Tuesday, May 14, 2013

የኢትዮጵያዊያኑ ስቃይ በየመን

የኢትዮጵያዊያኑ ስቃይ በየመን
በየመን ያሉ ኢትዮጵያያንን መንግስት ራሱ ሸፍጥ እየሰራባቸው ነው ሲል አል-ተውራ ጋዜጣ አጋለጠ
                                                                  ግሩም ተ/ሀይማኖት
 ሰሞኑን ስደተኛውን ወደ ሀገር ለማስገባት ግርግሩ ጦፏል፡፡ ብርሃን ሊወጣ እንደሆን የሚያስመስል ግርግር አለ፡፡ ለይምሰል የአንድ ሰሞን ሩጫ እንዳይሆን እንጂ…ደግሞም ነው፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትን የሚወክለው ኤምባሲ በዚሁ መጓጓዣ ወረቀቱን (ሊሴፓሴ) በማውጣቱ በኩል ይቀጥላል አይቀጥልም አይታውቅም፡፡ አሁን ግን ተግቶ ወደ ሀገር እንዲገቡ ማድረጉን ወገኖቹ ለይ የተፈጸመውን ወንጀል እንደማድበስበስ የሚቆጠርበት ሁኔታ እንዳለ አንዳንድ የመናዊያን ጋዜጠኞች እየዘገቡ ነው፡፡ ከዚህም አንዱ ከስደት ተመላሾቹ ላይ በኢትዮጵያም ሆነ በየመን መንግስት ግፍ እየተፈጸመ መሆኑን የመን ውስጥ የሚታተመ አል-ተውራ በመባል የሚታወቀው የመንግስት ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ ይህ አል-ተውራ የተባለው የመንግስት ጋዜጣ የኢትዮጵያዊያኑን ሬሳ በየመንገዱ ወድቆ ይታያል፣ አይተናልም፡፡ ግማሹ ቀባሪ አጥቶ ይሸታል…›› በማለትም ስለሁኔታው ጠንከር ያለ ዘገባ አስነብቧል፡፡ ጋዜጣው በገባው እንዳለው…

      የጋዜጣው ዘጋቢ ከመግቢያው ጀምሮ ያስቀመጠው ነገር የሚገርም እና የሚያሳዝን ነው፡፡ በመግቢያ ፀሁፉ ላይ…አባስ ሰዒድ የተባለ ጽዳት የሚሰራ ኢትዮጵያዊ ከስድስት ወር በፊት በሶማሊያ በኩል በባህር ተሻግሮ ወደ የመን ስለገባበት ሁኔታ ሲነግረው ‹‹እናንተ ሀገር ማንም በርሀብ የሚሞት የለም፣ ኢማን አለ፡፡ አዛኞች ናቸው፣ የሰው ክብር አለ..ምናምን…እኛ ሀገር ግን..ብሎ አነጻጸረልኝ፡፡ ዛሬ አባስ ይህን የማቀርበውን ዘገባ ስታይ ኢማን አለ? ደጎች ናቸው? ፈሪሀ አላህ ያላቸው ናቸው ያልካቸው ሰዎች የሰሩትን ስታይ ምን ትለኝ ይሆን? እኔስ እንዴት ብዬ በሙሉ አይኔ አይሃለሁ?..ምን አንገት የሚያቀና ነገር ሰሩና?..›› እያለ በሰፊው ሀተተ፡፡ አባስ የተባለውም ሆነ እሱን መሰል አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ስደተኛ የስብዕና እና የማንነት ማጣት ችግር የተበተባቸው ናቸው፡፡ መስለው ለመኖር የሐገራቸውን ክብር አውርደው፣ የራሳቸውን ማንነት አዝቅጠው ለህሊናቸው ሳይሆን ለሆዳቸው ያወራሉ፡፡ ራሳቸውን አንቋሸው ያልሆነውን ይክባሉ ማንነትን ማዝቀጥን የመሰለ አስጠሊታ ነገር የለምለ፡፡ እኔ ያልሆነውን ሆነ ብለው የሚክቡትን የምጠላው ልክ እንዲሁ ገብተውም ሀገር ውስጥ ያለውን በዚሁ አመለካከታቸው ነው የሚሰብኩት፡፡ ለዚህ ጋዜጠኛ ያወራለት ሀባስም ከሚለው(ከካባት፣ ከቆለላት) በተለየ መልኩ ናት የመን፡፡

   ‹‹..እናንተ ሀገር ማንም በርሀብ የሚሞት የለም እኛ ጋር ግን…›› ሲለው ምን እንደሚቀጥል አስቡት፡፡ እኛ ሀገር እየረገፍን ነው..፡፡ እውነታው ግን ሳያቃት በካባት የመን ውስጥ ከ7 ሚሊዮን በላይ የዕለት የምግብ ሽፋን የሌለው በቀን አንዴ የሚበላ ህዝብ የያዘች ሀገር ነች-እንደአለም ጤና ቢሮ ገለጻ፡፡ አዛኞች፣ የዋሆች ናቸው የሚለውም ቢሆን ከከተማ ውጭ ያለውን ነዋሪ የሚገልጽ ነው፡፡ በእርግጥም አብዛኛው ህዝብ ጥሩ ነው፡፡ መጥፎ ለመሆን ሲፈልጉ ደግሞ ሴጣን ራሱ በጭካኔያቸው የሚቀናባቸው አረመኔዎች ናቸው፡፡ የሰው ክብር አለ እናንተ ሀገር ላለው ክብር መሰደብ፣ መዋረድ የሆነለት አባስ ኢትዮጵያዊ መሆኑን ተጠራጠርኩ፡፡ የሚገርመኝ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የሚባሉ ሁሉ ችላ ያሉት ሀገር ጭቆና እና የቀለም መድልዎ የሚካሄድበት ለመሆኑ ካድም ተብለው በሚጠሩት ጥቁሮች ላይ የሚደረገው በቂ ማስረጃ ነው፡፡ ይህን አይነት ነገር ሳለ ለመኖር ሲባል ብቻ ያልሆነ የሚቀላምዱት አይነቶች ናቸው ጋዜጠኛውን ያሳፈሩት፡፡ ወደ ዋናው ታሪክ ስንሄድ…    

    ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ከ1000 በላይ በአጋቾች የታገቱ ስደተኞች ቢፈቱም ህጋዊ የሆነ ነገር አልተደረገላቸውም፡፡ በሀረጥ እና ዙሪያው አካባቢ በርካታ ጊቢዎች ውስጥ በደላሎች እየታገቱ ስቃይ ሲደርስባቸው የነበሩትን 535 ሰዎች ድንበር ጠባቂዎቹ ከመከላከያ ሰራዊት ጋር በመሆን ነጻ አውጥተዋቸዋል፡፡ ግን መንግስት ይህን ሁኔታ በምስጢር እንዲያዝ አድርጓል፡፡ አል-ዘሀራ የተባለ አነስተኛ መንደር ውስጥ በአጋቾቹ የተያዙት 48 ኢትዮጵያዊያን አሁንም ከአጋቾቹ ማስለቀቅ እንዳቃተቸው ነው፡፡ ካለፈው ወር ጀምሮ እስካሁን ሊያስለቅቋቸው ያልቻሉት የተደራጁ እና ከመንግስት ሰራዊት የተሻለ ትጥቅ ያላቸው በመሆናቸው ነው፡፡ አግተው ከያዙዋቸው  ኢትዮጵያዊያ ከቤተሰባቸውም ሆነ ከወዳጅ ዘመዳቸው እንዲያስልኩ የሚጠይቁትን 1500 የሳዑዲ አረቢ ሪያል ካልተላከላቸው አይለቋቸውም፡፡ እንዲላክላቸውም ሲሉም ነው የሚያሰቃዩዋቸው፡፡
  
       ጋዜጣው በዘገባው እንደገለጸው እዚህ ታግተው ከቀሩት ውጭ ካስፈቷቸው ውስጥ ሴቶቹ በአጠቃላይ ተደፍረዋል፡፡ ለወራት ያህል ዘግተው ይዘው እንደ ፈለጋቸው ሲጫወቱባቸው በቀን ከ20 ጊዜ በላይ የሚደፈሩበት ጊዜ እንዳለ ሁሉ ገልጸዋል፡፡ አባቱ ማን እንደሆነ የማታውቀው ህጻን የያዘችም አለች፡፡ (ከዚህችኛዋ ጋር 7 ይሆናሉ አባቱን የማያቁት ልጅ በዚህ መንገድ በመደፈር ብቻ ለመውለድ የበቁ እና ያወኳቸው፡፡) ግማሾቹን ደግሞ ለሽርሙጥና ሲያስሯቸው እንደነበር ጋዜጣው በአጽንኦት አስፍሮታል፡፡

      በአካባቢው ላይ እየተዟዟርን በአየንበት ሰዓት የኢትዮጵያዊያኖቹ ሬሳ በየመንገዱ ወድቆ ይታያል፡፡ በመደፈርም በዱላም ይሞታሉ፡፡ መንገዱ ላይ በርሃብ እና ጥም እየሞቱም ይታያሉ፡፡ ዘይት አፍልተው ይደፉባቸዋል፡፡ ላስቲክ በእሳት እያቃጠሉ ሰውነታቸው ላይ በማንጠባጠብ ይጫወቱባቸዋል፡፡ በርሃብ ተይዘው በውሃ ጥም ደርቀው አሳዛኝ ገጽታ ተላብሰው ማየት የተለመደ ነው፡፡ ግን ይህ ሁሉ ኢምንት ነው፡፡ አንዲት ጠብታ..ከሰማሁት ካየሁት የተናገርኩት አንድ ፐርሰንቱን ነው፡፡ ይህ ሁሉ ሲደረግ መንግስትም ያላወቀ መስሎ ዝም ብሏል፡፡ በይበልጥ ግን መረጃው ያለው የተለየዩ እርዳታ ድርጅቶች ውስጥ ነው፡፡ እነሱ ጋር እውነቱ አለ፡፡ በጣም ብዙ ማስረጃዎችም አሏቸው፡፡ ግን ሊያወጡት አይፈልጉም፡፡ በጣም ሰቅጣጭ እና የተደረገባቸው ድርጊት የሚቀፍ ስለሆነ ህዝብ እንዲያውቀው አልተፈለገም፡፡ አይፈልጉም፡፡ አሁንም ቢሆን የበለጠ መረጃ ያለው እነሱ ጋር እንደሆነ አበክሬ እናገራልሁ፡፡ ጉዳዩን ግን ደብቀውታል፡፡ ይህ ደግሞ ጉዳቱ እንዲቀጥል አድርጓል፡፡

    እንደእኔ እንደእኔ ከሆነ ለምንድን ነው የሚደብቁት የሚለውን በሰፊው እንይ ከተባለ ብዙ ምስጢር አለው፡፡ ሀገሪቱ ውስጥ ያሉት በልምምጥ ከመሆኑ የተነሳ ከዚህ ውጡ እንዲባሉ አይፈልጉም፡፡ ማድረግ የሚገባቸውን አለማድረጋቸውም ሌላው ህፀፃቸው ነው፡፡ የስደተኛው መብት ተገፎ ይህን ያህል ጭካኔ ሲፈጸም መጠየቅ ያለባቸውን አካል እንኳን ለምን ይህ ይሆናል ብለው አለመጠየቃቸው ስራቸውን ዘንግተው በመሆኑ ይህ ሁሉ የደረሰ ማንን ተጠያቂ ያድርጉ? ስለዚህ ምስጢር ጠብቀው ማቆየት ይፈልጋሉ፡፡ ይህ የእኔ ሀሳብ ነው ጋዜጣው የገበው ደግሞ በጣም የሚቀፍ ሁኔታ መሆኑ እና ሰዎች ቢያዩት የሚሰቀጥጥ ነው ከሚለው አንጻር ነው፡፡ ሌላው መንግስትን ላለመወንጀል ነው ብሏል፡፡

     ባለፈው ሀሙስ ሁሴን አሊ ሀምዛ የተባለ ሰው ተያዘ፡፡ የ31 አመቱ ሁሴን 210 ኢትዮጵያያንን ይዞ ነው ያገኙት፡፡ 10 ልጆች ሲሆኑ ወደ 63 ሴቶች ነበሩ፡፡ ሁሉም ላይ ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ አንድም ሳይቀር ምልክት አለባቸው የተጎዱበት፡፡ የተገረፉበት፣ በእሳት የተቃጠሉበት ምልክት ሰውነታቸው ላይ በየቦታው ይታያል፡፡ ያለ ምንም ማንገራገር ወደ ሚግሬሽን ነው የወሰዷቸው፡፡ አጋቹም እስር ቤት ገባ አሉ፡፡ ሌሎችም የተያዙ ነበሩ ባለስልጣኖቹ ስም መጥቀስ አልፍልጉም፡፡ ምክንያቱንም ሊከሷቸው አይልጉም፡፡ ሌላው ቀርቶ ይሄ ሁሉ የተያዙት በወታደሮቹ ጉብዝና አይደለም፡፡ በኢትዮጵያዊያኖቹ የተለያየ ጥረት ነው፡፡ ይህ በህገ-ወጥ አጓጓዦች የታገቱት ስደተኞችን የማስለቀቅ ስራ የሚከናወነው ወደ ከሰዓት ላይ አጋቾቹ ቅመው መርቀን በሚሉበት ሰዓት ነው፡፡ ሀረጥ ሀጃ የሚባለው አካባቢ 160 ሴቶች እና ህጻናት ያሉበት ታጋቾች ተለቀዋል፡፡

    ይሄንን መከላከያ ሚኒስቴር እንኳን መግለጫ አልሰጠም፡፡ አሳፈራቸው፡፡ በየጊዜው በየቀኑ፣ በየቦታው የሚለቀቀውን ቁጥር ሲያዩት መግልጫ ማውጣት አሳፈራው፡፡ ባለፈው ሳምንት ብቻ 535 ሴቶች እና ህጻናት ያሉበት የኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ሀረጥ አካባቢ አስፈትተዋል፡፡ ግን አልተናገሩም፡፡ ዜና ሊቀርብ ተዘጋጅቶ ሳለ ከሰዓት ያነሰ ጊዜ ሲቀረው ስበው አስቀሩት፡፡ ማንኛውም ሚዲያ እንዳያወራው.. እንዳይገልጸው ደበቁ(ከለከሉን)፡፡ /ልብ ይባልልኝ ወዳጆች ይህ መንግስት የከለከለውን መረጃ  ለህዝብ መታገዱንም ሆነ መከልከሉን የሚነግረን አል-ተውራ (ህዝባዊ) የተባለው የመንግስት ጋዜጣ ነው፡፡   

    እንዳይተላለፍ የከለከሉበትን ምክንያት ስናይ ደግሞ በየጊዜው የሚለቀቁት ታጋቾች ብዙ ስለሆኑ እፍረት ነው፡፡ እነዚህ የሰው ልጆች ላይ የተፈጸመው ነገር አውሬ ላይ እንኳን ሊደረግ የማይገባ በመሆኑ ተሰምቷቸው፣ ራሳቸውን  እንኳን ይቅር እንደማይሉ ተሰምቷቸው..በይሉኝታ፣ በእፍረት…ይሆን? ሲፈጸም ዝም ብለው ያዩት አሰቃቂ ድርጊት እንኳን ኢትዮጵያዊያኑ ራሳቸውም ለራሳቸው ይቅርታ የማያስደርግ ነው፡፡ አሰቃቂ ነገር በሀገራቸው ውስጥ መሰራቱ አንገታቸውን አስደፍቷቸዋል፡፡
 
     /ይህ ብቻ ነው ብሎ ማሰብም አይቻልም፡፡ ከዚህ ድብቅ መግለጠጫ ያለተሰጠበት ወንጀል ጀርባ ብዙ ነገር አለ፡፡
1. እነዚህ ሰዎች የሚሰሩትን ጭካኔ ለመደበቅ (ለማጥፋት)
2. ከመንግስት የሚጠበቀውን ሀላፊነት ያለመወጣት ችግር ፣ችላ ማለት..ለመደበቅ
3.በመንግስት ችላ ባይነት የስቃይ እና የወንጀል ቦታ በመሆኑ አካባቢው
4.መንግስትም፣ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትርም፣ በእምነቱም፣ በህጉም ፊት ችላ ብለውት በሀገሪቷ ወንጀል  
    የሚፈጸምበት ቦታ መሆኑ አሳፍሯቸው
5. ከራሳቸው ሀላፊነቱን ለማውረድም ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች እንዳይከሰሱ እና በህግም የጥፋታቸውን እንዳያገኙ ችላ አሉ፡፡ ለአፋኞቹ መደበቅ እና ሽፋን ለማድረግ እና ህግ ፊት እንዳይቀርቡ በሚያደርጉት ጥረት አስቀያሚ ሌላ ወንጀል ይሰራሉ፡፡
   
      አፋኞቹ በረሃ ውስጥ እንስሳ እንደሚያድን ሆነው እያደኑ ገንዘብ ከቤተሰባችሁ አስልኩ በማለት የሚያሰቃዩት፡፡ ያስፈቷቸውን እስረኞች መሀወር፣ መላሂጥ፣ ምስራቅ ሀረጥ፣ ሰብስቧቸው አስገቧቸው፡፡ ከ50 አፋኞች ጋር ነው የገቡት፡፡ከእነዚህ ውስጥ 9 ኢትዮጵያዊያን ናቸው፡፡ ሁሉንም ወደ ሰነዓ ኢሚግሬሽን አመጧቸው፡፡ የቀሩትንም ወደ ሀገራቸው ሊመልሷቸው ፕሮሰስ ጀመሩላቸው ፡፡ ግን ይህ ነው ህግ?.... በማለት ጋዜጠኛው ህሊናዊ ሙግት የሚፈጥር ኢትዮጵያዊያን ልንጠይቀው ይገባን የነበረውን ጥያቄ ያቀርባል እንሆ፡-

  ‹‹ …ግን ይሄ ነው ወይ ህግ? እንደዚህ ከተጎዱ በኋላ ያለምንም ፍትህ በቀላሉ ወደ ሀገራቸው መመለስ ውጤት ነው? ሀቁ ይህ ነው? …ያፈኗቸው እንዲህ የጎዷቸው፣ አካላቸውን ያጎደሏቸው ለፍትህ ሳይቀርቡ ውጤቱ ሳይታወቅ እነሱን ማሳፈር ማስረጃውን ማራቅ ነው፡፡ በትንሹ የጎዷቸውን፣ ያሰቃዩዋቸውን ለህግ ሳያቀርቡ የሰው ልጅ ክብር ባለው ሁኔታ እንኳን ትንሽ ሳያርፉ እና ምንም ሳይደረግላቸው ወደ ሀገራቸው መመለስ አግባብ ነውን? ባይሆን እንኳን ለእየአንዳንዳቸው ለተጎዱበት 500 ዶላር ለእጃቸው ማገገሚያ ካሳ ሳይደረግላቸው መሸኘት ከእምነትስ አንጻር ልክ ነው? ይሄን ለማድርግ ባይቻል እንኳን ከሀጃ ክ/ሀገር ባጀት ተቀንሶ ሊሰጣቸው ይገባ ነበር፡፡ በእነሱ ክልል በእነሱ ሰዎች የተፈጸመባቸው ናቸው እና በእምነት እንኳን ካየነው ትንሽ ሀጢያታቸውን (ወንጀላቸውን) ለመቅረፍ ይረዳቸው ነበር ብሏል፡፡
    ስለእነሱም የሚጠይቅ አካል ባይኖር ዝም መባሉ ልክ ነው ወይ? የሚለውን ስናይ ትክክለኛ ነገር ነው፡፡በእርግጥስ አካላቸው ሁሉ ጎሎ በባዶ እንዲመለሱ ሲደረግ በዝምታ ከመቀበል ውጭ ማንስ ምን አለ? ሰብሳቢ የሌለው ዜጋ……

Wednesday, May 8, 2013

ግንቦት አንድ፣ አድባርና ትዝታው ዛሬ ላይ ሆኜ…

ግንቦት አንድ፣ አድባርና ትዝታው ዛሬ ላይ ሆኜ

                በግሩም ተ/ሀይማኖት
   ስሞኑን ሁሉም ስለ ግንቦት ልደታ ብዙ ብለው እኔም ትዝታዬን አንጎዳጉጄ ዝምታዬ ውስጥ በዝምታ አልጎምጉሜ ዝም ብዬ ነበር፡፡ ታዲያ በስደት ንፍሮ ቀቅሉ ጎረቤት ሰብስቡ ልል ነው? ለመሆኑ ኮንደሚኒየም ላይ አድባር እንዴት ይሆን? ምነው ባየሁ ኖሮ…ለነገሮ ባየሁ ብሎ ነገር የለም፡፡ አላየሁማ ደግሞም ለማየት መመኘትም ብዙ ደግ አይደለም፡፡ የስንቱን ናፍቆት እና ምኞት ተሸክሜ ልኖር ነው፡፡ ስለዚህ ነው ዝም ብዬ በውስጤ ያልጎመጎምኩት፡፡ ግና ዝም ብልም፣ ልርሳህ ብለውም እንድረሳው ያላደረገ አንድ ትዝታ ቀስቃሽ ፎቶ የለጠፈች ዝምታ አቋራጭ ልጅ እንድጫጭር አድርጋኛለች፡፡ ሸዋ ወልዴ ከላይ ያለውን ፎቶ ለጣፊዋ ነች፡፡ በስደት ቤይሩት ቢሆንም ያለችው በዓሉን በስደት ያሉበት ቦታ እንዴት እንዳከበሩት በምናቤ እንድቃኝ አድርጋኛለች፡፡ እንዲያውም አብሬያቸው ቁጭ ብዬ ቡናውንም እነሱ በአካል እኔ በምናብ ጠጥተናል፡፡ ሸዋ ካለች በኦርቶዶክስ ዙሪያ ያሉ ነገሮች መፈለግ ይቀላል፡፡ ስደት ነኝ ብላ የያዛት ነገር የለም፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስርዓታዊ መንገድ የተዘጋጀ መንፈሳዊ ፊልም በስደት ሀገር ሆና ሰርታለች፡፡ አሁን ደግሞ እኔ ላይ በግንቦት ልደታ ትዝታ ዙሪያ ፊልም ሰራች፡፡ እግዚአብሄር አብዝቶ ይባርካት፡፡ እናንተም ላነበባችሁት ይህ ፅሁፍ መነሻ ነች እና መርቋት፡፡ እናንተ እሷን እስክትመርቋት እኔ ወደ ወጌ ላምራእኔን ግን ስለማትምርቁኝ እራሴን መርቄያለሁ፡፡ እግዚአብሄር ይስጠኝ!!!

       በዘልማድ ‹‹አድባር›› ይባላል ግንቦት አንድ ቀን የሚከበረው የግንቦት ልደታ፡፡ እምቤታችን ማሪያም የተወለደችበት ቀን ነው፡፡ ታዲያ ይሄ አድባር የሚለው ነገር መቼ እንደ ተጀመረ እና ለምን እንደሚባል ከፍተኛ ጥናት የሚጠይቅ ነው፡፡ እኔ ደግሞ እንደምታውቁት ከፍተኛ ጥናት የሚጠይቀውን ቀርቶ ከክፍል ክፍል የሚዞርበትን ሚጢጢ ጥናት አላጠናም፡፡ ስነፍ ነኝ:: ዛዲያ በእዛው ጎበዝ እንድትሆን አትሳልም ነበር እንዳትሉኝ አደራ፡፡ አታስዋሹኝ እና ዶሮ ይመስል ስለት ነገር እጠላለሁ፡፡ ስለት ለው ነገር አልወድም..

    ከፍተኛ ጥናቱን ትቼ ባለችኝ ትንሽ መረጃ መሰረት የማስታውሰውን ላውጋችሁ፡፡ ማጣቀሻ ዋቢ መፀሐፍት ቢኖሩ በደንብ ባወጋኋችሁ ነበር፡፡ የግንቦት ልደታን ከቤት ወጥታችሁ ጊቢ ውስጥ ቡና አፍልታችሁየሚል የኦርቶዶክስ ስርዓት /ቀኖና የለም/ ለዚህ ነገር መነሻው የኦሮሞ ባህል ስነ-ስርዓት ነው፡፡ ይሄ የያዘን ዘር ቆጠራ አባዜ አይለቀንም አይደል ቶሎ ብላችሁ ዘሬን ልታጠያይቁ እንዳትሞክሩ፡፡ከሁሉም ያለብኝ ሁሉም የሚመለከተኝ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ በቃ! ከፍ ሲል አፍሪካዊ ዝቅ ሲል ኢትዮጵያ ነኝ ከዛ በታች በብሄር በጎሳ እንዳትመነዝሩኝ አደራ፡፡ አልመነዘርም፡፡

    በኦሮሞ ማህበረሰብ ባህል እና እምነት ውስጥ ፈጣሪን የማመስገኛ እና የመለመኛ ሁለት ስርዓት አለ፡፡ እሬቻ ይባላል፡፡ እስካሁን ያለውን አንብባችሁ እንዴት ያንን ከዚህ ያገናኛል የሚል ሀሳብ ከተፀነሰባችሁ በዚህ ሰዓት እንኳን እውነታን ለመረዳት እንዘጋጅ፡፡ እሬቻ ፈጣሪን የማመስገኛ በዓል ነው፡፡ ከግንቦት ልደታ ጋር ግን ምንም አይነት ግንኙነት የለውም፡፡ የተወራረሰ ባህል ወይንም መንገድ ግን አለው፡፡ እሬቻ በአመት ሁለቴ ይከበራል፡፡ አንዱ መስከረም ላይ መስቀል በዓል በዋለ ቀጥሎ ባለው እሁድ የሚከበረው ነው፡፡ ወንዝ ዳር፣ ሀይቅየመሳሰሉት ውሀ ያለበት ቦታ ለምለም ቄጤማ ተይዞ የሚደረገው ሲሆን አላማውም ዝናቡን አዝንበህ ይህን ለም የሰጠኸን አምላክ ተመስገን ለማለት ነው፡፡

   ሁለተኛው ደግሞ ግንቦት ወር ላይ የሚደረገው የተራራ ሬቻ የሚባለው ነው፡፡ ይህ አከባበሩ ልመና ነው፡፡ መጪው ወቅት ክረምት ነውና ዝናቡን ስጠን ለከብቶቻችንም ግጦሽ የሚሆንውንእኛንም ከብቶቻችንንም ጠብቀን የሚል ስለሆነ ‹‹ቦረንትቻ›› ይባላል፡፡ የቦረና ልጆች ልመና በመባልም ይታወቃል፡፡ የተራራ እሬቻ ስለሆነ ትልቅ ዋርካ ስር ስለሚደረግ ሌላው ሰው ዛፉን የሚለመን ይመስለዋል፡፡ በአንድ ወቅት በዚሁ ዙሪያ ያናገርኳቸው በደብረዘይት ዙሪያ የዋቄ ፋና ማህበር አሰባሳቢ ‹‹ፈጣሪን አንተ እንደዚህ ዋርካ የገዘፍክ ነህ፣ ከለላችን ነህ፣ መሰባሰቢያችን ነህ ለማለት ነው…›› ዋርካው ስር የሚደረገቀው ብለውኛል፡፡ ተራራ ላይ የሚደረግ ብቻ ሳይሆን በሰፈር፣ በቤትም እንደሚደረግ ይታወቃል፡፡ ግንቦት መሆኑም አንድ ላይ ስለሚያከብሩት እየተለመደ መጣ፡፡ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው ከእኛ ግንቦት ልደታ ጋር ተገናኝቶ ጊቢ፣ ሰፈር ውስጥ ተሰባስቦ ማክበር ጋር ተዛመደ፡፡ ግንቦት ልደታ ሊከበር የሚገባው ግንቦት አንድ ቀን ብቻ መሆን ሲገባው እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ እና አሁንም አንዳንድ ቦታ ከዚህ ስርዓት ወጥቶ ከግንቦት አንድ እስከ ሰላሳ ባለው ጊዜ ይከበራል፡፡ ከዋቄፈታ የተራራ እሬቻ ጋር ያለው ዝምድና የፈጠረው እውነታ ነው፡፡ ስለዚህ በዓሉን ከግንቦት አንድ ውጭ ማክበር የእምነቱ መሰረት እንዳልሆነ ይታወቅልኝ፡፡

     እኛ ሰፈር ስለነበረው አደባር አከባበር ላወጋ ቢሆንም አነሳሴ እግረ መንገዴን ነገርን ነገር ጠልፎት ወደ ሌላ ገባሁ፡፡ ተመልሻለሁ ይታወቅልኝ፡፡ ታዲያ ትዝታው ዛሬም በስደት ሳለሁ ጊቢያችን ውስጥ የነበረ ስነ-ስርዓት ትውስ አለኝ፡፡ ጊቢው ውስጥ ያለው ቤት በቀበሌ የተወረሰባቸው አቶ ሞገሴ በእኛ አጠራር አባባ ሞገስ ናቸው ሰብሳቢ፡፡ ገና ሳምንት ሲቀራቸው አዋጡ ይላሉ ጋቢያቸውን እንደለበሱ በረንዳ የሌለው ቤታቸው በር ላይ ባለ ሶስት እግሩ ዱካ ወንበር ላይ ተኮፍሰው፡፡ ይሄ እዚህ ጋር ይሁን ጊቢው ይፀዳአንቺ የቀረብሽን አታዋጪምታዲያ ጊቢያችንን ብታዪት ትንሽ ቤት ያቆረ እንዳይመስላችሁ፡፡ 18 በላይ ነው፡፡ ሙሰሊሞችም አሉ፡፡ ዘሜ፣ አቶ ሙሳ፣ ጣይቱ አሊ..ከማስታውሳቸው ውስጥ ናቸው፡፡ እነሱም አብረው ያዋጣሉ፡፡ አብረውን አድባር ብለን የምንሰባሰብበት ቦታ ተቀምጠው ይቋደሳሉ፡፡ ያኔ ፍቅር ጋቢ ነበር፣ ቡልኮ ነበርእንዳሁኑ አንገት ልብስ አክሎ ተሸማቆ ሰዉ በቋፍ አልሆነም ነበር፡፡ የጎሪጥ አይተያይም፡፡

    ንፍሮ ይቀቀላል፣ አነባበሮ ይነባበራል፣ ቡና እቃው ይዘጋጃል፣ በግ ይታረዳል፣ ጠላው ነጭ አረቄውኡኡአይ! አሁን አሁን አለኝ፡፡ ታዲያ እኔ የሚደርሰኝን ነገር ሁሉ ብዙውን በስጋ እለውጣለሁ፡፡ አንዴ ታዲያ በግ ታርዶ፣ ተገፎ፣ ተቆራርጦ..ብረት ምጣድ ላይ ይንቻቻልዋይ!..ዋይ!.. ድረሱልኝ፣ ጉረሱኝ በሚልበት ሰዓት ነው፡፡ ምራቄ ከጉሮሮዬ ጋር ታሻርኮ ድምፅ እያወጣ ያጋልጠኛል፡፡ ምራቁን ዋጠ አሰኙኝ፡፡ ደሞ ምራቁን ዋጠ የሚለውን ጎመጀ በሚለው ይተረጎምልኝ፡፡ ምራቁን ዋጠ በሰለ አስተዋይ ሆነ የሚለው ዛሬም አይነካኝዞር ሲሉ አንዷን ብድግ….እኔን ተከትሎ የታላቅ ወንድሜ ደኛ ነው ብድግ አደረገ፡፡ ጓጉቶ ሊሆን ይችላል፡፡ ወደ አፉ ከማለቱ ምን አለፋችሁ ንጋቱ የሚባለው የፈንጂ ፍንጣሪ አይኑን ነክቶት ጡረታ የወጣ ወታደር ‹‹ቁጭ አድርግ! ሳይቋደስ አንተ ባለጌ..›› አለና ያነሳውን ልጅ በ10 አለቂኛ ተቆጣው፡፡ ፈራና ሊመልስ ሲል አምጣ እኔ ልመልስ ብዬ በላሁት፡፡ ንጋቱ የሚሉት ወታደር በኩርኩም ቆጋኝ፡፡ የሚቆጋ ይቆጋውና!..ታላቅ ወንድሜ በሰዎች ዘንድ የተወደደ ዝምተኛ ነው፡፡ ግን የሚሰራውን ተንኮል እሱ ይሰራዋል የማይባል ነው፡፡ እኔ በመመታቴ ተናዷል፡፡ አስቀምጥ የተባለው ልጅ ጊቢው እዛ አይደለም፡፡ ከወንድሜ ጋር በጣም ስለሚቀራረቡ እሱን ብሎም ስለሆነ የመጣው ‹‹አስቀምጥ›› ብሎ ስለሰደበው በሁለቱም ነገር ተናዷል፡፡ የተሰጠንን የበግ እንትን/ ስታነቡት እንዳታፍሩ ነው እንጂ የበግ ቆለጥ ማለት አፍሬ አይደለም/ ይዞ ማዕድ ቤት ገባ እና ኩራዙ ላይ ያለውን ጋዝ ቀብቶ ተመለሰ፡፡ ወደ ብትረት ምጥዱ ስር ወረወረው፡፡ ያየው የለም ያዩትም ሊጠብስ መሰላቸው ቦግ ቦግ አለና ‹‹ዱዋ!!!!!›› ፍንዳታውን ሲያቀልጠው ሁሉም በድንጋጤ ጨው ሆኑ፡፡ ንጋቱ የሚባለው ደንግጦ ወደ ኋላው ሊፈነገል ምንም አልቀረውም፡፡ ሚሊዮን የሚባለው የቀበሌያችን ሊቀመንበር ባያረጋጋ የተፈጠረው ነገር ብዙ ይሄድ ነበር፡፡

     እኛማ አጋጣሚውን ጠብቀን ንፍሮ ዘግነን ኪሳችን ደበቅን፡፡ ወንድሜ ግን በዚህም አልተደሰተም ነበር እና ንጋቱ የሚባለውን ሌላ ጊዜ ተበቀለው፡፡ እንዳይበላ ተቆጥተው ያሰመለሱት ልጅ ግን የተከለከላትን ስጋ ዳግም ሰርቆ አገኛት እና አጣጣመ፡፡ ሰዓቱ ደረሰና ቡናው ተፈልቶ ጫወታው ደርቶ ምርቃት ተንጋግቶ የሚሰጠው ታደለን፡፡ ከላይ እንዳነሳሁት ከእሬቻ ጋር ሌላ ያመሳሰለው ነገር በተን በተን የሚደረገው ነገር ነው፡፡ እኔ ደግሞ ይህን ልጅ እያለሁም እቃወማልሁ፡፡ ለነገሩ ሆዳም ስነበርኩ ለእህሉ አዝኜ እንጂ ትርጉሙ ገብቶኝ አይመስለኝም መቃወሜ፡፡ አቃቂን የምታውቁ መካና የሚባለው ቦታ እሬቻ ሲደረግ አይ ነበር፡፡ እዛ ተማሪ በነበርኩ ሰዓት የሚበትኑትን ለቅሜ እበላም ነበር፡፡ አድባር ላይ እንደዛው ነኝ፡፡ አይ ልጅነት ተደባድበን ሁሉ እናነሳው ነበር፡፡ አይ!..ሸዋ!...ብዙ አስባልሽኝ፡፡ አስታወስሽኝ፡፡