዝቡም በእልህ አድምቆት አደረ፡፡ አስታውሳለሁ እኛም ጃንሜዳ ቢሆንም ያመሸነው አዳር ያደረግነው እዛ ነው፡፡ እንኳን ሰው ታቦት በሚያግዱት ጳጳስ ማን አስተዳድሩ አላችሁ ብለው ለእየሱስ ደብር ካህናት ዋጋቸውን ሰጡዋቸው፡፡

ትዝታ ሶስት፡- ኢህአዴግ አዲስ አበባን ከተቆጣጠረ በኋላ በጦርነቱ ለተጎዱ ቤተክርስቲያናት ማደሻ ከጎንደር አገረ ስብከት ጽ/ቤት ጥያቄ ቀረበ፡፡ በወቅቱ ጠ/ሚኒስትር ለነበሩት አቶ ታምራት ላይኔ ነበር ጥያቄው የቀረበው፡፡ ምንም አይነት ባጀት የለንም 10 ቶን ቡና ተፈቅዶላችኋል እሱን ወስዳችሁ ሽጡና በትርፉ የተወሰኑትን አድሱ ተባለ፡፡ ይሄን ቡና ወስዶ የመሸጡን ሀላፊነት የሀገረ ስብከቱ ጳጳስ ዲያቆን ደሳለኝ ፈንቴን ወከሉ፡፡ ቡናው ተሸጦ ግን ለቤተክርስቲያኗ ማደሻ ሳይሆን ለአፍ ማሰሻ፣ ለኪስ ማደለቢያ ነው የሆነው፡፡

ቢታይ ቢታይ ሁሉም ዝም..ሆነ፡፡ ነገሩ የከነከናቸው አንዳንድ ካህናት ቤተክህነት ድረስ ለክስ ከጎንደር መጡ፡፡ ምንም የምናውቀው ነገር የለም ተባሉ፡፡ መፍትሄም ሊያገኙ አልቻሉም፡፡ በዚህን ጊዜ ‹‹ገመና›› የተባለ ጋዜጣ አሳትም ነበረ እና ሙሉ መረጃውን ሰጡኝ፡፡ አጣርቼ ትክክለኛ ማስረጃ በመሆኑ ለህዝብ አቀረብኩት፡፡ የመረጃውንም ኮፒ ጋዜጣው ላይ አቀረብኩ፡፡ ወዲያው በብፁዕ ወ ቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ክስ ተከፈተብኝ፡፡ የክሳቸው ፍሬ ሀሳብ ትክክለኛ እና መጠየቅ ያለበትን ነው የጠየቁት፡፡ ‹‹ገመና›› የተባለ ጋዜጣ ያወጣውን ዘገባ አይተን ሁኔታውን ለማጣራት ሞክረናል፡፡ የተጠቀሱት ግለስብ የቀረበብኝ ማስረጃ ፎርጅድ ነው እኔ ስለሁኔታው አላውቅም ስላሉ ጋዜጠኛው ላይ ክስ ተመስርቶ ያለው ማስረጃ እንዲረጋገጥ፡፡ ትክክለኛ ከሆነ የጉዳዩ ባለቤቶች እንዲጠየቁ፡፡ ያቀረበው ማስረጃ ትክክለኛ ካልሆነ እና ፎርጅድ ከሆነ የእምነታችንን ክብር የሚያወርድ ነገር በሀሰተኛ ማስረጃ በማቅረቡ እንዲጠየቅ..ይላል፡፡ በዚህ ክስ ቅሬታ የለኝም፡፡

ለመርማሪ ፖሊሱ ግን ገንዘብ ሰጥተው ትንሽ ቅጣትም ያሰፈልጋቸዋል፡፡ በደንብ መርምርልኝ ማለታቸው ከሀይማኖት አባት የሚጠበቅ ይሆን? ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት እንዲፈፀምብኝ አድርገዋል፡፡ ክትትል ሲደረግብኝ ቆይቶ ዘውዲቱ ሆቴል ራት እየበላሁ ሳለ ተያዝኩ፡፡ ፖሊስ ጣቢያው ጊቢ ውስጥ ገና ከመግባቴ ጀምሮ ዱላ ተቀበለኝ፡፡ ውብሸት የሚባል መርማሪ ወዲያው ስልክ ደውሎ መያዜን ሲናገር ከቢሮው ውጭ ብቀመጥም እየሰማሁት ነው፡፡ ቃል ለመስጠት ፍቃደኛ ባለመሆኔ ሶስት ፖሊሶችን ጠርቶ ከራሱ ጋር አራት ሆነው ሰማይ ምድሩ እስኪዞርብኝ አዞሩኝ፣ ቀጠቀጡኝ፡፡ በግድ ግን ቃሌን ለመስጠት ፍቃደኛ አልሆንኩም፡፡ መረጃው አለህ? ያለህ መረጃ ፎርጅድ ነው ተብሏል፡፡ እላዩ ላይ ያለው ማህተም የሀገረ ስብከቱ ጳጳስ አይደለም አለኝ፡፡ /አንድ ወረቀት ላይ ያረፈ ማህተም እያሳየኝ/ የእሳቸው ማህተም ይሄ ነው ..››ሲለኝ ግን እልህ ያዘኝ፡፡ ማህተሙን ከዚህ ወረቀት በኋላ መቀየራቸውን የሚያረጋግጥ ትንሳዔ ዘ ጉባኤ ማተሚያ ቤት ማህተም ያስቀረጹበት ማስረጃ እንዳለኝ ጭምር ቃል ሰጠሁ፡፡ ይህንን የሰጠሁትን ቃል ግን ወዲያውኑ ደውሎ የነገራቸው ፊቴ ነው፡፡

በሚያሳዝን ሁኔታ ተከሳሽ የሆነው ዲያቆን ደሳለኝ ፈንቴ ጉዳዩን እንዲከታተል በእሳቸው ፍቃድ ተላከ፡፡ በዛው ማታ መጣ፡፡ ይሄኔ ነገሮች ሁሉ ጎረበጡኝ፡፡ በጣም ተጠራጠርኩ፡፡ ከምሽቱ አራት ሰዓት ተኩል ላይ ቤቴ ሄደን መረጃውን እንድናመጣ ፈለጉ፡፡ ግደሉኝ እንጂ አልሄድም እናቴ በዚህ ሰዓት እንድትደነግጥ አልፈልግም አልኩ፡፡ ሰበቤ በእናቴ ሆነ እንጂ እሳቸውስ መረጃው እንዲጠፋ ካልፈለጉ እንዴት ብሩን ያጨበረበረውን ሰው ይልካሉ? ለምንስ እሰኪነጋ መጠበቅ ሳይፈልግ ዲያቆን ደሳለኝ መጣ? ፍርድ ቤት ስቀርብ ካልሆነ ላለማቅረብ ወሰንኩ፡፡ ዳግም ዱላ ተጀመረ፡፡ እነሱ ሳይበቃቸው እኔ ተዝለፍልፌ ስለወደኩኝ መሰለኝ ድብደባው የተጠናቀቀው፡፡ ራሴን ስለሳትኩ እንዴት እንደነበር አላውቅም፡፡ ራሴን ሳውቅ ግን ሌሊት ስምንት ሰዓት አካባቢ ይመስለኛል፡፡ ሽንቴ ስለመጣ ካጋደሙኝ አግዳሚ ወንበር ላይ ቀና ብዬ ሽንት ቤቱ የቱ ጋር እንደሆነ ተራኛውን ፖሊስ ጠየኩት፡፡ አሳየኝ እና ተነስቼ ስሄድ ውሻዋን ጃስ..ጃስ..ብሎ ሲያደፋፍራት እግሬን ዘነጠለችን፡ ወይም ዘነጠለኝ፡፡ የውሻውን ፆታ ስለማላውቅ ነው ሁለቱንም የተጠቀምኩት፡፡ እየተሳሳቁ ደግፈው አንስተውኝ ጊቢው ውስጥ ቆማ የበሰበሰች እና ሽንት የሚሸናባት አይጥ የሚርመሰመስባት አሮጌ መኪና ውስጥ ከተቱኝ፡፡ በማግስቱ ጓደኛዬ ዳንኤል የጋዜጣዬ ዋና አዘጋጅ ስለሆነ መታሰሬን ሰምቶ ፖሊስ ጣቢያ መጣ፡፡ ሳምንት ሙሉ እዛች የሚሸናባት መኪና ውስጥ አሳለፍን፡፡

ይህን ሁሉ የምለው ግን አስተያየት ሰጪዎቹ እና እሳቸው ይመሳሰላሉ ወይ? ወይስ አዲስ የሚመረጡትን ይሆን የሚያሞግሱት የሚለው እሳቤ መቶብኝ ነው፡፡ ምናለ እውነትን ለሰው ብለን ባንደፈጥጥ..ሰው ለማስደሰት ዋሽተን ፈጣሪን እያሳዘንን መሆኑን አትረሱ፡፡ ሙት አይወቀስም ብለንም ከሆነ ያልሆነ ቀባጥረን ከፈጣሪ ከምንጣላ ዝም ማለት አይቀልም?
ነብሳቸውን ይማር!!!!

Saturday, August 18, 2012


ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በአረብ ሀገር

ክፍል አራት

እርሰ በአርሳችን የመበላላታችን ጭካኔ ውጤት

      በግሩም ተ/ሀይማኖት



  ሰላም ወዳጆቼ…ሰላማችሁ ይብዛ! አሜን!! ለምን ገመናችን ተነካ ብላችሁ የተሳደባችሁ ስድባችሁ ባዶነታችሁን ያሳያል እንጂ ክብሬን አይነካም እና..ምላሳችሁ ይብዛ!!!…ወገን እየሸጣችሁ በሰው ደም የሰከራችሁ ስካራቸሁ ይጥፋ..ወገናችሁን መሸጥ መለወጥ የለመዳችሁ ይሄ መጥፎ አባዜያችሁ ከላያችሁ ይታጠብላችሁ…ለሁላችንም ልቦና ይስጠን፡፡ አሜን!!!! በሉ፡፡



    በአረብ ሀገር ያሉ ሴቶችን ስም አጠፋህ የሚሉ ጥቂት ሀሞት ዘልዛላ ሰዎች ገጥመውኛል፡፡ ምንም አልላቸውም፡፡ ችግራቸው አንብቦ መረዳት ነውና ቃላት መቁጠሩን ሳይሆን አስተውሎ…ማገናዘቢያውን ህሊና ይስጣቸው፡፡ እነዚህን አንባቢዎቼ ልበላቸው? ወይስ ‹‹አንቡብልኝ ብዬ ሳስነብብ ለሰው መርዶ ይመስለኝና…›› የሚለውን ዜማ አስታዋሾቼ በአረብ ሀገር የሌለ ሰቆቃ እና ስም ማጥፋት ነው የምትጽፈው ባይ ናቸው፡፡ ይሄ ሁሉ አስተያየት የሚሰጠው አረብ ሀገር ኗሪ ለእኔ አግዞ ነው እየዋሸ ያለው ማለት ነው? እውነታውን ቢክዱ አልፈርድባቸውም፡፡ ለእኔ ሲሉ ከዋሹልኝም ተመስጌን የዚህን ሁሉ ሰው ፍቅር የሰጠኸኝ አምላክ፡፡ አያዩ አያዩምና እየሰሙ አይሰሙምና ልቦና ስጣቸው..አሜን!! ከኳታር የመጣ አንድ የግል መልዕክት እንዳበሰረኝ እየተሳደበ ያለው ልጅ /እዚህ ጋር የማንንም ስም ለመጥቀስ አለመፈለጌ የሰዎችን ሰብዓዊ ክብር ላለመንካት መሆኑ ይታወቅልኝ/ ስራውን እንዳላጋልጥበት በመፍራት እንደሆነ ተነግሮኛል፡፡ አንድ እህቴ የገጠማትን ገጠመኝ አታሎ እንዴት ለሁለት የውጭ ዜጎች ሊሸጣት እንደነበር ገልጻልኛለች፡፡ ታሪኩን በቀጣይነት ስለምጠቀምበት ለጊዜው ወደ ጀመርኩት ልሂድ፡፡



      መሸጥ የለመደ እናቱን ያስማማል….ነው፡፡ የራሳቸውን ገላ ከመሸጥ አልፈው ሌላው ገላውን እንዲሸጥ የሚደልሉ መኖራችውን አረብ ሀገር ያለ ማንም ኢትዮጵያዊ የሚያውቀው እውነታ ነው፡፡ ታዲያ ይህን ማለት ግን በአረብ ሀገር ያሉ ሴቶች በሙሉ ይሸረሙጣሉ ማለት አይደለም፡፡ በተደጋጋሚ እየገለጽኩ ያለሁት እውነታ ጥቂቶች ባራከሱት ስም ሁሉም እየተሰደበ ነው አልኩ እንጂ ሁሉም አንድ አይነት ነው አላልኩም፡፡ አልልምም፡፡ በጣም ስርዓት ያላቸው አንገታቸውን ደፍተው የሄዱበትን አላማ የሚያሳኩ ሞልተዋል፡፡ ቤተሰባቸውን ጥቂት ከማጉረስ አልፎ መሰረታዊ ለውጥ ያስከተሉ እንዳሉ አናውቃለን፡፡ ለፍቅረኛቸው አለያም ለትዳር አጋራቸው የገቡትን ቃል ጠብቀው የሚቆዩ በዋዛ የምናሰላቸው አይደሉም፡፡ ለነገ ህይወታቸው መመስረቻ የሚሆን ለፍተው የቋጠሩ አጋጥመውኛል፡፡ ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ ከምናያቸው የህዝብ ማመላለሻ ታክሲ ውስጥ ወደ ግማሽ የሚጠጋው አረብ ሀገር መጥተው በሰሩ እህቶች ለቤተሰብም ይሁን ለራሳቸው መተዳዳሪያ የተገዛ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡



   እንዲያውም ላባቸውን አንጠፍጥፈው፣ የደረሰባቸውን መከራ ተቋቁመው የሚኖሩ መኖሩ በጉልህ ሊጻፍ የሚገባው ነው፡፡ በዚህ አጸያፊ በምንለው ተግባር ተሰልፈው ያሉት 10 በመቶ የሚሆኑት እንኳን አይሆኑም፡፡ በእነዚህ ጥቂቶች ሁሉም ይሰደባል እያልኩ ነው፡፡ ከእነዚህም በመጥፎ ተግባር ላይ ከተሰማሩት ውስጥ ራሳቸውን ለውጠው ቤተሰባቸውን የለወጡ አሉ፡፡ በተጨማሪ አብዛኛዎቹ ወደው ሳይሆን ሁኔታዎች ናቸው የሚገፋፉዋቸው ባይ ነኝ፡፡ ለምሳሌ ከዚህ በፊት የጻፍኩት ታሪክ ላይ ማስተላለፍ የፈለኩት በዚህ አይነት ሁኔታ ተገደው ሊገቡበት ይችላሉ የሚል መልዕክት የሰነቀ ነው፡፡ ችግራቸው ካለፈ በኋላ የሚወጡ የመኖራቸውን ያህል ‹‹…የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም..›› ብለው ሌሎችን ሁሉ እየደለሉ የሚከቱ ብሎም የሚያቃጥሩ መኖራቸውን በአረቡ አለም ላይ ያለን ሰዎች እያየን ነው፡፡  እኔ ወደ የመን ከመምጣቴ በፊት የተደረገ አሁንም የሚደረግ አንድ ታሪክ ብተነፍስ ብዙ ያስረዳልኛል፡፡ ተንፍስ የምትሉ እጃችሁን አውጡ…እዛ ጋር ማነሽ ሁለት እጅ ማውጣት….አባባ ተስፋዬ ትዝ አሉኝ፡፡ እኛን ስርዓት ለማስተማር አትጋፉ..አንተኛው እዛ ጋር.. ሲሉ ዞረን እያየን ቁጭ በሉ እስኪሉን የጠበቅነው…ድካማቸውን፣ እኛን በስርዓት ለማነጽ ያደረጉትን ነገር፣ ብሎም ያደግንበት ስርዓትና ቤተሰባዊ ከበሬታ /መከባበር/ ዛሬ የት ጠፍቶ ይሆን? በሬድዬ ፋና አፋልጉኝ እናስነግር እንዴ?

  

     ወደ ታሪኬ ልመለስ…እዚህ አንድ ደላላ አለ፡፡ትውልደ ኢትዮጵያዊ ነው ይሉታል፡፡ ለዚህ ደላላ ወኪል ሆና የምትሰራው ሴትዬ ሳሪስ አካባቢ ነው ያለችው፡፡ የሴትዮዋ ልጆች የመን ውስጥ ከሰውዬው ጋር ሰራተኛ እያሉ ከኢትዮጵያ የሚያግዙትን ሴቶች ማስቀጠሩ ብቻ አላረካቸውም፡፡ የሚያዋጣ አዲስ የስራ መስክ ፈጠሩ፡፡ ወይም በኢህአዲጊኛ አባባል ለስራ ካላቸው ተነሳሽነት አዲስ የስራ ፈጠራ ፈጠሩ እንደበል? መሸጥ ጀመሩ፡፡ ስለጉዳዩ ያጫወተችኝ ዛሬ በኤች.አይ.ቪ ተለክፋ አንድ ልጇን ይዛ ወደ ሀገር የተመለሰች እህታችን ነች፡፡ ሀገር ከገባች ስድስት ወር ቢሆናትም ዛሬ ያለችበትን የጤና ሁኔታ አላውቅም፡፡ የመን ውስጥ ብቻ 7 ጊዜ አፖርሽን ማድረግዋን ስትነግረኝ 4 በግድ በተደረገ ወሲብ የመጣ ጽንስ ነው ያስወረደችው፡፡ በመጨረሻው ጊዜ ልክ የዛሬ አመት በ03/07/2011 የወለደችውን ልጅ ግን አግብታ ቢሆንም እርግዝናዋ ሲመጣ አስረጋዡ ሄደ፡፡ ወደማይቀረው አለም ነጎደ-ነፍስ ይማር፡፡ አሟሟቱ ድንገት ወይም አሁን ይዛ የገባቸውን ልጅ ልትገላገል አዋላጅ ፍለጋ ከሆስፒታል ሆስፒታል ተንከራተተች፡፡ ሁሉም ሊቀበሉ እና ሊያስተናግዱዋት አልፈለጉም፡፡ ሰበቡ የኤች.አይ.ቪ ተጠቂ ስለሆነች በሆስፒታላችን አናዋልድም ብለው ነው፡፡ በመጨረሻ UNHCR ቢሮው ቅድመ ክፍያ አድርጎ በብዙ መለማመጥ ሙተወከል የሚባል ሆስፒታል በኦፕሬሽ ወለደች፡፡

 

     ‹‹..እንኳን ማርያም ማረችሽ..›› ለማለት ስሄድ ደነገጥኩ፡፡ በብዙ ሰው ተከባ የማውቃት ልጅ ብቻዋን ተንጋላ ተኝታለች፡፡ ለወትሮው አጀበ ብዙ ነበረች ባሏ ሲሞት አጅሬው ነው የገደለው..እያሉ ጥቂት ሰዎች ርቀዋት ነበር፡፡ እንዲህ ብቻዋን ትቀራለች ብዬ ግን አላሰብኩም፡፡ ብዙ ሰው ስለምታውቅ ግርግር ይኖራል ያልኩበትን ሰዓት አሳልፌ መሄዴ ነው፡፡ ስገባ ጠላታችሁ ስቅቅ ይበል ተሳቀኩ፡፡ አብራኝ ሄለን የምትባል ጉዋደኛዬ /እህቴ/ አለች፡፡ ምንም ከጠያቂ የመጣም ሆነ ገዝታ ያስቀመጠችው የሚበላ የሚጠጣ ነገር ባለመኖሩ ባዶ እጄን በመግባቴ ይበልጥ ተሳቀኩ፡፡ እጄ ላይ ያለው ሳንቲም ከታክሲ ከተረፈ አንድ ደረቅ ዳቦ የሚገዛ ሽርፍራፊ ሳንቲም ብቻ ነው፡፡ ምን ላድርግ? በእርግጥ ቤት ያስቀመጥኩት ሳንቲም አለኝ፡፡ ቤቴ ግን ሩቅ ነው፡፡ ‹‹አልበር እንዳሞራ ሰው አድርጎ ፈጥሮኛል…›› ማለት ይሄኔ ነው፡፡ ብቻዋን ጥያት ወደ ቤቴ መሄድ እንደሌለብኝ ራሴን አሳመንኩት፡፡ ሄለን ከእኔ ጋር ሆስፒታል ማደር አትችልም፡፡ ጠዋት ስራ ስለምትገባ እንቅልፍ ይጥላታል፡፡ ሁለተኛ እህቷ ልትቆጣ ትችላልች፡፡



    ገንዘብ መያዝዋን ስጠይቅ 3.000 የየመን ሪያል እንዳላት ነገረችኝ፡፡ ተቀበልኩዋት፡፡ ብዙ ምስሎዎት በሀብታሚያ የተራመድኩ እንዳይመስሎት፣ ሶስት ሺህን ያህል እንዴት በቦርሳዋ ይዛ ትሄዳለች እንዳይሉ…በዶላሪኛ ሲቀየር ያኔ 15 አሁን 12 ዶላር ነው፡፡ 



    ወጣንና ሄለንን ታክሲ አሳፈርኳት፡፡ ለበሽተኛዋ የምትበላው እና የምትጠጣው ገዛዝቼ ስገባ ከተበደርኩት ሳንቲም ላይ ለራሴም ራሴ ራት ጋበዝኩት፡፡ ተመልሼ ስገባ ‹‹መጣህ?..›› አለች፡፡ አይኗ ግን እጄ ያነጠለጠለው ላስቲክ ላይ መሆኑን ሳይ ርሃብ ሸንቆጥ እንዳደረጋት ገምትኩና ፈጠንኩ፡፡ እንዳጎርሳት አልፍልግችም፡፡ የዚህ ሀገር ባህል አለ፡፡ ወንድ እና ሴት እንደፈለጋቸው አይሆኑም፡፡ ለዛ መሰለኝ እና ‹‹አንቺም የእነሱ ባህል ያጠቃሻል? ቀና ብለሽ መጉረስ አቅቶሽ የለ? ላጉርስሽ…›› አልኩና አጎረስኳት፡፡ አብልቻት ስጨርስ ቀስ በቀስ ወሬያችን ደራ፡፡ የመጣችው አሽጣል በሚባል ደላላ ነው፡፡ ስሟን መጥራት ያልፈለኩት ሳሪስ ያለች ሴትዬ 4000 ሺህ የኢትዮጵያ ገንዘብ አስከፍላ ላከቻት፡፡ የሴትዮዋ ልጅ እዚህ የመን ውስጥም ከአየርማረፊያ ድረስ መጥቶ ተቀብሎኝ ደላላው ቢሮ ወሰደኝ፡፡



    ይህን ስሰማ በፊት ካሰባሰብኳቸው መረጃዎች ውስጥ አንዱን ሊያጠናክር የሚችል መረጃ ትሰጠኝ ይሆናል ብዬ ጥያቄዬን ማከታተል ጀመርኩ፡፡ ቢሮው ውስጥ ማደሪያ አለ እዛ ሲያሳድሩ እና ኮንትራት ላመጡለት ሰው እስኪያስረክቡ ሌላ ግፍ ይሰራሉ ይባላል እውነት ነው? እፍረት ፊቷ ላይ ክልብስ ሲል በቅስፈት አየሁት፡፡ የደረሰባት ነገር እንዳለ ገመትኩ፡፡ ማበረታት ያስፈልጋል እና አንዲት ልጅ የደረሰባትን ነገር እንደነገረችኝ ስሟን ሳልነግራት አወጓኋት፡፡ ለእኔም እንዲሁ ነው የገጠመኝ አለችና ጀመረች፡፡ በል በለው…እያልኩ አሰፋ ማሞ ወጣቱን ፋይዳ ለሌለው እልቂት እንደከተተው እኔም አሷን ወደማናዘዙ ገባሁ፡፡ በእየአንንዱ ንግግሯ መካከል ማደፋፈር ግድ ነበር፡፡



   ‹‹..ከኤርፖርት ወስዶኝ ቢሮው ስንገባ ከምሽቱ 5 ሰዓት ተኩል ነው፡፡ በቢሮው አቋርጦ ቁልቁል በደረጃ ወረድን አስጠሊታ ሽንት ቤት ይመስላል፡፡ ማደሪያዬን አሳይቶኝ ሲመለስ ክፍል ውስጥ ያለውን ሁኔታ ሳላጤን በጨለማው እጅ አረፈብኝ፡፡ ልጮህ አፌን ስከፍት ሽሽሽሽ… የሚል ነገር ሰማሁ፡፡ የሚሆነውን ጠበኩ..ብቻ የሚሰሩት ስራ ተወኝ፡፡ አረመኔዎች ናቸው፡፡ እናታቸው እዛ ባራችንን በልታ…እ!!...›› አለችና እልኋን በተቃጠለ አየር መልክ ለማስወጣት ስታምጥ አየኋት፡፡ ከዚህ ሁኔታዋ ለመረዳ የቻልኩት በሌሎቹ የደረሰ ሁሉ እንደደረሰባት ነው፡፡ ግን የማወቅ ጉጉቴ ንሮ..ንሮ..በየአንዳንዱ ንግግሯ መሀል እያደፋፈርኩ፣ ሰምቼዋለሁ እያልኩ አውጣጣኋት፡፡ ቀፋፊ በሲሚንቶ የተሰራ አልጋ መሳይ መደብ ላይ በሶስት ቀን ውስጥ ሶስት ሰው እንደተገናኛት እፍረት በሸበበው ቁርጥርጥ ቃላት አሰማችኝ፡፡ እነዚህ ኮንትራት ስራ እያለች የምትልከው የሳሪሷ ሴትዬ ልጆች ያልሰሩት ግፍ.. ያላለቀሰችባቸው የሀበሻ ሴት የለችም፡፡ ካራቸው ለራሳቸውም ስሜት መተንፈሻ ያደርጋሉ የሚል ነገር ብሰማም ይህን እውነት ያሉ ሴቶች ግን አልገጠሙኝም፡፡ ለኮንትራት ስራ የሚሄዱ ሴቶች ኤች.አይ.ቪ ተመርምረው ስለሆነ ያለሀሳብ የግፍ ወሲብ ለመፈጸም ገንዘቡን የሚያዘንብ አረብ በመብዛቱ ወገናቸውን መሸጥን ለአረቦቹም አስተማሩ፡፡



     ዋናውም ሰውዬ ጀመረ አሁንም ይሰራል፡፡ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኞች ግን ማሀረቤን ያያችሁ አላየንም እየተጫወቱ የጠገበ ውሻ አይጮህም ብሂልን ሲተገብሩ የየመን መንግስት ሁኔታውን ደርሶበት ዳግመኛ ወደ የመን እንዳይገቡ አገዳቸው፡፡ ኢትዮጵያ ሲገቡ ግን የጠየቃቸው አካል የለም፡፡ ለወገኑ ተቆርቋሪ የሆነው መንግስት በድብቅ ሽልማት ሳይሰጣቸውስ ይቀራል? ስንዝር ያለተራመደ ሁሉ ሲሞት መቃብሩ ላይ በጉልህ ‹‹..ሩጫዬን ጨርሻለሁ!!›› ተብሎ እንደሚጻፍለት ከንቱ ነው እዚህ ያለ ኤምባሲ፡፡ ሀሺሽ ይዛ ሀገራችንን ቅሌት ውስጥ እንደከተተችው ዲፕሎማት በርበሬ እና የመን ውስጥ ክልክል የሆነ ነገር /መጠጥ/ ከመነገድ የዘለለ ስራ የላቸውም፡፡ ወገን ተበደልኩ ጥቃት ደረሰብኝ ብሎ ወደ ኤምባሲ ሲሄድ መልሰው ለደበደቡ እና ጉዳት ላደረሱ ሰዎች መልሶ ማስረከቡ ‹‹እኛ ለገረድ አልመጣንም!..›› እያሉ መዘባነናቸው የታወቀ እና በስደተኛው ዘንድ የሚታወቅ ነው፡፡



    በአንድ ወቅት ኮሚኒቲውን በሊቀመንበርነት የሚመራው ሰው ሁንም አለ፡፡ ችግር ደርሶባት አድኑኝ ብላ ወደ ኮሚኒቲ የሄደችን ሴት አሳልፋችሁ ስጡኝ ያሉ የመናዊያን ትንሽ ገንዘብ አጎረሱት፡፡ አታስቡ የመን ሙስና ወንጀል አይደለም፡፡ በቃ!..በህይወት ማላውቃቸው አያቴ ውሻ በበላበት ይቾሀል ይሉ ነበር..ሲባል የሰማሁትን ተረት እውነታተገበረው አሉኝ፡፡ በደረሰባት ድብደባ እና ስቃይ ጭንቀት ውስጥ ገብታ እሳቤቀዋ ትንሽ ተዛብቶ ሳለ ወደ አሰሪዎችሽ መመለስ አለብሽ ብሎ ጥብቅና ለአረቦቹ ቆመ፡፡ ሊመልሳትም ቆርጦ ወሰነ፡፡ ልጅት ራሷን እዛው ኮሚኒቲ ውስጥ በገመድ ሰቀለች፡፡



    አሁን በቅርቡ ወዳጄ እና የሞያ ባለደረባዬ ነብዩ ሲራክ ‹‹…በጅዳ ቆንስል ግቢ የውሃ ገንዳ ሰው በላ ! ኢትዮጵያዊቷ ሞታ ተገኘች!..በሚል ያቀረበውን ዘገባ እንመልከት እስኪ..ልብ በሉ ይህች ኢትዮጵያዊ ሞታ የተገኘው በጅዳ ቆንስል ኢንባሲ ግቢ በሚገኘው ገንዳ ውስጥ ነው፡፡ አሁን እኔ ያለኳችሁም በየመን ኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ውስጥ ነው ራሷን ያተፋችው፡፡ አለም ደቻሳ በቤሩት ቆንስላ በር ላይ ነው ያን የመሰለ አሳፋሪ ተግባር የተፈጸመባት፡፡ ሌሎችም የደረሱ በደሎችን መጥቀስ እችላለሁ፡፡ ይህን ይህን ስናይ የኢትዮጵያ መንግስት ከኋላ ቆሞ ‹‹እሰይ ስለቴ ሰመረ..›› ሳይል ይቀራል፡፡ በወገን ደም የቀለደ መንግስት እህቶቻቸውን የሚሸጡ ደማቸውን የሚመጡ ትውልዶችን የሚያበረታታ መንግስት አሁንም ከሳዑዲያ ወደ የመን የሚመጡ ኢትዮጵያዊያንን እያሰቃየ ነው፡፡



  ወደ ወዳጄ ነብዩ ሲራክ  ዘገባ ልመለስ…ወቅቱም ሌሊት በግምት 315 አካባቢ መሆኑን ለማዎቅ ችያለሁ፡፡ የዚህች እህት ሞታ መገኘት እንደሰሙ ምክትል ቆንስል ሸሪፍ በቦታው በመገኘት የአደጋ ጊዜ ፈጥኖ ደራሽ ፖሊስ ሬሳውን ከጉድጓድ አውጥተው ነብሷ ከስጋዋ ያልተለየውን እህት ለማዳን ሲታገሉ የአይን ምስክር ነበሩ፡፡ብሏል ነበዩ…በሆዳቸው ባለተረፈች…ባለተረፈች ሳይሉ ይቀራሉ?ሞቷን አይተው ለመርካት ይሆን ቦታው የተገኙት? የመጥፎ ስራቸውን ውጤት ፍሬውን ሊያቸጭዱ መሆን አለበት፡፡

   

     እንደታዘብኩት በወቅቱ የነበሩት መርማሪዎች እጅና እግሯ ታስሮ እያለ በገንዳው ውስጥ ገብታ ስለሞተችው ስለዚህችው ልጅ አሟሟት ዙሪያ ግራ በመጋባት መስቀለኛ ጥያቄዎችን ሲጠይቁ በቦታው ነበርኩ፡፡ የወቅቱ የቆንስሉ ዘበኛ የነበሩት አቶ ገሬ ስለ ተፈጠረው ሁኔታ ማብራሪያ ሲሰጡም ሟች ገና ከምሽቱ በግምት 400 ሰአት አካባቢ ወደ ካፍቴሪያው ግቢ እንደመጣችና የዓዕምሮ ህመምተኛ በመሆኗ ከመጮህ በቀር አድራሻና ስሟን ባለመናገሯ እጅና እግሯን በማሰር ወደ ጊዜያዊ መጠለያው እንዳስቀመጣት ተናግሯል፡፡ ከዚያም አቶ ገሬ ሲያስረዳ ከምሽቱ 200 አካባቢ ግቢን በሙሉና ገንዳውን ጨምሮ ከሰወች ጋር በመሆን ቢያፈላልጋትም የውሃው ገንዳ ገበድ ያለ ብረት መዝጊያ ገርገብ ብሎ እንዳገኘው በመብራት ቢመለከትም ምንም ነገር እንዳላየ ገልጿል፡፡ አቶ ገሬ በማከል ሲናገር ብዙም ሳይቆይ ግን ልጅቷ ከገንዳው ገብታለች ብሎ በመጠራጠሩ ገንዳውን ለማስፈተሽ ለፖሊስ ጥሪ ማድረጉን ተናግሯል፡፡ ከዚያ ፖሊስ መጥቶ ገንዳው ሲፈተሽ የዚህች ሬሳ ተገኝቶ በፖሊሶች እንደወጣ በቦታው ተገኝቸ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ በመጨረሻም የቆንስሉ ዘበኛ ለጥያቄ ወደ ጣቢያ መወሰዳቸውን ተመልክቻለሁ፡፡ እኔን ጨምሮ ዲፕሎማቶችና የኮሚኒቲ ሃላፊዎች ንጋት ላይ ወደ የቤታችን ተመልሰናል፡፡


          ይህ በእንዲህ እንዳለ በርካቶች ያበዱ የኮንትራት ሰራተኞች በቆንስሉ ግቢና በጊዜያዊው መጠለያ ከአርባ የማያንሱ በአሁኑ ሰአት እንደሚገኙ ከቆንስሉ ያገኘሁት መረጃ ያስረዳል፡፡ በቆስል ከዚህ በፊት ተጠልለው የነበሩ አንዳን እህቶች በቆንስሉ በተጠጋንበት ቆንስል መስሪያ ቤት ዘበኛ አቶ ገሬ በሴትነታቸው ሊያጠቋቸው እስከመደብደብ እንደደረሱ ለቆንስል መስሪያ ቤቱ መከሳቸውን በመረጃ ማቅረቤ አይዘነጋም ፡፡ ዛሬ በዚሁ ጉዳይ ያነጋገርኳቸው አምባሳደር መርዋን ከዚህ በፊት ስለተፈጸመው ጥፋት ጠይቄያቸው አስተዳደራዊ እርምጃ እንደተወሰደ ገልጸውልኛል፡፡

By: Nebiyu Sirak…. ›› ይላል፡፡ ልብ ያለው ልብ ይበል እነዚህ ከአርባ ባላይ ሴቶች ወደው ለመዝናናት ያበዱ ናቸው የሚል ይኖራል?