Tuesday, May 8, 2012

ስለ ልጅነቴ እውነት እውነቱን እናውራ ካልኩ ብዙ ደስ የሚል ባይሆንም በድህነታችን ላይ የተመረኮዘ ጦሽ..ጧ../ባያስቅም ለሞራሌ ስትሉ ሳቁ/ የሚያደርግ ወግ አወጋችሁዋለሁ።ጆሮዎትን ለመስማት አቀባብሉና አበድሩኝ። ተኖረና ተሞተ ያሉት የአለቃ ገ/ሀናን አይነት ህይወት ባይሆንም አኛም ሰፈር ተኖሯል። ምን ይጠበሰ እንዳይሉ..አሳ እንዳልል ተወልጄ ያደከበት ሰፈር አሳ በስህተት ካልሆነ አይገባም። ወንዝ የለ ሀይቅ የለ ከየት ይመጣል?የአሳ ስዕሉን እንኳን ይዞ መገኘት ሰው በማጓጓት እና ምራቅ በማሰዋጥ ወንጀል ያሰከስሳል። 4ኪሎ እና 6 ኪሎ መሀል 5 ኪሎ ብለው ይጠሩታል፡፡ ማን መዘነው እንደትሉኝ ተወለድከበት አልኩ እንጂ መሰረትኩት አ...ላልኩም።

ዘውዱ አዲስ፣ነብዩ ሀይሉ፣ወንደሰን ሰብስቤ፣ ዳንኤል መሀሪ..ተወልጄ ያደኩበት ጊቢ ያሉ ልጆች ናቸው። የረሳሁዋችሁ አትቀየሙ። አንተነህ ፑሲን ግን አልረሳሁም።ዛሬ ዘውዱ አሜሪካን በዲቪ ሰበብ ከትሟል። ነብዩ እና ወንደሰን የት እንዳሉ አላውቅም። የት ናችሁ ከሰማችሁ አለን በሉኝ። ዳንኤል ግን ኤርትራዊ ስለሆነ መውጣቱን አውቃለሁ እንጂ የት አንዳለ ምንም መረጃ የለኝም። ዳንኤል ይህችን መጣጥፍ ካገኘሀት ሰላምታዬን ማድረሴ ብቻ ሳይሆን ዘውትር እንደማስብህ ተረዳ። /ማኸዛይ ኩሉ ጊዜ ይዝክረካ-ሰላም ንዓካ/ ብዙ ትዝታ ያለኝ ግን ከጌታሁን መሳፍንት፣ከተካልኝ ተክሌ፣ከቀìላ ሲሳይ፣ከካሳሁን የሺጥላ፣ሳሙኤል ብስራት..ታዩ…ሽፈራሁ ሀብቴ፣ካሳሁን መኮንን.. ሰይፈ ጌታቸው….ብዙ ነን። ሰይፈ ነፍሱን ይማር በሞት ተለይቶናል።

ከነዚህ ውሰጥ ጌታሁንን ከሁሉም ይበልጥ እወደዋለሁ። ጌትሽ አጭር እና ቀጭን በመሆኑ እንዝርት የሚል ቅêል ስም አለው። እኔ ድንጋይ ስወረውር ባለመሳቴ ጠጅቱ የምትባል የሰፈር ሰው ቦምቤ አለችኝ። ይህች ቅêል ስም ከራሴ መተለቅ ጋር ተያያዘችና ቦምብራስ የምትል ታፔላም ሆና ነበር። ትንንሽ ቦምብ መኖሩን ቢያውቁ ስያሜውን ይፍቁልኝ ነበር። አባቴ ሁሌም ሱፍ ሱሪና ኮት ያሰፋልን ስለነበር ከበተር ፍላይ ከረባት ጋር ስለማደርግ እና ካቆሸሽኩ ሰለምገረፍ ጓደኞቼ ኳስ ሲጫወቱ እኔ ቁጭ ብዬ ስለማይ አካሄዴንም ጨምሮ ባንታለም ሰብስቤ ሚኒስቴር የሚል ቅêል ስም አውጥቶልኛል። ሁለት በሉ።

ከጌታሁን ጋር ትምሀርትም አብረን ነው የምንማረው። አርመን/አሁን ብሔራዊ ቤተመንግስት/ የሚባለው ት/ቤት ነው የተማርነው። ብሩክታይት አሰፋ..አሁን ካናዳ አለች የፒያሳ ሰራተኛ ሰፈር ልጅ፣..ፍሬህይወት አጥላባቸው.. ሳባ ተርዲ የሚባሉ የምንቀርባቸው ልጆች ናቸው። ሳባ ተርዲ ለጌትሽ ሴት ጓደኛው ነበረች። ሁለተኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ የገጠመኝን መዓት ላውጋችሁ ፦ ቲችር አበበ የምንላቸው አንድ እግራቸው አጠር ያለ የክፍል ሀላፊያችን በአንደኛ ሴሚስተር አንደኛ መውጣቴን ገልጠው ሰርተፊኬቴን ሲያቀብሉኝ አሰጨበጨቡልኝ። እግዚአብሔር ይስጣቸውና ያኔ ባያስጨበጭቡልኝ ኖሮ ሳይጨበጨብልኝ እሞት ነበር። ከዛ በሁዋላ ጭብጨባን ዳግም አላገኘሁትም። ለማየት እንኳን ምክር ቤት እሱንም በቴሌቪዥን ነው የማየው። ቀጠሉና ሁለተኛ ለወጣው መስፍን ተ/ሀይማኖት ሰርተፊኬቱን ካቀበሉ በሁዋላ አጫሽ ስለሆኑ ሁሌ ያስላሉ። በሳል የታጀበ ጥያቄ መረቁለት።

<<..ወንድማማቾች ናችሁ?>> ጢም የከበበው አፋቸውን ሞጥሞጥ አድርገው ሲያፈጡብኝ ፈራሁ እንጂ <<..በአማርኛ ክፍለ ጊዜ ላይ ያስተማሩንን አዛምድ እኛ ላይ ሊሞክሩት ነው እንዴ?እኛ ቤተ ሙከራ ያለ አይጥ ነን >> ልላቸው አሰብኩ። ምን ያደርጋል ስለምፈራ ፍርሃቴን ተሸክሜ ቀረሁ። እሳቸው ግን ድፍረት አገኙና በአንካሳ እግራቸው ከፍ ዝቅ እያሉበት ብላክቦርዱ ጋር ቆመው እያስተዋሉን <<..ደሞ በመልክም ትመሳሰላላቸሁ..>> ሲሉ ሽርደዳ የሚመስል ቃላት መረቁልን። አሁን የማላስታውሰው ስድብ በውስጤ ሰደብኳቸው። ለነገሩ እንኳን አላስታወስኩት የስድብ ጥሩ የለው። ነብሳቸው ይማረውና በመጥፎ ድርጊት ስለሚታሙ በሱው የሰደበኩዋቸው መሰለኝ። ሁሌም አውቶቡስ ላይ ከሴቶች ሁዋላ ቆመው ይተሻሹና..አንድ ጊዜ አንድ ሴትዬ እንትናቸውን ይዛ ስትጎትታቸው በዓይኔ አይቻለሁ። ከዚህ የራቀ አልሰደበኩዋቸውም። ከፈለጉ ራሳቸው አያስታውሱ እኔ ምን አቀጣቀጠን? አባቴን ዋልጌ አድርገው ከእናቴ ውጭ እንደወለደ ለምን አሰቡ ብዬ ነው መሳደቤ።

ከውስጥ ኔትወርካችን ተገናኝቶ ይሁን ተጠላልፎ ድንገት ሳናውቀው እኩል <<አይደለንም>> አልናቸው። አልተዋጠላቸውም። እንኳን ሊዋጥላቸው ከጆሯቸውም የገባ ሳይመስሉ << ለማንኛውም ተጠያየቁ>> የሚል ማሳሰቢያ ቢጤ ወርውረው ሰርተፊኬት ማደል ቀጠሉ። አጠገቤ የተቀመጠው አላዛር ነጋሽን ቢሉ የሁለታችንም ራሰ ጠበደል በመሆኑ ሊያመሳስሉን ይችላሉ የሚል እሳቤ ከማሰቢያዬ ውስጥ ስንቅር አለ። እስክንወጣ ተነቆራጥጨ ጠበኩ። ስንወጣ መስፍንን በጥያቄ አጣደፍኩት።
<<የአንተ አባት ምን አይነት ነው? የእኔ አባት ቀይ ረጅም ሽበታም ነው..የአውራ ጎዳና መኪና ይነዳል ትልቅ የነዳጅ ቦቲ..>> በጥሞና ሲያዳምጠኝ ቆይቶ <<የእኔም አባት አንተ እንደምትለው ነው ብዙ ጊዜ ክፍለ ሀገር ነው።ግን ትላንት ማታ መጥቶ ነበር።..>> አለና የቲቸር ሳያንስ እሱም ጥርጣሬ አርሶ ስለዘራብኝ ቤቴ ልወስደው አሰብኩ።

የልጅነት ታሪካችን ቢውራ..ቢወራ የሚያልቅ አይደለም። ቀጣዩን ሳምንት እመለስበታልሁ። ከደበራቸሁ ግን ገትረው በሉኝ።እገትረውና ቴዘር ትጫወቱብታላችሁ። ከተመቻቸሁ ጭብጨባችሁን አሰሙኝ። ወደፊት እንላለን።
ቸር እንሰንብት
See More

Friday, May 4, 2012


ጥቁሯ ቦርሳዬ ክፍል 4
                     ወግ  በግሩም ተ/ሀይማኖት
   
 ሰላም ለምታነቡኝ፣ ሰላም ለምታዝናኑብኝ፣ ሰላም ለጓደኞቼ..ሰላም ለኢትዮጵያዊን ሁሉ...ምኞቴ ለሁሉም ሰላም ነውና ሰላማችሁ ይብዛ እላለሁ፡፡ ሰው ያለውን ከሰጠ ንፉግ አይባልም፡፡ ያለኝ አቅም መመኝት ነውና ተመኘሁላችሁ፡፡ ማየት መመኘት ማመንዘር ነው የሚለው እዚህ ጋር አይሰራም አትፍሩ፡፡ ከሰላም የበለጠ ምን አለ? ምነው በጥቁር ቦርሳ ተነሳህ የሚለኝ በዝቷል፡፡  የከለር ምርጫዬ ቀይ ቢሆንም ቦግ ብሎ መታየትን ስለማልሻ ሳይሆን ይቀራል? ብቻ እወዳታለሁ፡፡ ውስጧ ብዙ ምስጢር አለ፡፡ የጡረታ ጊዜዋ ቢያልፍም ፍቅር አስከ መቃብር ብዬ ሙጥኝታዬን አብዝቼባታለሁ፡፡ ለነገሩ ከሀገሬ ስወጣም ልክ የዚህችን አይነት ጥቁር ቦርሳ አንጠልዬ ነበር፡፡ እናቴም ሆነች እህቴ እኔና ጥቁር ቦርሳዬን ነው የሸኙን፡፡ ያቺ ቦርሳ ከእኔ ጋር ያላየችው ስቃይ የለም አንደበት ኖሯት አላወራችውም እንጂ...ደግነቱ እግዚአብሄር ይስጠኝ እኔ አውርቼላታለሁ፡፡ የአሁኗ ጥቁር ቦርሳ ከሀገር ስወጣ እንዳደረኩት ቡትቶ ሞልቼባት ሳይሆን ላፕቶፕ እና ወረቀታ ወረቀት ነው ያቆረችው፡፡ ስለያዘቻቸው ወረቀቶች እና መጣጥፎች ላወጋችሁ ነው፡፡

    ርዕሷን ግን ጥቁሯ ቦርሳዬ ያልኩበትን ምክንያትን መተንፈስ ግድ ይላል እና ላውጋዎ፡፡ የመብራት ችግር የመንን ከተጠናወታት ከረምረም አለ ከሚባለው አልፏል፡፡ አንድ አመት ከስድስት ውር ተጠግቶዋል፡፡..ያን የመብራት ችግር ለመቋቋም በተገኘው አጋጣሚ በቀን አንድም ሆነ ሁለት ሰዓት ብቅ ሲል ቻርጅ የሚደረገውን ሁሉ ቻርጅ ማድረግ ግድ ይላል፡፡ እኔም ላፕቶፔን ይዤ መብራት ወዳለበት እብስስ....ቻርጅ አደርግና ለ3 ሰዓት ከተጠቀምኩ፣ ሞባይሌም ቻርጅ ከሌለው ከላፕቶፑ ካጋራሁ በኋላ ሌላ መብራት ወዳለበት...በቃ ምን አለፋችሁ እንደመድፍ አስተኳሽ ቦታ እየቀያየርኩ.. መዋጋት ነው፡፡ ታዲያ ቃታ ስቤ ጥይት አፈንድቼ አለመሆኑ ይታወቅልኝ፡፡ እሷን ነገር አልወዳትም፡፡ ከመብራት ችግሩ ነው የምዋጋው፡፡ እንደዛ ሆኜ ነው ‹‹እኔ እና ጓደኞቼ››ን እና ‹‹ሀበሻ በየመን›› የሚሉ ጽሁፎቼን ያስነበብኩት፡፡ ለካ ያቺ የማንጠለጥላት ጥቁር ቦርሳ ተከራይቼ ያለሁበት አካባቢ ያሉ የመናዊያንን አይን ስባ ነበር፡፡ እኔን ሳትስብ የሌላውን መሳቧ ቢያስቀናኝም ቀናሁ አልልም፡፡ ቅናተኛ የሚል ታፔላ እንዳይለጠፍልኝ ፈርቼ ነው፡፡ ታዲያ አይናቸውን የሳበቻችው የመናዊያን  እኔ ሳልሰማ ‹‹አቡ አስወድ ሻንጣ›› ይሉኛል፡፡ ባለጥቁር ቦርሳው ማለት ነው፡፡

     አንድ ቀን ተከራይቼ ያለሁበት ፎቅ ላይ ከእኔ ቀጥሎ ያለውን ክፍል ከሚስቱ ጋር የተከራየ ልጅ ሱቅ እቃ ሊገዛ ይሄዳል፡፡ ነጋዴው ‹‹ለአቡ አስወድ ሻንጣ መልዕክት እኔ ጋር አለውና ንገረው›› ይለዋል፡፡ አንድ ጓደኛዬ...እእ በዘልማድ ነው ጓደኛዬ ያልኩት፡፡ የመን ውስጥ የልብ የምለው ጓደኛ የለኝም፡፡ ከምር ነው ለጓደኛነት የሚሆን ማሰብ ሀጢያት ነው የሚመስለው፡፡ ለዚህም ሳይሆን ይቀራል ብቸኝነት ያለ ፍቃዴ፣ የቤት ኪራይ ሳይከፍል..ቂብ ብሎብኝ ያለው፡፡ እናላችሁ የተቀመጠልኝን መልዕክት እንድወስድ ላከብኝ፡፡ ለምን እንደሆነ ስጠይቀው ባለሱቁ ሁሌ ጥቁር ቦርሳ ስለምይዝ እና ስሜን ስለማያውቁት እንደሆነ ነገረኝ፡፡ እኔ ግን ስያሜዋን ወደድኳት፡፡ ተጠቀምኩባት፡፡ ጥቁሯ ቦርሳ የያዘችውን ምስጢር ቢያውቅ....አይ የኔ ነገር ልታውቁት አይደል?

       ከርዕስ ውጭ ጥቂት እናውራ፡- ቴዲ አፍሮ የአሁን ዕለቱ ትላንትና በለቀቀው አልበሙ ‹‹...ተናነቀኝ እንባ...ተናነቀኝ፣ ተናነቀኝ...›› የሚለው ዜማ በጥፊ ስትባል ከምትንኮራኮር ቴፔ ይንቆረቆራል፡፡ ቀልድ የማያውቀው አይኔ የምር አድርጎት እንባዬ ተናነቀኝ እና ቁጭ፡፡ ምክንያት ያደረገው ብቸኝነቴን ቢሆን ደግሞ ምን ትላላችሁ? የተናነቀኝ እንባ ግን ዝርግፍ ያለው ቆይቶ የሰማሁት ‹‹ስለፍቅር ሲባል ስለፀብ ካወራን ተሳስተናል አንድ ላይ ብንኖርም ተለያይተናል፤አጥተናል እውነት ነው ተቸግረን ብዙ አይተናል..›› ሲል ብሶታችንን እቅጩን ነው የነገረን እኮ ታዲያ እንዴት አልዘረግፈው? ሰው ብሶቱን ሲነግሩት አይደል..መጎዳቱን የሚያውቀው? ተቸግረን እናገኛለን በማለት ስንሰደድ አይደለም ባህር ስንቱን የዋጠው? ዋ! ወገኔ...መቼም ምስኪን ነኝ እና ቴዲን አስለቅሶኝ መረቅሁት፡፡ ሰው በልኬ ብለህ የለመንከውን የሰማና በልክህ የሰጠህ አምላክ ነገም ብንረዳህም ባንረዳህም ማንነታችንን፣ ችግራችንን፣ ታሪካችንን ፍቅራችንን፣ ማጣታችንን፣ አረንጓዴ መሬት ይዘን መራባችንን.. አንቆርቁረህ እንድታሰማን እድሜ ይስጥህ አልኩት፡፡ ምነው ፈጣሪ ምርቃቴን ሰምቶ እውን ባደረገለት? ዋይ ቢኖረኝ ላጥ አድርጌ ወርቅ ነበር የምሸልመው፡፡ ለነገሩ ያለኝን ሸለምኩት አይደል? ከወርቅ የበለጠ እድሜ ለምኜለታለሁ፡፡ ወርቁንም የሚያጌጥበት እድሜ ያስፈልገዋል እኮ...

     ለነገሩ እኛ እኮ ሽልማት የሚመስለን ቁሳቁስ ነው፡፡ ህሊና የሚያድስ እንደ ብርታት መርፌ የሚቆጠር ምስጋና እና አድናቆት ጥቅሙ አይገባንም፡፡ ‹‹አመሰግናለሁ›› ስንባል ‹‹ምስጋና ኪስ አይገባም..›› ማለት ተዘውትሮ የሚሰማ እና ኪስ የሚገባ ብቻ ናፋቂነታችንን ያስመሰከረ ማንነታችን እየሆነ ነው፡፡ በምስጋና፣ በአድናቆት ህሊና መገንባትን እና ለህሊና መኖርን ጎበዝ እስኪ ከዛሬ እንጀምር፡፡ ህሊና ቢስ ሸቀጥ አምላኪ...በሸቀጥ የምንለካ፣ የምንመዘን.. ቁስ አንሁን፡፡ ሰው አድረጎ ፈጥሮናል እና ሰውን በሰውነቱ እንመዝን....

   አንዴ ይቅርታ ይደረግልኝ እና ቅድም እንባዬን አመጣው ካልኳችሁ ‹‹...ተናነቀኝ እንባ ተናነቀኝ..ተናነቀኝ እንባ ተናነቀኝ..›› ወደ ሚለው ዜማው ልመለስ፡፡ እዚህች ጋር ምስጢር ያላት ነገር የሰማሁ ስለመሰለኝ የእጅ ፍሬን ባይሆን የጆሮ ፍሬን ያዙና አስተውሏት፡፡
 
‹‹..የተለያየን ለት ልቤ አዝኖ ሊከፋ
ምወዳት ከልቤ ነበረ በተስፋ....›› እንደእኔ እንደኔ ይቺ ለሴት ነች ለሀገር? ለነገሩ ሁለቱም አንድ ናቸው፡፡ ሀገርም ሴትም እናት ናቸው፡፡ በማህጸናቸው ተሸክመው በጀርባቸው አዝለው...ከልብ የምንወዳት ሀገራችን ከልብ የምንወዳት እናታችን....ሁለቱም የተማስሎ ቁርኝታቸው ይበዛል፡፡ ስደት ሲወጣ እናቱን ሲሰናበት ያልከፋው ይኖር ይሆን? ሀገሩንስ? እኔ እናቴን ስሰናበታት የቤታችን ድንበር የሆነው በር ላይ፣ ሀገሬን ስሰናበት ድንደር የሆነው ወንዝ ድልድይ ላይ እንባዬን ጠብ አድርጌያለሁ፡፡ 

‹‹..ስትሰናበተኝ ላይቀር መተከዜ
ሰው አልሰማ እያልኩኝ በፍቅሯ መያዜ...
ይሄው ዛሬ ስትሄድ ሆዴ ባባ ተናነቀኝ..
ተናነቀኝ እንባ..ተናነቀኝ..›› በእሱ ዜማ ሂያጇ/ተሰናባቿ/ እሷ ሳትሆን ስሰማው ተገልብጦ ሀገሬን ተሰናባቹ እኔ ሆኜ እርፍ ነዋ! እኔ የማወራው የእኔን ነው የእናንተን እናንተ አስቡት፡፡ እንኳን የሰው የራሴንም የሚያስብ ጭንቅላት አጥቼ በጎረቤት/በየመን/ አዴንግ ማሽን ነው የምጠቀመው፡፡ እነዚህ ዘፋኞች ሲባሉ ነገረኞች ናቸው፡፡ አንድ ሰሞን ጎሳዬ እና ኤፍሬም ‹‹ኑ..ኑ..ተስብሰቡ›› እያሉ ምድረ ሀገሩን የረሳ ዲያስፖራ ሁላ አንቀዥቅዠው አስገቡት፡፡ የእኔም ልብ ብድግ ቢልም ፀሀዩ መንግስታችን ለመስተንግዶ ማረፊያ እንዳይቸግርህ ብሎ ኤርፖርት ጠብቆ ያንጠለጠልኳት ፌስታል ውስጥ ቦንብ ተገኘ ብሎ ‹‹አሸባሪ›› የሚል ታፔላ ለጥፎ ቃሊቲ ይልከኛል ብዬ ፈራሁና ቀረሁ እንጂ...ዋይ!! ተክልዬ..ወዲ ኮንካ ወዲ ዘይምኳን..አነስ ፈርሔ እንድዒ ንበር..
 
‹‹...ሰው ልኬ አታውራ ተው ሲለኝ ያኔ..
ሲነግረኝ ሰው ፈርቶ አኳኻናን አይቶ
ለእኔ እደማትሆነኝ አልሰማም አልኩና...›› ይሄ ደግሞ የመናገር እና የመፃፍ መብት ተሰጠ ብለን፣ እውነት መስሎን ስንቶች መከራ ያየንበትን...ብቻ ይሄ ቴዲ አፍሮ የመሳለሚያ አካባቢ ልጅ ነው መባሉን አልቀበልም ነበር፡፡ አባቱ ካሳሁን ግርማሞን፤ አክስቱ ገነትን፣ ጓደኛው ቴዎድሮስን..ያደገበት ቀስተደመና ት/ቤትን ባላውቅ ኖሮ የጎጃም ቆሎ ተማሪ ነው ብዬ እሟገት ነበር፡፡ የዋዛ ይመስጥረዋል እንዴ....የቅኔ እርጎ እየጋተን.... እይ! የኔ ነገር በዘፈኑ ተመስጨ ያሻኝን ስል ዝም ትሉኛላችሁ? 

    ፀሀፊው ብቻ ነው መብት ያለው? ከዚህ በላይ ያለው እኔን አይመለከትም፡፡ የፈጣሪዬ የአቶ ፀሀፊ ሀሳብ ነው፡፡ እኔ ቀጠልኩ....ስለላቡ ስለምኑ እያሰብኩ..እያሰብኩ ሳላጠናቅቅ ‹‹ተጫወት እንጂ ምነው ዝም አልክ?›› ሄለን ናት ያለችኝ፡፡ አየኋት አየችኝ፡፡ አይኗ አቀጣሪ ነገር ነው ሳልጠይቀው ጫዎታ መፈለጓን ቀድሞ አሳበቀልኝ፡፡ ቁልጭልጭ አለ፡፡ እንዴት አባቱ ያምራል አይኗ እባካችሁ? የአስራሁለት...ኤጭ ደርዘን ማለት እችል ነበር ለካ...የደርዘን ቻይናዎች አይን ቢደምር አይወዳደረውም፡፡ እንዴት እስከዛሬ ልብ ብዬ አላየሁትም? ለነገሩ እንዴት ይታያል፡፡ ይሄ እንደቀለበት መንገድ የተሟለለ ፊቷ በቡግር ተንቆጥቁጦ ኮረኮንች መንገድ ስለሚመስል የሰውን አይን ከሩቅ ይመልሳል፡፡ ምቀኛ ፊት አላት አይን የማያስገባ...ገበያ ከልክል ነው፡፡ ደግሞ እኮ ዘመናዊ ልሁን ባይ ነች፡፡ ከአለባበሷ ጀምሮ ስልጣኔ የፈነጠቀባት፣ አወቀች..ዘመነች የተባለች እንድትሆን ትፈልጋለች፡፡ ወርቅ ብትለብስ ዘምና ሙትት ብትል የሚያሳብቅ ገጠሬነት አላት፡፡ ጥርንቅ ባለ፣ ሞልቶ በፈሰሰ የገጠር ባህል እና ወግ ተኮትኩታ ማደጓ ያስታውቃል፡፡ ራሱ ውበት እንደሆነ ሳታውቅ ባላገርነትን ነውር አድረጋው እሷም ‹‹ባላገር›› ብላ ትሳደባለች፡፡ ዝንጀሮ የራስሽን መቀመጫ ሳታይ...ያስተርታል፡፡ ለእኔ ግን በባላገርነቱ የሚኮራ ወዳጄን ያስታውሰኛል፡፡ አይ! ሰማኸኝ በለው፡፡ እባካችሁ የምታገኙት ይህችን ፅሁፍ አሳዩት ላስፍራት፡፡

       ከምሰራባቸው ጋዜጣና መፅሔቶች መካከል አንዱ ለሆነው ዜጋ መፅሔት ጥበብ አምድ ቃለ-ምልልስ ልናደርግ እኔ እና ሰማኸኝ በራሱ መኖሪያ ቤት ውስጥ ተገናኝተናል፡፡ ሜዳውም ፈረሱም ያው ተብለን ግን ብቻችንን ወጋችንን መጠረቅ አልቻልንም፡፡ የአዲስ አልበም ስራ ስለነበረው ታዋቂው የባህል ዘፈኖች ግጥም ደራሲ ግሩም ኃይሌ፣ ሙዚቃ አቀናባሪው ሙሉጌታ አባተ፣ ለሰማኸኝ ጥሩ ጥሩ ግጥሞችን የሰራለት ገጣሚ አባተ ማንደፍሮ፣ የሰማኸን ሚስት ገበያነሽ..ሌላ ማን ነበር? ሌላ ማን ነበር?..በቃ! ጊዜው ስለረዘመ ረሳሁት የረሳኋችሁ ይቅርታ አለን ብላችሁ እጅ አውጡ...ስሜ ሳይጠቀስ ብላችሁ ሆድ እንዳይብሳችሁ ፈጣሪ አይርሳችሁ፡፡ ብቻ ተሰባስበን አርጋን ይጠቀጠቃል፣ ዜማ ይዜማል፣ ግጥም ይታረማል..ጥሎብኝ ደግሞ የሰማኸኝን ነጎድጓዳማ ድምፅ እወደዋለሁ፡፡ የምንቅም ሰዎች እየቃምን ነው፡፡ ላብ እንጠርጋለን፣ ቡና እንጠጣለን፣ ሲጋራ እናጨሳለን፡፡ በመሀል ላይ የሰማኸኝ በለው ስልክ ደግሞ ደጋግሞ አንቃጨለ፡፡ አነሳው እና ‹‹ሀሎ!›› ሲል ጀመረ፡፡ሁላችንም በትኩረት እንድናዳምጥ በምልክት ነገረን፡፡ ያ- ወቅት ሰማኸኝ ምሽት ከሚሰራበት ሸዋጌጥ ሆቴል /ጭፈራ ቤት/ ወጥቶ የራሱን ጭፈራ ቤት ካሳንቺስ መናኽሪያ ጋር የከፈተበት ወቅት ነበር፡፡

       ታዲያ ረጅም ጊዜ የሰራበት ሸዋ ጌጥ ሆቴል ሌላ የባህል ሙዚቃ ተጫዋች ተክቶላቸው እንዲወጣ ስለለመኑት አሁን ስሙን ለክብሩ ስል የማልጠቅሰውን ታዋቂ ድምፃዊ ወስዶ ያነጋግረዋል፡፡ በነገራችን ላይ ይህ ስሙን የማለጠቅሰው ድምፃዊ በአንድ ወቅት ቅ/ማርያም አካባቢ ቡና ቤት ውስጥ የራሱን ካሴት ከኪሱ አውጥቶ ይከፈትልኝ ብሎ ለብቻው ሲጨፍር ስላመሸ ዘገባ አድርጌው ነበር፡፡ በራሱ ሂሳብ እየጠጣ በነፃ ጭፈራ ቢያስኮመኩመንም በወራዳ ተግባሩ ተጣልተናል እና ስሙን የማልጠቅሰው በቀል እንዳይመስልብኝ ነው፡፡

     እንተደለመደው ምሽት ላይ ተቀናጅቶ ለማቅረብ ልምምድ ሊያደርጉ በጊዜ ተሰባሰቡ፡፡ ያ ለቤቱ አዲስ ድምፃዊ ሲንጠባረርባቸው ምን ሆነህ ነው ይልና ሙሉጌታ ቦርጋ ይጠይቀዋል፡፡ እኔ እኮ ታዋቂ ዘፋኝ ነኝ ብሎ የማይሆን ነገር ይናገራቸዋል፡፡ ከመሀላቸው አንዱ ‹‹ሂዲ አንተን ብሎ ታዋቂ የባላገር ዘፋኝ..›› ይለዋል ይህን ተባልኩ እኔ እዛ አልሰራም ለማለት ነበር ወደ ሰማኸኝ የደወለው፡፡ ይህን የሰማው ሰማኸኝ ታዲያ ምን አለበት ባለ-ሀገር ነን እኮ..እያለ አረጋግቶት ስልኩን ዘጋው፡፡ ሰማኸኝ ባለ-ሀገር!...ባለ-ሀገር!!!! እያለ ሲደጋግም ቆይቶ ባላገር /ባለ-ሀገር/ ማለት ስድብ ነው? እኔ ባላገር ባላገር..ሰሜ ባላገር ባላገር እያለ እያጠና በነበረበት ዜማ አንጎራጎረ፡፡ ደስ የሚል ቅላፄ አለው፡፡ ወዲያው ለአባተ ማንደፍሮ እና ለግሩም ሀይሌ እሰኪ ለዚህ ግጥም ስሩልኝ አለ፡፡ ተሰራ ለዝናው እርከን ከፍ ማለት ብቻ ሳይሆን ለእሱነቱ መታወቂያ ሆነው፡፡ ባላገርነት ውበት ነው....ለሰሜ ባላገር
   
     ወደ ወጌ ስመለስ ሄለን ባላገርነቷ ውበቷም ድም ግባቷም መሆኑን ባወቀች ምንኛ ደስ ይል ነበር? ለነገሩ ትራንዚት አድርጎ አዲስ አበባ ከረም ያለ ሁሉ የአዲስ አበባ ልጅ ነኝ ይላል፡፡ አዲስ አበባ ከተባለ ሁሉ የአራዳ ልጅ እየመሰላቸው ነው፡፡ ስንት ጀንፈል እና ጀዝባ እንዳለ ቢያውቁ አፋቸውን በቆጠቡ፡፡ ሄለንም አዲስ አበባ ሳሪስ አካባቢ ያለች ዘመዷ አገናኝታት ፓስፖርት አውጥታ ወደ የመን ስትመጣ ሀብታም ስትሆን ታይቷት ነበር፡፡ እንዲያውም ሀብታም ስትሆን በምናቧ ያቀናበረችውን ፊልም እንደ ራንቦ ክፍል ስድስት ድረስ በተኛች ቁጥር በህልሟ አጣጥማዋለች፡፡ በኮንትራት ሁለት አመት ከሰራችበት ከወጣች ስድስት አመት አስቆጥራለች፡፡ በአጠቃላይ ስምንት አመቷ ነው፡፡ በያን ሰሞን ቀኑን እረሳሁት እንጂ ቤቷ እንድቅም ጋብዛኝ ሳለ ብዙ አውግታኛለች፡፡ አስታውሳለሁ ኮንትራት ቤት በገባች በ15 ቀኑ አሰሪዋ አስገድዶ ከደፈራት በኋላ በተደጋጋሚ ያስተኛት ነበር፡፡ በመሀል ፀንሳ ስለነበር አስወርዳለች፡፡ እድለኛ ነች፡፡ ስንቷ ስታረግዝ ሆዷ ሳይገፋ ተጠርዛ ወደ ሀገር ቤት ገብታለች? ስንቷ አስወርዳለሁ ብላ ሞታለች? ስንቶቹስ እዚህ አባት የሌለው ልጅ ይዘው ያሳድጋሉ? ለነገሩ ማህጸናቸውን ያለምልመውና ሀበሻ ለሀበሻ የተጋቡት ሁሉ የህዝብ ቁጥርን ከፍ ለማድረግ ያላሰለሰ ጥረት እያደረጉ ይሁን መዝናኛቸውን አልጋቸው ላይ አድርገው ልጅ በልጅ ናቸው፡፡

     ‹‹ሁሌም እንደዚህ ነህ?››  ምን አይነቷ ናት? ሄለን አሁንም አቋረጠችኝ፡፡ እነዚህ እያሉ ሰው በነፃነት ሀሳቡን ማንሸራሸር እንዴት ይችላል? አቋራጭ የበዛበት ዘመን፡፡

     ‹‹እንዴት?›› አፈጠጥኩባት፡፡

      ‹‹ስትቅም ዝምታ ታበዛለህ?››

     ‹‹ታዲያ ዝም ብዬ ልዘላብድ?››

     ‹‹ምን እያሰብክ ነው?››                    
  
     ‹‹ባክሽ ምን የሚታሰብ ይጠፋል? አንድ ቀን ፀሀፊ ለመሆን አስባለሁ፡፡ ልፅፍ የምችለውን አስባለሁ፡፡ አወጣለሁ፤ አወርዳለሁ፡፡››
      
      ከሄለን አጠገብ የተቀመጠችው ሰናይት ‹‹ፀሀፊ ለመሆን ብዙ ማሰብ ግድ ነው እንዴ?›› እዚህ ቤት ውስጥ መገኘቷ ያስገረመኝ ሴት ነች፡፡ ከመስከረም ጋር በአንዱ ተጣልተው ነበር፡፡ ሰናይት አግብቶ መፍረታት ሪኮርድ ሳይኖራት አይርም፡፡ ትዳርና አዳር ተምታቶባታል፡፡  በሰባት አመት ውስጥ 5 ጊዜ አግብታለች፡፡ አጠገቧ የተቀመጠው ኩኩሻ እዚህ ሀገር ከመጣ አራት ረመዳን ቆጥሯል፡፡ እኛ ሀገር ቢሆን አራት ደመራ ለኩሷል ነበር የሚባለው፡፡ እዚህ ደመራ ስለሌለ በአመት አንዴ በሚመጣው ረመዳን ነው የሚቆጠረው፡፡

    ኩኩሻን አልረሳለትም አንድ ቀን ነጭ ቅፈላ ቀፈለኝ፡፡ ድርቅ ያለ ቅፈላ..እኔ ደግሞ አውቄ ተቀፈልኩለት፡፡ጫት ገዝቼለት አብረን ቁጭ ብለን ስንቆረጣጥም ብዙ አወጋኝ፡፡ ‹‹ከልጅነቱ ጀምሮ አባቱ የሚሰሩበት ቦታ እየሄደ አብሯቸው ቀለም እንደሚቀባ ነገረኝ፡፡ ኢን አዘር ሀንድ.... በሞቴ እንዳታሳበፍሩኝ አንዳንዴ ምናለ ጉራማይሌ ባወራ?..ነውርነት የለው እንደሞባይል ካርድ አይጠይቅ፡፡ አይከፈልበት...በቃ ይቺን ስለማውቃት ተጠቀምኳት፡፡ የካበተ ልምድ ስላለው አሁን በጥሩ ክፍያ በዚህ ሞያ እንደሚሰራ ሲነግነኝ ከእኔ እጥፍ እያገነ ለምኖ መቃሙ ገረመኝ፡፡ ለነገሩ እዚሀ ሀገር መለማመጥና የሰው ኪስ..ኪስ ማየት የሁሉ ባህሪ እንዲሆን በአዋጅ የታዘዘ ነው የሚመስለው፡፡ ብቻ ጥሩ ይለብሳለ፤ አምሮበታል፡፡ ፊቱ ግን ቡግር ጥሎት በሄደው ጥቁር ጥቁር ነጠብጣብ ተዥጎርጉሯል፡፡ እንዲያውም አፍንጫው ላይ ካለው ማዲያት ጋር ሲታይ የቀለም መቀባት ችሎታውን ተጠቅሞ አብስትራክት ለመስራት ያዥጎረጎረው ይመስላል፡፡ ቡሬ አልኩት በሆዴ...

                                  ሰላም፣ ሻሎም፣     
       

Monday, April 23, 2012


 ስለሜተር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ የማውቀውን እውነታ ለማስጨበጥ አንድ ዙር ጫር..ጫር ያደረኩትን አቋድሻችኋለሁ፡፡ በቀጥታ ወዳቆምኩት ቃለ ምልልስ ከምሄድ ደጋግመን በመገናኘታችን ምክንያት በአንድ ወቅት አስቂኝ ገጠመኝ ነበረ፡፡ በገጣሚ እና የሴት ደራሲያን ማህበር ፕሬዘዳንት በወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን /አሁን ኢንተርፕሪነር ሽፕ ስራ ተሰማርተው በኢቲቪ የሚተላለፈው ስራ ፈጠራ እና ተነሳሽት ውድድሩ ላይ ዳኛ ናቸው፡፡ በነገራችን ላይ ወ/ሮ ሙሉ በዛን ወቅት ነው የሴት ደራሲያን ማህበር ፕሬዘዳንት የነበሩት፡፡ በሌላ አባባል ብዙም ቅርርብ ስለሌለን ነው አንቱ ማለቴ እንጂ የየጥበብ ሰው አንቱ የሚባል ሆኖ አይደለም፡፡/ እና በወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን አስተባባሪነት ለጋዜጠኞች ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት ፈቀዱ፡፡ በሰዓቱ የወ/ሮ ሙሉ አላማ አፈወርቅ ተክሌ ከመገናኛ ብዙሀን ብዙ የራቁ ስለሆነ ለማቀራረብ የተደረገ መንገድ ነው፡፡ ምን ያህል ስኬታማ ሆኗል የሚለውን አላውቅም፡፡ ስለ ስኬቱ እና አሁን ስለማቀርበው ገጠመኝ የሚያስታውሱት ካለ ወ/ሮ ሙሉ እዚህ ላይ ቢጨምሩበት እጠይቃለሁ፡፡

       ጋዜጣዊ መግለጫውን ሊሰጡን ተጠራን፡፡ በቪላ አልፋ ጊቢ ውስጥ ነው ጋዜጣዊ መግለጫው፡፡ በኢቲቪ የአውደሰብ ፕሮግራም አዘጋጅ የሆነ ስለሺ ይሁን ሽመልሽ..ስሙ ተረሳኝ በቴሌቪዥን ፕሮግራሜ ላይ ላቀርቦት ፈልጌ በደብዳቤ ጠይቄዎት እሺ አላሉም፡፡ ከመገናኛ ብዙሀን የሚርቁት እርሶዎ ነዎት አለ…፡፡ ለዘብ ባለ አነጋገር መጀመሪያም ከልብ አልነበረም አጠያየቅህ ጋዜጠኛ ቢጋበትም ያንኳኳል እኮ…አሁን ማነው ምኒልክ የሚባል ጋዜጣ አዘጋጅ አለ፡፡ ስለእኔ ተከታትሎ ነው የሚሰራው መረጃውን ከየት እንደሚያመጣ ሁሉ ይገርመኛል፡፡ አንተ ግን ..መቼ ስሜን እንኳን አስተካክለህ ጽፈህ ነው….እያሉ ሲናገሩ አቋረጥኩና አሁንም አለሁ ጥያቴ አለኝ ስላቸው ሁሉም በሳቅ አደመቁት፡፡

       ወደ ቀረው ቃለ-ምልልስ እናምራ እና በኋላ ትንሽ በሌሎች ጉዳች ላይ እመለሳለሁ፡፡  በዛን ወቅት ሳናግራቸው Great minds of the 21th century የሚል ሽልማት ነበር የተሰጣቸው የአለም ሎሬትነት ማዕረግ ቢሰጣቸውም በየትኛውም የመገናኛ ብዙሀን አለመነገሩ ይገርመኝ ስለነበር ‹‹የአለም ሎሬየት የሚለው ማዕረግ የተሰጠዎት ቅርብ ጊዜ ነው ሲሰጥዎትም ሆነ ከተሰጥዎት በኋላ በመገናኛ ብዙሃን የተሰማ ነገር የለም፡፡ ይታወቃል ብለው ነው ወይስ ያልተሰማበት መንገድ ይኖረዋል?..›› ስል ጠየኳቸው፡፡ መልሳቸውም ‹‹ይሄ ነገር ያልተሰማው እኔ እንደሚመስለኝ ከንቀት የተነሳ ነው፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ መንግስት ቴሌቪዥንና ሬድዮ የሚያስተጋባው የሚታዘውን መሰለኝ፡፡ ያዘዘው ሰው ይኑር አይኑር አላውቅም፡፡ የአለም ሎሬት ለመሆኔ ክሪዲንሺያሉ /ማረጋገጫው/ ያው እዚህ የምታየው ነው..››

    ተነስቼ ዲፕሎማው ወዳለበት በመሄድ አየሁት፡፡ ከበርካታ ሽልማቶች መካከል ልክ እንደ ሌሎቹ ለራሱ በተሰጠው ዙሪያው ወርቅማ ከለር ባለው መስታዎት ፍሬም ውስጥ ተቀምጧል፡፡ ሽልማቶቹን ሳይ ስለ እሳቸው እስክንድር ነጋ የነገረኝ መረጃ ታወሰኝ እና በፍጥነት ዞርኩ፡፡ መጠየቅ ያለብኝ ሰዓት ነበረ እና ጠየኳቸው፡፡ ‹‹ዓለም አቀፋዊ ጉባዔ ላይ ለመገኘት ከነገ ወዲያ ወደ እንግሊዝ ይሄዳሉ በዚህ ጉባዔ መዝጊያ ላይ በታወቁት የታሪክ ተመራማሪ በአርነስት ኪም ስም የተሰየመ ሽልማት አለ፡፡ ለእዛ ሽልማት እጩ ነዎት ይህ ሽልማት ምን አይነት ነው?›› አልኳቸው፡፡

    ‹‹ይህ ሽልማት ክብር ነው፡፡ በገንዘብ በኩል የገንዘብ ተሸላሚነት የለውም፡፡ ለምን አብዛኛውን ጊዜ በሰው አእምሮ ውስጥ የሚኖረው እንደ ኖቬል በብዙ ሚሊዮኖች እና በሺህዎች የሚገኝ ነገር እንዳለ ነው፡፡ አስተዋፅዖው ስምህ ሪኮግናይዝድ መሆኑ ብቻ ነው..›› አሉኝ፡፡ በዚህ ዙሪያ ባለኝ መረጃ መሰረት ‹‹..እርስዎ በዚህ ጉባኤ ላይ አራት ወጥ የፈጠራ ስራዎትን ከ40 ምርጥ የስላይድ ስዕሎች ጋር ይዘው ይሄዳሉ ተብሏል፡፡ ምን ያህል እውነት ነው? ከስራዎችዎ ውስጥስ ለዚህ ጉባኤ እንዲሆኑ ብለው የመረጡበት መስፈርት እንዴት ነው? ከታሪክ፣ ከፈጠራ ምሉዕነት፣ ወይስ ከእነሱ አላማ ጋር የሚሄዱትን አስበው ነው?...›› የሚል ጥያቄዬን ሰነዘርኩ፡፡

     ‹‹ስለአፍሪካ ምንድን ነው አስተዋጽኦ የማደርገው? ስለሀገሬስ ምንድን ነው አስተዋጽኦ የማደርገው? በምልበት ጊዜ መጀመሪያ የኢትዮጵያን ስነ-ጥበብ ታሪክን ማጎልበትና አንዲት ስራ ዛሬ ላይ እንደ ወሬ እንደጫዎታ ሆኖ እኛ ካለፍን በኋላ ስለ እኛ ዘመን አንድ አስተዋጽኦ አድርጌ ማለፍ፡፡ እንደ አክሱም፣ ላሊበላ እንደ ቅርሳችን የሚሆን አንድ ነገር ለማውረስ ነበር፡፡ በዚህ ትግል ውስጥ በዚህ ሂደት ውስጥ ደግሞ አጋጣሚ ሆኖ አፍሪካውያኖች ለነፃነታቸው የሚታገሉበት ጊዜ ነበር፡፡ እና በዚህ ላይ እኔ ምን አስተዋፅዖ አደርጋለሁ? በምልበት ጊዜ ያው በአፍሪካ አዳራሽ የሚገኘው የመስታዎት ስዕል (ዘስትራግል ኤንድ ኦስፕሬሽን ዘ አፍሪካ ፒፕል) የሚለውን ሰራሁ፡፡…›› ይህን አባባላቸውን አሁን ላይ ሆኜ ሳስበው እውነት ለታሪክ፣ ለሀገር የሚቀር ነገር ስርተው አልፈዋል የሚለውን በድፍረት መናገር ያስችላል፡፡

     ስለዚህ ስዕል እና ስለሌሎች ስራዎቻቸው ቀጥለው ያሉኝ ‹‹..በውስጡ ያለው ፍልስፍና፣ የትግሉን ወደ ፊት ተስፋ ምን እንደሆነ እንዴት ማድረግ እንዳለብን ያሳያል ብዬ ከማምነው ስራዬ አንዱ ነው፡፡ በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ እኔ በሰዓሊነቴ ምንድን ነው አስተዋተጽዖ የማደርገው? ይሄው ተማርኩ፣ ታለንትም አለኝ፡፡ ነገር ግን ተመልሼ ሀገሬ በምሰራበት ጊዜ ምንድን ነው አንዱ በሀገር ውስጥ መገኘት ነው፡፡ ሁለት የሀገርን ታሪክ አውቆ ከዚህ ውስጥ ምን መጨመር ይቻላል ብሎ መስራት ነው፡፡ ያንን እውን ለማድረግ መስራት እና በስራዬ መግለጽ ነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያን ታሪክ አንኳር አንኳሩን በዘመናችን መታሰብ ያለባቸውን ወደ 28 ያህል ቴምብሮች ህዝቡም የሚያየው የእኛን ታሪክ በውጭ የሚያሳይ ፣በቀላሉ ሰው እጅ የሚገባ እነሱን መስራት ጀመርኩ፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ ከሚታዩት አንዱ ይሄ ኮሌክሽን ስታምፕ ያለበት ነው፡፡

   ‹‹…ከዚህ በላይ ደግሞ አፍሪካን በሚመለከት ደግሞ እንደዚሁ የአፍሪካ ቅርስ ምንድን ነው? ምንድን ነው የወረስነው? እንዴትስ ነው የምናስተዋውቀው? ወደ ፊትስ ምን መጨመር አለብን? የሚለውን አክዬ የአፍሪካ ቅርፅ (አፍሪካን ሄርቴጅ) የተባለው ዋናው ስራዬ አሁን በብሄራዊ ሙዚየም የሚገኘው ነው፡፡ አፍሪካኖች የታሪክ ደሀ አለመሆናችንን በስራዎቼ ሊያዩ እንዲችሉ፤ የፀሀይ መብራት ሲበራበት የሚታየው ስራዬ ብዙ ሰዎች ከውጭ ሀገር እየመጡ የሚመለከቱት እሱን ነው፡፡
 
     ከዚህ ቀጥሎ ምንድን ነው ሌላው ስራዬ ኮንሰርን ያደረገው የአፍሪካን አንድ መሆን፣ አንድ በመሆን ሰላምን አግኝተን፣ ራሳችን አውቀን፣ እያንዳንዱ ስራ ተገኝቶለት፣ በእኩልነት እና በህብረት፣ ፍቅር የሚጎለብትበት ዘመን ለማየት በስራዬ ጥረት ያደረኩበት ሁኔታ ነው፡፡ ይህ ስራዬ ኦ.ኤ.ዩ ከተመሰረተ በኋላ ኤምብለም ይውጣ በተባለ ጊዜ ያደረኩት ሶስት እጆች የጥቁሩ፣ የጠይሙ፣ የነጩ ተባብሮ አንድነትን ሲፈጥር የፀሀይ ብርሃን ይወጣል፡፡ የፀሀይ ብርሃን የህይወት ዋናው መንቀሳቀሻው ስለሆነ የሚል እሳቤ ነበረኝ፡፡ ከቆየሁ በኋላ ግን የአፍሪካ ህብረት ብቻ መች ይበቃል? የአለም ህብረት መኖር አለበት በሚል ያው እንደሚታየው አራቱ እጆች ተባብረው ሲተሳሰቡ አዲስ ብርሃን ይመጣል፡፡ ይህን እና ይህን የመሳሰሉትን ስራዎቼን በማየት ነው እነዚህ ሰዎች የጋበዙኝ፡፡›› የሚል ምላሽ ሲሰጡኝ ሌላ ጥያቄ አቀበልኳቸው፡፡

   ‹‹..እነዚህ አሁን የጠቃቀሱልኝ ስዕሎች ከእነሱ አላማ ጋር ይዳል ብለው ነው የመረጧቸው? ሽማቱንስ አገኛለሁ ብለው ያስባሉ? ብዬ ጠየኳቸው፡፡ በእርግጥ በነበረኝ መረጃ መሰረት ያ-ፋውንዴሽን በቂ ያለውን ሰው ያጫል ድምጽ ይሰጣሉ፣ ይሸልማሉ፡፡
 
    ‹‹እንግዲህ እዚህ ላይ ግልጽ ይመስለኛል›› አሉ እና በስላይድ ካዘጋጁት ስዕል ውስጥ የተወሰነውን አሳዩኝ፡፡ ቡርሽ ቤቷን አውቃ ገብታለች የሚል እሳቤ ውስጤ ተላወሰ፡፡ ልክ ነበርኩ፡፡ እሳቸው የተጠበቡት እያሉ እኔ ለማየት በመብቃቴ ኮራሁ፡፡ የምጣዱ እያለ የእንቅቡ ተንጣጣ ማለት ይሄኔ ነው፡፡ ውስጤ ያልነበረ ስዕል የመስራት ፍቅር ያኔ ተወልዶ አደገ፡፡ ለነገሩ የአለም ዋንጫ ሰሞን ሁሉ ኳስ ተጫዋች መሆን ያስብ የለ? የእኔም ሀሳብ ከዛ አልዘለለም፡፡ ያሳዩኝን ሲጨርሱ የሰጡኝ መልስ….

   ‹‹እነሱ እኔን ለመጋበዝ ያላቸው ምክንያት ስራዎቼ ከእነሱ አላማ ጋር የገጠመ በመሆኑ እና አሁንም ይሄ ሰውዬ ራሱ/አርነስት ኪይ/ የአለምን እንደዚህ አይነት ነገር አስተዋፅዖ የሚያደርጉትን ሰዎች በመብራት እየፈለገ ታሪካቸውን ይፅፍ ስለነበር እሱ በአረፈ ጊዜ በስሙ ይሄ ፋውንዴሽን ተመሰረተ፡፡ በኮንግተረሱ ላይ የሚገኙት አብዛኛዎቹ ኢንቨስትጌትድ ናቸው፡፡ በእነሱ መካከል ይሄን አላማ በፈጠራ ስራው ያራምዳል የሚሉትን የዛ ፋውንዴሽን ሴኔት ሽልማት ይሰጣል፡፡ እኔ ራሴም ኮንግረሱ ላይ እሄዳለሁ እንጂ ለዚህ ሽልማት እበቃለሁ ብዬ በሀሳቤ የለም፡፡›› አሉኝ፡፡ ቢሆንም ግን ሽልማቱን ተቀብለው ከመጡ በኋላ ተገናኝተን ‹‹ይበልጥ እንድሰራ ያበረታታኛል እንጂ አያሰንፈኝም፡፡›› ብለውኛል፡፡ ቃለ-ምልልሱን በደረግንበት ወቅት እስካሁን ከተሸለሙት ውስጥ የትኛውን ይበልጥ ይወዱታል? የትኛው ነው የበለጠ ክብርስ ያለው? ብያቸው ነበር፡፡ ማበላለጥ ይከብዳል ሁሉም የሚሸልሙህ ስራህን ወደው አክብረውህ እስከሆነ ድረስ አንተም የሸለሙህን ልታከብረው ግድ ይላል፡፡ ቢሆንም ግን ዋጋቸው /ክብራቸው ይለያያል፡፡ እኔ በመሸለሜ ይበልጥ ደስ ያለኝ.. The International Biographical Center of Cambridge በስነ ሙያ ጥበብ የመጨረሻ ሽልማት የሆነውን Davinci Diamond የደቬንቺ አልማዝ የተባለው ሽልማት ለእኔ ልዩ ነው።

    ከዛ በላይም The United Cultural Convention of the United States of America የተባለው ማዕከል International Peace Prize ልዩ ሽልማትና፣ የክብር የሰላም አምባሳደርነትን ሰጥቶኛል፡፡ Great minds of the 21th century የሚል ሽልማት አግኝቻለሁ፡፡ ይህም ትልቅ ክብር ያለው ነው፡፡ በተቀረ የምጠላው ሽልማት የለኝም፡፡ ቢኖር አልቀበልም ነበር፡፡ ይህች አባባላቸው ፈገግ አድረጋኛለች፡፡

    እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ እንደ ጥበብ ሰውነታቸው በጥንታዊት ኢትዮጵያ ታሪክ፣ ነጻነት፣ ባሕልና ሥልጣኔ እንዲሁም በግዕዝ ቋንቋ፣ በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖታቸው አስተምህሮ፣ ትውፊትና ስርዓት በእጅጉ የሚኮሩ ናቸው፡፡ ለኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖታቸው የነበራቸውን ጥልቅ ፍቅርና ክብር ከገለጹባቸው መካከልም የአራዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የመቅደሱ፣ ግድግዳዎች የሌሎችም በርካታ አድባራት የእሳቸው የጥበብ ትሩፋታቸውን ያረፉባቸው እንደሆን ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት ባሳተሙት የህይወት ታሪካቸው ላይ ሰፍሮ ይገኛል፡፡
           እግዚአብሄር ነፍሳቸውን በገነት ያኑራት


ልጅነትና ትዝታውን ማንሳት ከጀመርኩ የፓስቲ /የጉራጌ ብስኩት/ ለሰባት አመቴ ጥርስ መነቀል አስተዋጽኦ ያደረገውን ከተናገርኩ ለዛችው ፓስቲ ብዬ ሳንቲም ሰርቄ መገረፌን ሳላነሳት ማለፍ አልፈልግም። ቀበሌ ህብረት ሱቅ ግዛ ተብዬ ስላክ ሳንቲም መቀርጨጭን ስለለመድኩ ሁሌ እንድላክ የማላደርገው ጥረት የለም። ተሳክቶ ስላክ ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ ጋር ወጣት አበባ ሻይ ቤትን የሚያውቅ እዛ ያለ ብስኩትን ያውቃል። ታዲያ አንድዋን ቀድሜ አጣጣምኩና ሄድኩ። ህብረት ሱቅ ግን የዛን ቀን ብጥብጥ ስለተነሳ ለልጆች አንሰጥም ተባለ እና መለሱኝ። ከተሰጠኝ ገንዘብ ደሞ አጉድያለሁ።

ነገር መጣ።

ቤት እንደገባሁ ከተላኩበት ብር ላይ ልጆች አንዱን ነጠቁኝ አልኩና የቀረችውን ደበኩዋት። ትንሽ ቆይቼ ወጣሁ እና ብስኩቴን ገዝቼ ሳሻምድ እናቴ ለካ ቀበሌ ህብረት ሱቅ ለመሄድ ወጥታለች። አየችኝ። ዱላው የጠበቀኝ ግን ማታ ነው።

እንደወናፍ ቆዳ ታሸሁ።

ከዛ በሁዋላ አልሰረኩም ማለት አይደለም። ብሰኩት ጠባሹ አረቦ እስከሞተበት ጊዜ ድረስ የዛ ቤት ቋሚ ተሰላፊ ነኝ። ክርስትና ስነሳ እንጃራ ይውጣልህ ተብዬ ሳይሆን የጉራጌ ብስኩት ይውጣልህ ተብዬ ነው መሰል የተመረቅሁት -እወደዋለሁ። አሁንም እወዳለሁ። የምትችሉ ላኩልኝ።

ትላልቅ ሴቶች ህጻናት ወንዶችን እንደሚያባልጉ ያወኩበት አጋጣሚ ደግሞ እነሆ፦ የምስራች ትባላለች ዛሬ..ዛሬ ትዳር ይዛ መውለድዋን አውቃለሁ። እሷ ትረሳው ይሆናል። እኔ ግን አልረሳትም። ጠባሳ የጣለብኝ ነገር አለውና ነው። አስታውሳለሁ ያኔ ገና ስምንት አመቴ ነበር እና ልላክህ ስትለኝ ቤታቸው ገባሁ። እኔ መግባቴን ያየው ዳንኤል እየጠራኝ ተከትሎኝ ገባ። ዳኒ የያኔውን ነገር ታሰታውሳለህ?/ዳኒ ሽኒ ዝተፈጠረ ትርሰኦ አይመስለን/ ቂጣ በዘይት እና በርበሬ የታሸ ለሁለታችን አበላችን። እያጫወተችን ያደረገችውን ነገር ዛሬ እዚህ ቦታ ላይ ባልጽፈውም ለሁላችሁም የሚገባ ነገር ነው። ድርጊቱ አስጠሊታ ስለሆነ ነው የደፈንኩት።

እኔ፣ ባይከዳኝ፣ ዳዊት፣ ተካልኝ፣ታምራት…ሌሎቹም በየጊቢው ያሉትን የኮክ እና የፖም ፍሬዎች በማደን ለራሳችን ደስታ እንፈጥር ነበር። ቅንጨ ጊቢ..አዳነች ጊቢ..የቀበሌው መዋለ ሀጻናት ጊቢ..ናዘሬት ት/ቤት አካባቢ ያሉ የሀብታም ጊቢዎች በየተራ እናዳርሳቸዋለን። ታዲያ አንዴ አዳነች ጊቢ የምንለው ጋር በአጥር ተንጠላጥለን ኮክ ዛፍ ላይ ወጣን። በርካታ ውሻዎች አሉ። እየጮሁ አስቸገሩን አንዱን ትል የበላው ኮክ ቀጠፍኩና ውሻው ላይ እወረውራለሁ ብዬ ካለሁበት ዛፍ ላይ ስቼ ወደኩ።

ውሻው ነከሰኝ።

ህክምና ስሄድ ውሻው ተገድሎ ለምርመራ እንዲመጣ ተባለ። ተደረገ። ለካ በሽተኛ ነው። ሆዴ ላይ 43 መርፌዬን ጠጣሁ። ለኮክ ተብሎ..አይ ልጅነት? ደስ ይላል። ሆዴን ሳይ ሁሌ አስበዋለሁ። ሌላው ደሞ እንደ ልጅ ሆያ ሆዬ መጨፈርም ሆነ ለአበባዮሆሽ አበባ መስጠት እከለከል ነበር። እናቴ ለምን እንደሆነ አላውቅም አትወድም። አንዴ ተደብቄ ስጨፍር ቆየሁና የተካፈልነውን ሳንቲም እንደሌላ ጊዜው በወረቀት ጠቅልዬ ሳልደብቅ ረስቼ ገባሁ። ሳንቲሙ ተገኘብኝና ተደበድቤ ሲበቃ በርበሬ ታጠንኩ። መቼም የደረሰበት ያውቀዋል። አቤት ስቃይ!! ከዛ በሁዋላ ሆያ ሆዬ የሚል ዘፈን እንኩዋን ሰሰማ ያቅለሸልሸኛል። በርበሬዋ ትዝ ትለኛለች።

ብዙውን ጊዜ እናቴን በስራ እረዳታለሁ። አባቴ ከሞተ በሁዋላ እንጀራ ሸጣ ስለሆነ ያሳደገችኝ አዝንላታለሁ። እንጨትና ቅጠል እገዛላታለሁ፤ እህል ገዝቼ አሰፈጫለሁ፤ እንጀራውን ተሸክሜ ያኔ ሺረጋ ሆቴል ይባል የነበረው አራት ኪሎ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት አጠገብ እወስድላታለሁ። ጉሊትም አደርስላታለሁ። በዛ ያለ ጊዜዬን እስዋን ስራ ሳግዛት ደስ ይለኛል። ይህን በስራ ማገዝ እንጀራ መሸጡን እስካስቆምኩዋት ድረስ ዩንቨርስቲ ተማሪ ሆኜ ሁሉ አላቋረጥኩም።
ልጅነት፣ አይናፋርነት እና ፍቅርን በተመለከተ በክፍል 4 እመለስበትና እንሰነባበታለን።
ስላም ለእናንተ፣ ሰላም ለእኔ፣ ሰላም ለፌስ ቡክ ወዳጆቼ፣ ሰላም ለማውቃችሁ፣ ሰላም ለማላውቃችሁ…ሰላም ገና ወደፊት ለማውቃችሁ ሁሉ እንዲሆን እመኛለሁ።
ቸር እንሰንብት
 

ፍል ሁለት
አቦ ተመቸኝ

<<የአንተ አባት ምን አይነት ነው? የእኔ አባት ቀይ ረጅም ሽበታም ነው..የአውራ ጎዳና መኪና ይነዳል ትልቅ የነዳጅ ቦቲ..>> በጥሞና ሲያዳምጠኝ ቆይቶ <<የእኔም አባት አንተ እንደምትለው ነው ብዙ ጊዜ ክፍለ ሀገር ነው።ግን ትላንት ማታ መጥቶ ነበር።..>> አለና የቲቸር ሳያንስ እሱም ጥርጣሬ አርሶ ስለዘራብኝ ቤቴ ልወስደው አሰብኩ። ወደቤት ስወስደው ነገር ተገለብጦ ..ለእሱ እኔ ውጭ የተወለድኩ ወንድሙ ነኝ። እሱ ለእኔ ከውጭ የተወለደ ወንድሜ ነው። አራዳው ፋዘር አራርቆ መውለድ ሲባል ተሸልቅቆ አቀራርቦ አንድ ሰፈር በስድስት ወር ልዩነት ከች አርጎናል። ታላቅነቴን ግን አልተነጠኩም። ብራቮ አባቴ ብኩርናዬን ስላላስነጠከኝ።
በቃ!! ተዋደድን ምንስ ቢሆን ወንድሜ አይደል? የአንዱ ሲገርመኝ እሱስ ታናሽ ወንድምም አለው።አንድ ብቻ የነበረው ታላቅ ወንድሜ ታናሾቹ በረከትንለት።ያኔ ነው አሁንማ ታላቅ ወንድሜ በስደት እያለሁ በሞት ተለየኝ።ድምጻችሁን ዝቅ አድርጋቸሁ ነፍስ ይማር በሉ። ውሎዬ ከጓደኞቼ ይልቅ ከወንድሜ ጋር ሆነ። ከወንደሜም ጋር ሆኜ ተካልኝ ተክሌ፣ታምራት ተክሌ፣ባይከዳኝ..የአባቱን ስም አላውቅም እሱም ሲናገር ሰምቼው አላውቅም። ቅዳሜ..ቅዳሜ መርካቶ እንሄድና ሲኒማ አዲስ ከተማ እንገባለን። በ50 ሳንቲም ሶስት ፊልም እናያለን፤ብዙ ስቃይ እንቅብላለን። ወረፋ ላይ ዱላ እንቀምሳልን፤መሬት ተቀምጠን ሽንት በቂጣችን ስር ሲሽኳለል ይውላል። የሲጋራ ትርኳሽ ሲወረወር ላያችን ካረፈ እንቃጠላለን። ብቻ ሁሉም ያኔ አሁን ያራዳ ልጅ ትሪፕ እንደሚለው ነው።

ፊልሙ አልቆ ስንወጣ ስለፊልሙ አክተሩ እንዲህ አለና እንዲህ ብሎት..አይደለም እንዲህ ነው ያለው/ትርጉም በራሳችን ክርክር ለመንገዳችን/ እየተዳረቅን በሲኒማ ራስ ቴያትር በኩል አቋርጠን ወደ ሰፈር በእግር እንጓዛለን።ሁሌም ከፊልም መልስ በሲኒማ ራስ በኩል የምንሄደው በአምስት ሳንቲም የምትሸጥ ሳንቡሳ ስላለ እሱዋን ለመብላት ነው። የቻልነውን ያህልም እንሰርቃለን። እኔ ግን ከሳንቡሳ ስርቆት ይልቅ አራዳ ጊዮርጊስ ጋር የመጽሐፍ ስርቆት ይቀናኝ ነበር። አነብና መልሼ ሸጨ ለቅዳሜ ፊልሜ እና ለሳንቡሳ አውለዋለሁ። ሳንቡሳ መብላት ውድድርም አለ። ግን የሪኮርዶ ባለቤት ባይከዳኝ ነው።የበላውም መጠን ብረሳውም 20 ይመስለኛል።ካሳነስኩት ግን ይቅርታ ባይኬ…ይህን ስላችሁ አፉን ሸፈፍ ድርጎ <<ኤኔ ሲሜ ባይኬ..>> የሚላት አባባል ታወሰችኝ።

አንድ ጊዜ ቀኑ ቅዳሜ ስለሆነ ተካልኝ እና ወንድሙ ታምራት እናታቸው ለፊልም ሰጥታቸው ሊሄዱ ነው። እኔ፣ባይከዳኝ፣ዳዊት..የምንገባበት የለንም። ቅዳሜ..ቅዳሜ ድሞ ሰፈራችን ያለ ሻፊ የሚባል ከሰል ነጋዴ ንፍሮ አስለምዶናል። ንፍሮው ዝም ብሎ እንዳይመስላችሁ። ዘይት አለው ስንኩርት አለው። ከፈለጋችሁ እናንተ ነፍሮ ወጥ በሉት። እኛ ጥሞን ተጋፍተን ነው አንዳንድ ጭልፋ በሹራባችን ተቀብለን ድጌ ሁላ የምንሄደው። ችግሩ ሻፊ አይሸለቀቅም።

ውይ የእኔ ነገር ንፍሮው ታወሰኝ እና ተዘናጋሁ። እናላችሁ የለመድነውን ንፍሮ እሱ ሊሰጠን አኛም ልነቀበል የሰጪና ተቀባይ ፕሮሰስ ላይ እያለን ገንዘቡን ፊት ለፊት በጣሳ ተቀምጧል። ለባይከደኝ እኔ ሸፈንኩለት አነሳው። ሸኛ ፊልም ገብተን ሻፊ ምን ተረፈኝ ታንቄ እሞታለሁ ብሎ እንደነበር ስሰማ ተጸጸትኩ።

ያኔ አባቴ በህይወት እያለ ነው። ጓደኞቼ ሞጋ/በረባሶ/ የሚባለውን ከጎማ የሚሰራ ጫማ ፊት በር ገበያ እየሄዱ ያሰራሉ። እኔም ቀናሁና አሰራሁ። አቤት የተመታሁት? ለስፖርት ሸራ ጫማ አስገዝቼ አባቴ እናቴን የተቆጣትን አልረሳውም። ሌላ ጊዜ ግን እሱ ሞቶ አድርጌያለሁ። የጉራጌ ብስኩት ነብሴ እስከወጣ እወዳለሁ፡፡ሳንቲም እሰርቅና እገዛለሁ። ከዚህ ጋር የተያያዘ ገጠመኜ ሰባት አመቴ ላይ እንደ ልጅ በወግ ጥርሴ ተነቃንቆ በክር ተጎተቶ አይደለም የወለቀው ፓሰቲ የሚባለውን ደቡልቡል ኳስ የሚመስል የጉራጌ ብስኩት ስገምጥ ስክት ብሎ ቀረ። ጣጣ የለ ፈንጣጣ ውልቅ..ብቻ ብስኩቴን ደም ነካውና ጨርሼ ላጣጥም አልቻልኩም::እሷ ትቆጨኛለች::
ወደ ት/ቤት ገጠመኜ ስመለስ
አንድ ጊዜ ከምንቀርባቸው ውስጥ አንዷ እወድሀለሁ ብላኝ አስታውሳልሁ ሁለት ቀን ከት/ቤት ቀርቻለሁ። ብትስመኝ ኖሮ ከት/ቤት ከናካቴው ሳቋርጥ አይታያችሁም? በጣም አይናፋር ነበርኩ-የዛሬን አያርገውና። ዛሬ እሷ በውጭው አለም ታዋቂ ሞዴሊስት ሆና ፌስቡክ ዳግም አገናኝቶናል። ለነገሩ ከልጅነት ጓደኞቼ መካከል ከጌትሽም፣ከተካልኝም፣ከካሳሁን የሺጥላ ጋርም ፌስቡክ አገናኝቶናል። ተካልኝ ስዊዲን፣ካሳሁን አሜሪካ ከትመዋል።
ወደ ያኔ ወጌ ስመለስ…ያኔ ጓደኛ እንባባላለን እንጂ ምንም የምናውቀው ነገር የለም ነበር። ሳባን የእህቴ ያህል እወዳታለሁ። ዛሬ የልጆች እናት መሆኗን ከመስማት ውጭ የት እንዳለች አላውቅም። ኮኮበ ጽብሃ ከገባን ጊዜ ጀምሮ አላገኘዋትም።
ኮኮበ ጽበሃ ስንማር ለአውቶቡሰ የሚሰጠንን ቀበና ያለችው ሻይ ቤት የጉራጌ ብስኩት እንበላባትና በእግር <<እሰኪ ልወዝወዘው ልወዝወዘው በእግሬን..>> አያንጎራጎርን እናስነካዋለን፡፡ እኔና ጌትሽ ያችን ብስኩት ለመብላት ብቻ ሳይሆን ከሳምሶም ዳቦ ቤት ባለ 20 ሳንቲም ዳቦ ገዝተን ልክ እንደኬክ በወረቅት ይዘን እያጓመጥን መንገዱን እናስነካዋለን::ዳቦ በሙዝ..ሎሚ በከረሜላ..የማይታወሰው አለ ይሆን?

የልጅነት ታሪካችን ቢውራ..ቢወራ የሚያልቅ አይደለም። ቀጣዩን ክፍል ሶስት እመለስበታልሁ። ከደበራቸሁ ግን አስተያየት መስጫው ላይ x ምልክት አስቀምጡ::ከተመቻቸሁ ጭብጨባችሁን አሰሙኝ። ወደፊት እንላለን።
ቸር እንሰንብት
 —
ስለ ልጅነቴ እውነት እውነቱን እናውራ ካልኩ ብዙ ደስ የሚል ባይሆንም በድህነታችን ላይ የተመረኮዘ ጦሽ..ጧ../ባያስቅም ለሞራሌ ስትሉ ሳቁ/ የሚያደርግ ወግ አወጋችሁዋለሁ።ጆሮዎትን ለመስማት አቀባብሉና አበድሩኝ። ተኖረና ተሞተ ያሉት የአለቃ ገ/ሀናን አይነት ህይወት ባይሆንም አኛም ሰፈር ተኖሯል። ምን ይጠበሰ እንዳይሉ..አሳ እንዳልል ተወልጄ ያደከበት ሰፈር አሳ በስህተት ካልሆነ አይገባም። ወንዝ የለ ሀይቅ የለ ከየት ይመጣል?የአሳ ስዕሉን እንኳን ይዞ መገኘት ሰው በማጓጓት እና ምራቅ በማሰዋጥ ወንጀል ያሰከስሳል። 4ኪሎ እና 6 ኪሎ መሀል 5 ኪሎ ብለው ይጠሩታል፡፡ ማን መዘነው እንደትሉኝ ተወለድከበት አልኩ እንጂ መሰረትኩት አላልኩም።

ዘውዱ አዲስ፣ነብዩ ሀይሉ፣ወንደሰን ሰብስቤ፣ ዳንኤል መሀሪ..ተወልጄ ያደኩበት ጊቢ ያሉ ልጆች ናቸው። የረሳሁዋችሁ አትቀየሙ። አንተነህ ፑሲን ግን አልረሳሁም።ዛሬ ዘውዱ አሜሪካን በዲቪ ሰበብ ከትሟል። ነብዩ እና ወንደሰን የት እንዳሉ አላውቅም። የት ናችሁ ከሰማችሁ አለን በሉኝ። ዳንኤል ግን ኤርትራዊ ስለሆነ መውጣቱን አውቃለሁ እንጂ የት አንዳለ ምንም መረጃ የለኝም። ዳንኤል ይህችን መጣጥፍ ካገኘሀት ሰላምታዬን ማድረሴ ብቻ ሳይሆን ዘውትር እንደማስብህ ተረዳ። /ማኸዛይ ኩሉ ጊዜ ይዝክረካ-ሰላም ንዓካ/ ብዙ ትዝታ ያለኝ ግን ከጌታሁን መሳፍንት፣ከተካልኝ ተክሌ፣ከቀìላ ሲሳይ፣ከካሳሁን የሺጥላ፣ሳሙኤል ብስራት..ታዩ…ሽፈራሁ ሀብቴ፣ካሳሁን መኮንን.. ሰይፈ ጌታቸው….ብዙ ነን። ሰይፈ ነፍሱን ይማር በሞት ተለይቶናል።

ከነዚህ ውሰጥ ጌታሁንን ከሁሉም ይበልጥ እወደዋለሁ። ጌትሽ አጭር እና ቀጭን በመሆኑ እንዝርት የሚል ቅêል ስም አለው። እኔ ድንጋይ ስወረውር ባለመሳቴ ጠጅቱ የምትባል የሰፈር ሰው ቦምቤ አለችኝ። ይህች ቅêል ስም ከራሴ መተለቅ ጋር ተያያዘችና ቦምብራስ የምትል ታፔላም ሆና ነበር። ትንንሽ ቦምብ መኖሩን ቢያውቁ ስያሜውን ይፍቁልኝ ነበር። አባቴ ሁሌም ሱፍ ሱሪና ኮት ያሰፋልን ስለነበር ከበተር ፍላይ ከረባት ጋር ስለማደርግ እና ካቆሸሽኩ ሰለምገረፍ ጓደኞቼ ኳስ ሲጫወቱ እኔ ቁጭ ብዬ ስለማይ አካሄዴንም ጨምሮ ባንታለም ሰብስቤ ሚኒስቴር የሚል ቅêል ስም አውጥቶልኛል። ሁለት በሉ።

ከጌታሁን ጋር ትምሀርትም አብረን ነው የምንማረው። አርመን/አሁን ብሔራዊ ቤተመንግስት/ የሚባለው ት/ቤት ነው የተማርነው። ብሩክታይት አሰፋ..አሁን ካናዳ አለች የፒያሳ ሰራተኛ ሰፈር ልጅ፣..ፍሬህይወት አጥላባቸው.. ሳባ ተርዲ የሚባሉ የምንቀርባቸው ልጆች ናቸው። ሳባ ተርዲ ለጌትሽ ሴት ጓደኛው ነበረች። ሁለተኛ ክፍል ተማሪ እያለሁ የገጠመኝን መዓት ላውጋችሁ ፦ ቲችር አበበ የምንላቸው አንድ እግራቸው አጠር ያለ የክፍል ሀላፊያችን በአንደኛ ሴሚስተር አንደኛ መውጣቴን ገልጠው ሰርተፊኬቴን ሲያቀብሉኝ አሰጨበጨቡልኝ። እግዚአብሔር ይስጣቸውና ያኔ ባያስጨበጭቡልኝ ኖሮ ሳይጨበጨብልኝ እሞት ነበር። ከዛ በሁዋላ ጭብጨባን ዳግም አላገኘሁትም። ለማየት እንኳን ምክር ቤት እሱንም በቴሌቪዥን ነው የማየው። ቀጠሉና ሁለተኛ ለወጣው መስፍን ተ/ሀይማኖት ሰርተፊኬቱን ካቀበሉ በሁዋላ አጫሽ ስለሆኑ ሁሌ ያስላሉ። በሳል የታጀበ ጥያቄ መረቁለት።

<<..ወንድማማቾች ናችሁ?>> ጢም የከበበው አፋቸውን ሞጥሞጥ አድርገው ሲያፈጡብኝ ፈራሁ እንጂ <<..በአማርኛ ክፍለ ጊዜ ላይ ያስተማሩንን አዛምድ እኛ ላይ ሊሞክሩት ነው እንዴ?እኛ ቤተ ሙከራ ያለ አይጥ ነን >> ልላቸው አሰብኩ። ምን ያደርጋል ስለምፈራ ፍርሃቴን ተሸክሜ ቀረሁ። እሳቸው ግን ድፍረት አገኙና በአንካሳ እግራቸው ከፍ ዝቅ እያሉበት ብላክቦርዱ ጋር ቆመው እያስተዋሉን <<..ደሞ በመልክም ትመሳሰላላቸሁ..>> ሲሉ ሽርደዳ የሚመስል ቃላት መረቁልን። አሁን የማላስታውሰው ስድብ በውስጤ ሰደብኳቸው። ለነገሩ እንኳን አላስታወስኩት የስድብ ጥሩ የለው። ነብሳቸው ይማረውና በመጥፎ ድርጊት ስለሚታሙ በሱው የሰደበኩዋቸው መሰለኝ። ሁሌም አውቶቡስ ላይ ከሴቶች ሁዋላ ቆመው ይተሻሹና..አንድ ጊዜ አንድ ሴትዬ እንትናቸውን ይዛ ስትጎትታቸው በዓይኔ አይቻለሁ። ከዚህ የራቀ አልሰደበኩዋቸውም። ከፈለጉ ራሳቸው አያስታውሱ እኔ ምን አቀጣቀጠን? አባቴን ዋልጌ አድርገው ከእናቴ ውጭ እንደወለደ ለምን አሰቡ ብዬ ነው መሳደቤ።

ከውስጥ ኔትወርካችን ተገናኝቶ ይሁን ተጠላልፎ ድንገት ሳናውቀው እኩል <<አይደለንም>> አልናቸው። አልተዋጠላቸውም። እንኳን ሊዋጥላቸው ከጆሯቸውም የገባ ሳይመስሉ << ለማንኛውም ተጠያየቁ>> የሚል ማሳሰቢያ ቢጤ ወርውረው ሰርተፊኬት ማደል ቀጠሉ። አጠገቤ የተቀመጠው አላዛር ነጋሽን ቢሉ የሁለታችንም ራሰ ጠበደል በመሆኑ ሊያመሳስሉን ይችላሉ የሚል እሳቤ ከማሰቢያዬ ውስጥ ስንቅር አለ። እስክንወጣ ተነቆራጥጨ ጠበኩ። ስንወጣ መስፍንን በጥያቄ አጣደፍኩት።
<<የአንተ አባት ምን አይነት ነው? የእኔ አባት ቀይ ረጅም ሽበታም ነው..የአውራ ጎዳና መኪና ይነዳል ትልቅ የነዳጅ ቦቲ..>> በጥሞና ሲያዳምጠኝ ቆይቶ <<የእኔም አባት አንተ እንደምትለው ነው ብዙ ጊዜ ክፍለ ሀገር ነው።ግን ትላንት ማታ መጥቶ ነበር።..>> አለና የቲቸር ሳያንስ እሱም ጥርጣሬ አርሶ ስለዘራብኝ ቤቴ ልወስደው አሰብኩ።

የልጅነት ታሪካችን ቢውራ..ቢወራ የሚያልቅ አይደለም። ቀጣዩን ሳምንት እመለስበታልሁ። ከደበራቸሁ ግን ገትረው በሉኝ።እገትረውና ቴዘር ትጫወቱብታላችሁ። ከተመቻቸሁ ጭብጨባችሁን አሰሙኝ። ወደፊት እንላለን።
ቸር እንሰንብት

Sunday, April 22, 2012


 ወግ በግሩም ተ/ሀይማኖት
(ክፍል 3)

   መጥቻለሁ ወዳጆቼ…የእኔ ነገር መጣሁ ብዬ አስጠበኳችሁ አይደል? ምን  ብዬ ነበር ያቋረጥኩት? ‹‹…ምን ባጠፋሁ ነው የእናቴን ገበር ምጣድ በሚያክል እጁ በጥፊ የከደነብኝ፡፡ አሁን ሳስበው ያኔ ይቺ ድንቡሎ ፊቴ እሱ እጅ ላይ ስታርፍ የቡሄ ሙልሙል መስላ ይሆን? ምነው ያኔ ፎቶ ባነሱኝ ነበር፡፡ እኔ ወድቄ እሱ ለያዥ ገናዥ አስቸገረ…›› ማለቴን አስታውሳለሁ፡፡

    ተጣጥቤ ስመለስ ከንፈሬ ከበደኝ፡፡ አብጦ ማር የተሞላ ስልቻ መስሎ ተወጠረላችሁ፡፡ እንኳን ዘንቦብሽ እንዲያውም ጤዛ ነሽ ነው ነገሩ..እንኳን ቡጢ አርፎበት ቀድሞም ደባደቦ ከንፈር የሚባለው አይነት ነበረ፡፡ ኪሎ ስጋ አፌ ላይ ለጥፌ የምዞር ያህል ከበደኝ፡፡ አይ የኔ ነገር መቼም አያምርብኝ..እኔን ብሎ ጠባሽ፡፡ ምነው ባልጠብስስ..ራሴ በቦክስ ከምጠበስ? ተጣጥቤ እንደመጣሁ ሳየው ይባስ ብርክ ያዘኝ..ፈርቼ እንዳይመስላቸሁ ወንድነቴ መጥቶብኝ ነው፡፡ ታዲያ ሰው ፊት ያን የሚያክል ቡጢ አሳርፎብኛል አይደል? /ቡጢ ይሁን ጥፊ  ስለተምታታብኝ እናንተ ደስ ያላችሁን በሉት/ የሰዉ ሁሉ አይን እኔ ላይ ሲያርፍ እንድደባደብ እየተበቁ መሆኑ ገባኝ፡፡ ሊገላግሉ የተዘጋጁ ሁሉ ነበሩ…

     ፈሪ ለእናቱ በውስጤ ያዜምኳት ዜማ ነች፡፡ ‹‹እንገናኛለን አሁን የሰው ሰርግ አልበጠብጥም..›› ብዬ ዛትኩና ወደ ጭፈራዬ ላመራ አሰብኩ፡፡ በኋላማ ስሰማ ለካ ፍቅረኛው ነች፡፡ እሷ ቹዝ ዘ ቤስት ልትል ማማረጫ ይሁን አጫፋሪ ብቻ ያጨችኝ እሷ እና ፈጣሪ ይወቁት፡፡ ልጨፍር ስሞክር ጉልቻ ያከለው ከንፈሬ ወደ ፊት ሊደፋኝ አዘነበለ፡፡ ቅሌት ብርቄ አይደል ብዬ ከሚሳቅብኝ ሹልክ ብዬ ወደቤቴ ነዋ!...፡፡ ብቸኝነቴ ይሻላል ከቡጢ አልኩና ለእራት የሚሆን ፎሰሊያ በእንቁላል /ማልቤድ/ ገዝቼ ገባሁ፡፡ እናንተዬ ቤት ስገባ ጭር ብሎ አሳነባሪ ሆድ ውስጥ የምገባ መሰለኝ፡፡ ቅዝቃዜው ፍሪጅ ውስጥ የማድር ቢያስመስለኝ አይፈረድም፡፡ የሙቀት ሞተር የምትሆን ‹‹ፍቅሬ›› ብላ እቅፍ የምታደርግ የግራ ጎኔን አጠንክሬ ማፈላለግ እንዳለብኝ ግን አመንኩ፡፡

    በሳምንቱ ፍለጋው አያልቅም እያልኩ አንድ ሀሙስ ሀሙስ እየተሰባሰቡ የሚቅሙበት ቤት ሄድኩ፡፡ አንድ ክፍል ቤቷ ተጨናንቃለች፡፡ ዛሬ ቀኑ ሀሙስ በመሆኑ በርካታ እንግዶች አሉባት፡፡ ሀሙስ ሀሙስ የእሷ ቤት ሁሌም በሰው እንደተሞላ ነው፡፡ የመን ውስጥ ከቀኖች ሁሉ ሀሙስ ልዩ ማዕረግ አለው፡፡ ‹‹አሊዮም ከሚስ›› ይላሉ የመናዊያኑ፡፡ ዛሬ ሀሙስ ነው ማለታቸው ነው፡፡ በዚህ እለት ሚስቶች ለባሎቻቸው የማይሆኑት የለም፡፡ በየቤቱ በየቀኑ የሚቃም ቢሆንም የሀሙሱ አቃቃም ይለያል፡፡ ይህን ባህል ሀበሻው ለመቀበል አልከበደውም፡፡ እኛ ዘንድስ ሀሙስ የቀን ቅዱስ እያልን እናንቋለጳጵሰው የለ? ደግሞስ የትኛውም ቦታ ላይ መጥፎ ነገር እንጂ ጥሩ ነገር አንኮርጅም እኮ!!!

   የሄድኩባት ልጅ መስከረም ትባላለች፡፡ የአመት መጀመሪያ ሳይሆን መጨረሻ ነው የሚመስለው ፊቷ፡፡ ጨፍጋጋ ነገር ነች፡፡ ህይወቷ በተደጋጋሚ በአንድ ምህዋር የሚሽከረከር ነው፡፡ጠዋት ወደ ስራ ትሄዳለች፣ ከስራ ስትመጣ ጓደኞቿ ጋር እየዞረች ጫት ትቅማለች፣ሺሻ ታጨሳለች ሲነጋ ስራ ትሄዳለች፡፡ በቃ! ሁሌም ይሄው ነው፡፡ ሀሙስ እሷ ቤት ነው ተራው፡፡ ሀሙስ ሀሙስ ሁሌም የቤቷ እና የእሷ ንጽህና የተለየ ነው፡፡ እንደ እድል ሆኖ የእሷ ሀሙስ ፍቅረኛም ሆነ የትዳር ጓደኛ አላመጣላትም፡፡ ቢያመጣላትም አልበረከተላትም፡፡ ለትዳር ሳይሆን ለአዳር ህብረ አንሶላ የሚፈጥር ግን ደጋግሞ ገጥሟታል፡፡ ‹‹ይሄንንስ ማን አየው? ጦም ከማደር ያገኙትን መቀርቀር..›› የምትለው ፍሬከርስኪ አባባል አላት፡፡ የየእለቱን ስታሳድድ ሳይነጋ እየጨለመባት እድሜዋ ሽምጥ እየጋለበባት መሆኑ አልታወቃትም፡፡ የኋላ ኋላ ከፀፀት ጋር የምታኝከው ቁጭት እያጠራቀመች መሆኑ መች ገባት? ቢገባት በነቃች፡፡ ነቅታ ለነገ ህይወቷ ራሷን ባዘጋጀች፤ ወይ ትዳሯን አጥብቃ በያዘች፡፡ ይሄ ደግሞ የአብዛኛዎቹ ሴት እህቶች ችግር ነው፡፡ ባክነው ኖረው ባክነው ይቀራሉ፡፡ እድሜ ሲያልፍ ‹‹እህህ!..››ን እያንጎራጎሩ የፀፀትን ሸማ አጣፍተው ይቀመጣሉ፡፡

   ‹‹ቡናውን ተቀበላት!..እየቃምክ ታንቀላፋለህ እንዴ?..›› የመስከረም ድምጽ ነው ከሀሳቤ ያባነነኝ፡፡ ጭልጥ ብዬ በሀሳብ ባህር መዋኘቴን መቼ አወቀች? ስንቱ ጋር ደርሼ፣ ስንቱን አውርጄ፣ ስንቱን ሰቅዬ፣ ስንቱን ሸፍኜ፣ ስንቱን ገልቤ፣ ስንቱን አስሼ..፣የእሷን ህይወት ዳስሼ መመለሴን ብታውቅ ታንቀላፋለህ እንዴ? ባላለችኝ፡፡ አጠገቤ የተቀመጠችው ሶስና የዘረጋችልኝን ቡና የተሞላ ሲኒ ተቀበልኳትና ቀመስ አድርጌ አስቀመጥኩት፡፡ የአንዳንዱን ቡና አጠጣጥ ስሰማ አስጠላኝ፡፡ አንዱ ፉት አባባሉ የሚያፏጭ ይመስላል፡፡ ሶስና ስታጣጥም በነጠላ ጫማ የምትራመድ ትመስላለች፡፡  ምላሷን ላንቃዋ ላይ  አጣብቃ ‹‹ጧ!›› ታደርጋለች፡፡

   ሴቶቹ፣ ወንዶቹ ሁለት ሶስት ቦታ የሺሻ እቃ ጥደው ያንቦለቡሉታል፡፡ ጫቱን አቃቃማቸው በሆዳቸው ትተው በጉንጫአቸው ማርገዝ የጀመሩ እስኪያስመስላቸው ወጥቀውታል፡፡ በዝና የሚወራለትን የመስከረምን ቤት የሀሙስ ቃሚዎችን ፕሮግራም ለማየት ነው ጫቴን አንጠልጥዬ የመጣሁት፡፡ በእርግጥም ከጠበኩት በላይ ብዙ ሰው አለ፡፡ ስለዚህ ሁሉ ሳስብ ነው ‹‹ተኛህ እንዴ ያለችኝ..›› የሁሉ አዚም ተሰብስቦ ይተኛባትና በዚህ ሁሉ ጫጫታ መሀል ጫት እየቃምኩ የምተኛው ተንቀሳቃሽ በድን አደረገችኝ? ያቋርጣትና አቋረጠችኝ፡፡  ቅድስትና አብደላ የጀመሩትን ፍቅር አቋረጠች፤ ጎረቤቶቿን አጣልታ አቆራረጠች፡፡ እሷ ራሷ ከአንዱ ጋር የጀመረችውን ፍቅር አቋረጠች፡፡ ቅድም ራሱ ጣሂር እና አሰፋ ሲያወሩ አቋረጠች፡፡ አሁን እኔን ከሀሳቤ…በቃ!..ማቃረጥና ማንቋለጥን ቋሚ ስራዋ አደረገችው?

     ቁመናውም ሆነ ነገረ ስራው በጣም የሚያስገርመኝ ቀጭኑ አሰፋ በሩ ስር ተቀምጧል፡፡ በዛ ቁመቱ ተጣጥፎ ሲቀመጥ ያሳዝናል፡፡ ሰዓሊ ነኝ ቢልም የረባ ነገር ሰርቶ /ስሎ/ ያየው የለም፡፡ ድንገት የሚስለው ሸራ ወጥሮ ቡርሽ ወድሮ ሳይሆን በጫት እንጨት..ጫት ቅጠል ላይ ነው መሰለኝ የሚስለው፡፡ጫት ይዞ፣ ጫት ወድሮ፣ ጫት ጎርሶ ነው ሁሌ የማየው፡፡ አሰፋ ስደት መቼ እንደወጣ የሚያውቅ የለም፡፡ አንዳንዴ ሳስበው እሱ ራሱ የሚያውቀው አልመሰለኝም፡፡

     አጠገቡ ካለ ሰው ጋር የጦፈ ወሬ ይዟል፡፡ ጫቱን እያነሳ በጣትና ጣቱ መሀል እያስገባ አሸት..አሸት ያደርገዋል፡፡ ወዲያው ወደ አፉ ከቶ ሌላ ያነሳል፡፡ ሂደቱ አያቋርጥም፡፡ የሚቋረጠው ቶሎ ቶሎ አፉ ላይ የሚለጉመውን ሲጋራ የያዘ እንደሆን ነው፡፡ አጠገቡ የተቀመጠው የጣሂር ወሬ የሰለቸው ይመስላል፡፡ ጣሂር እሱ ሲያወራ እንጂ ሰው ሲያወራ ማዳመጥ አይወድም፡፡ ቀለብላባ አይን እና ቀለብላባ ምላስ ለጉድ ታድሎታል፡፡ ወሬው ማቋረጫ የለውም፡፡ የአሁንለቱ በቀደምለት ታክሲ ስጠብቅ አገኘሁትና ለአፍታ ጆሮዬ ግሎ እስኪገለማ ሁለት ነጥብ፣ አራት ነጥብ..የሌለው ወሬውን አንቆረቆሮብኝ አደነዘዘኝ፡፡ ጆሮ ስትራፖ ሲይዘው አይታችሁ ታውቃላችሁ እኔ ግን የዛን ቀን አየሁ፡፡ ዳግም ሳየው እንደተበደረው ሰው መንገድ አቋርጨ እብስ…ዳግም ጆሮዬን ስትራፖ ቢይዘው በምን ይለቀኛል? ይሄ ቋንቋው የማይገባኝ የአረቦቹ ኤፍ.ኤም ሬዲዮ እንኳን እንደሱ አይታክትም፡፡ እማማ ትሙት! እላችኋለሁ ስለምን እንዳወራኝ አላውቅም፡፡ በእርግጥ እናት ኖሮኝ አይደለም እማማ ትሙት ያልኩት፡፡ መቼም ፈጣሪዬ /ፀሀፊው/ ያለ እናት ነው የፈጠረኝ ማለት ይከብደኛል፡፡ ግን እስካሁን አላውቃትም ወይም አላስተዋወቀኝም እናቴን፡፡

    ስለዚህ ጣሂር ያለውን ስላልሰማሁት ያን ሁሉ ቃላት ዝም ብሎ ለአየር ዘረገፈው፡፡ ኪሳራ ነው፡፡ ለነገሩ የእሱ ወሬ ዞሮ ዞሮ ስለየመናዊ አባቱ እና ስለኢትዮጵያዊ እናቱ ነው፡፡ 20 ጊዜ ባገኘው ሀያ ጊዜም ያወራልኛል፡፡ አረብ የጠበሱት የእሱ እናት ብቻ ናቸው እንዴ? ‹‹ባሌ ምን የሚያክል እርሻ አለን መሰለህ..›› ሲል ሁሌ ይጀምራል፡፡ አረብ ሀገራትን በስደት ያጥለቀለቀው ወንድ ሁላ መሳ ለመሳ የእርሻ መሬት ነበረው፡፡ ለኢትዮጵያ የእሱ አባት ብቻ ከየመን ሄደው ያረሱላት ይመስል ይንጦረጦራል፡፡ ጣሂር ከቁመቱ ማጠር ጋር ጉራው ሲነፃፀር ጉራው መቶ ሺህ ጊዜ ይበልጣል፡፡ ወደፊት ሾል ያለ አፍንጫው እያሸተተ ያለ ቀበሮ ያስመስለዋል፡፡ እኔ ግን ከአይኑ ማነስ እና መቁለጭለጭ ጋር አይጠመጎጥ ነው የሚመስለኝ፡፡ ያለ ቅጥ የወጠቀው ጫት ጉንጩን እባጭ አስመስሎታል፡፡ ሞልቶ እየፈሰሰ ነው ጫቱ፡፡ ሶፍት ወረቀቱን እያነሳ አፉን በጠረገ ቁጥር ንጣቱን በአረንጓዴነት ያቀልመዋል፡፡ አሁንም አሁንም አፉን ቢጠርግም ፊተኛ ጥርሱ ላይ ከተለጎደው ጫት ጋር ሲታይ የተዝረከረከ የገልቱ ቡሀቃ መስሏል፡፡ መዝረክረኩን አልኩ እንጂ አረንጓዴ ሊጥ የለም፡፡

   ‹‹ቡናው ቀዘቀዘ እኮ አትጠጣም እንዴ?..››አለችኝ መስከረም፡፡ ደህና ከምኮመኩመው ሀሳብ አላቀቀችኝ፡፡ ይቺ ልጅ ለማቋረጥ ብቻ ነው የተፈጠረችው? ትቀናለች መሰለኝ ሰው ጥሩ ነገር ሲያስብ አትወድም አስሬ ትጠራኛለች፡፡ ስሟን ቄስ ይጥራውና..ለካ ደግሞ የመን ቄስ ቢኖርም ስም አይጠራም፡፡ ፍታት የለ! ክርስቲያን ሲሞት የሚሰልምበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ክርስቲያን ሲባል መቃብር የለም፡፡ ቦታ አንሰጥም ይባልና ሬሳ ፍሪጅ ውስጥ ከቶ ለማውጣት ከላይ እታች መንጦልጦል ነው፡፡ ለዚህ ሲባል ወንደሰን ከማል፣ ማንያህሉሽ ሀቢባ እየተባሉ ስም ገለባብጦ አፈር መቅመስ ነው፡፡ ፍታት የለ ሰዓታት..ታዲያ በምን ቦታ ቄስ ስሟን ይጥራው? ቄስ ባይሆንም ሴጣን ይጥራው፡፡ አቤት ብላ ስትወጣ እስክትመለስ ብዙ አስባለሁ፡፡ ለካ ቄስ ይጥራው ሲባል ትሙት ማለት ነው? ይሄ ነገር ይለፈኝ፡፡
       
    ሀሳብ ማመንዠጌን እንደጣሂር ወሬ አራት ነጥብ ከማሳጣው ፉልስቶፕ አደረኩና ቀዝቅዞ ወዘናው የረገበ ቡናዬን መጠጣት ጀመርኩ፡፡ ቤቱ በጭስ ታፍኗል፡፡ በኩር ተበክሯል፡፡ ሺሻው ይጨሳል፤ ግማሹ ሲጋራውን ለጉሞ ያንቦለቡላል፡፡ የሽታው ነገር መላ ቅጥ የለውም፡፡ የቡና ሽታ፣ የጫት ሽታ፣ የብብት ሽታ፣ የጫማ ሽታ፣ የአፍ ሽታ፣ የእንትን ሽታ፣ የሽታዎች ሽታ፣ ይፈሳል፣ ይገሳል፡፡ እኔም እያላበኝ ስለሆነ የሰውነቴን ቢያንስ የብብቴን ሽታ አዋጥቻለሁ፡፡

                   እመለሳለሁ፡፡    




Thursday, April 19, 2012


ጥቁሯ ቦርሳዬ

 ወግ በግሩም ተ/ሀይማኖት

(ክፍል 2)



    ስሙኝማ ዝም ብላችሁ ንባቡን ብቻ ትሸከሽካላችሁ…አረ ሼም ቆንጠጥ ያድርጋችሁ.. እንተዋወቅ አይባልም እንዴ? ብቸኝነት ድንኳኑን ጥሎ እንደ ፋሺሽት ጣሊያን በቅኝ ግዛት ሊይዘኝ ሲታገል..እኔም በኢትዮጵያዊ ወኔ አልገዛም ባይነቴን ይዤ ስታገል ጎበዝ እኛም አለን በርታ ትላላችሁ ብዬ ስጠብቅ….ገብጋቦች!!..ማለቴ የሰላምታ ንፉጎች፡፡ በዛ ላይ አይዞህ ወንድማችን ትላላችሁ ስል….ኤጭ እቴ እዚህ ፌዝ ቡክ ላይ የፈሰሰ ውሃ ማቅናት አይቻልም ማን ለማን…



      ክፍል አንድ ላይ ስጨርስ ካሰፈርኩት ለማስታወስ ኳል እያረኩ ልመለስበት፡፡ ያኔ እንዲያው በደፈና ሞናሊዛዬ ነሽ እንዳለው በደፈናው ደፈንኩት፡፡ ‹‹..እስካሁን ማነህ አላላችሁኝ ማንነቴ አላስፈለጋችሁም፡፡ እኔም ኮራ ያልኩ ኢትዮጵያዊ ነኝ ፍቅርን እንደሸማ የተላበስኩ፡፡ ጥቃትን የማልወድ፣ ድህነት ቢይዘኝም በባዶ ኪሴ ኩራት የጠፈነገኝ..ከእግዚአብሄር ቀጥሎ ለውጭ ዜጋ የሚሰግድ ኩሩ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ (ይቺ ቃል የሚያጎበድድ በሚል ትታሰብልኝ ለዚህም ማስረገጫ ላጣቅስ…

  

   ማስረገጫ አንድ፡- ከወገናችን ይልቅ የውጭ ዜጋ በፍጥነት፣ በትህትና የምናስተናግድ፡፡



    ማስረገጫ ሁለት፡- የራሳችን ምሁሮች ተመራምረው ከሚነግሩን ግኝት ይልቅ ለውጭዎቹ ተራ ወሬ ጆሮ ምንሰጥ፣ ያሉትን የምናመልክ ሌላው ቀርቶ ጥይት መድኃኒት ነው ቢሉን የምንቀበል ቂቂቂቂ..ለወገናችን ክብር ያለን ኢትዮጵያዊ መሆናችንን ያሳያል አይደል?

  

    ማስረገጫ ሶስት፡- ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሄር ትዝረጋለች የሚለውን ቅዱስ ቃል ገልብጠን ለስንዴ እርዳታ እና ለአበድሩኝ ወደ ነጮቹ የዘረጋን…)



    ብቻላችሁ እንዳልኩት ኩሩ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ ማነህ ብላችሁ አልጠየቃችሁኝ እኔም እገሌ ነኝ አላልኩ፡፡ ኩራት እራት ማለት እንዲህ አይደል? ግን ለምን አትሞክሩትም? ኩራት እራት በሉና ጦማችሁን ሞክሩት እስኪ…ጨጓራችሁ እኩለ ሌሊት ላይ እንደ እንጨት ሰራተኛ መፈቅፈቂያውን ይዞ ሲፈቀፍቃችሁ..ሁሉም ዜሮ ዜሮ ብሎ ራሱ ዜሮ እንደሆነው ዘፋኝ ዜሮ ሆኖ ታገኙታላችሁ፡፡ አውቃችኋል አይደል? ይህ ታሪክ የጸሀፊው አይደለም፡፡ ፀሀፊው የፈጠረኝ የእኔ ነው፡፡ ምናብ ወለድ ፍጡር ነኝ፡፡ የጸሀፊው ፍጡር ታሪክ ነው፡፡



     አሁን አንተ ማነህ ካላችሁ ለስሜ አልጨነቅም፡፡ ከበደም በሉኝ አበበ፣ ጀማልም በሉኝ እንድሪስ…መጠሪያው አያጨቃጭቀንም፡፡ ሰው ሆኖ መገኘት ነው ዋናው፡፡ ለእኔ ስሜ ምግባሬ ነው፡፡ አልዳሰስ አልከሰስ…ሳልፈጠር በፍጡር የተፈጠርኩ፡፡ ያለነበርኩ በእሱ ዘንድ የኖርኩ፡፡ ለእናንተ እንግዳ ነኝ፡፡ ለፀሀፊው እስኪፈጥረኝ አርግዞ  እስኪወልደኝ ምን ያህል እንዳማጠኝ እሱኑ ጠይቁት፡፡ ያለ ግንኙነት ተፀንሼ በወንድ ምጥ የተወለድኩ ነኝ፡፡ ደግመዋለሁ ለስሜ አልጨነቅም ማንነቴን ባልነግራችሁም ምግባሬ ይገልጸዋል እውነቱን ይዞ መሄድ ነው ፍላጎቴ፡፡ ብዙ መታዘብ አዘውትራለሁ.. ታዲያ አፈር ስሆን ጋሽ ኦብዘርበር እንዳትሉኝ፡፡ አስቡት እስኪ በእንግሊዘኛ ሳቅ ከየት አምጥቼ እስቃለሁ?…በአማርኛ ከሆነ በፈለጋቸሁት ጥሩኝ ግን ማን ብባል ነው ደስ የሚላችሁ? ስም ነገሩኝ እስኪ…  በዚህ ዘመን ለበዛ ትርጉም አልባ ስም ምን ችግር አለ አንዱን ለጥፉልኝ፡፡ ታዲያ አደራ ሊሊ ኪኪ ባቢ ቦቢ..እንዳትሉኝ፡፡ እነዚህ ስሞች ይደብሩኛል፡፡ ደስ የሚል ስም ብታወጡልኝ ችግር የለም አትከፍሉበት፤ አይፈልጣችሁ አይቆርጣችሁ ደስ ያላችሁን አንሱ እና…እህ!..ትርጉም ያለው ቢሆን ግን ደስ ይለኛል፡፡

    

   እንድታስቡ  የምፈልገው መኖሪያ አድራሻዬ ጥቁሯ ቦርሳ ውስጥ ወረቀቶች መሀል ተኝቼ ነው የምገኘው፡፡ ስትፈልጉ እዛ ኑ ታገኙኛላችሁ….ወይኔ ጉዴ!.... የት ላይ ነበር ያቆመኩት? እንኳን የሴት የወንድ ጓደኛ መምረጥ፣ ማግኘት እንደሚከብድ ነግሬያችሁ የለ? ወንድ ጓደኛ ለመያዝ ሲታሰብ እንደ ውሻ እጅ እጅ፣እንደ ሌባ ኪስ ኪስ የሚያይ መሆኑ ያሳፍራል፡፡ ትርፍራፊ የማበላው ውሻ ሳይሆን የእኔ የምለው ጓደኛ ነበር ፍላጎቴ እና ተውኩት፡፡ ‹‹ብቸኝነቴን ነው እኔ ማስታውሰው…›› የሚለውን ደጋግሜ ባዜምም አዲስ ስልት እና ስትራቴጂ ቀይሼ ብቸኝነቱን ልዋጋ ጦር መምዘዝ አላስፈለገኝም፡፡ የህይወት ጦሯም፣ ሞተሯም ሴቶች ናቸው እና የግራ ጎኔን ልመነትፍ፣ ለስላሳ አጣጪዬን /ያው ከውሀ ለስላሳ ይቀንሳል ብያችኋለሁ አስታውሱ../ የሄዋንን የልጅ ልጅ እጣ ፋንታዬም ትሁን እጣ ጦሴ ለማግኘት ፍለጋ በድጋሚ ጀመርኩ፡፡ የበዚያ ሰሞኑ ሀሙስ ሰርግ ነበረ እና ትከሻዬን ሰብቄ ልጨፍርም በአጋጣሚው ጥሬ ልጭርም ሄድኩላችሁ፡፡ ያው መቼም ጠርተውናል ያበሉናል ብዬ ነው፡፡



   ከርዕስ ውጭ ትንሽ እናውራ…ሰነዓ ያለ ሀበሻ ሞኝ ነው ሰርግ ይደግሳል፡፡ ቤተሰቡ የችግር አረንቋ እንደካባ ከላዩ ተመርጎበት፤ ማጣት እንደኩፍኝ ሳይሆን እንደፈንጣጣ አዥጎርጉሮት፣ ርሀብ ጨጓራው ላይ ሲጨፍርበት እሱ እዚሀ አፈሰማይ አብልቶ ያስጨፍራል፡፡ ይሄ የብዙዎች ገጠመኝ እና እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ አንዱ ወዳጄ /መቼስ ጠላቴ አይባል ወገኔ ነው/ ኢትዮጵያ የማውቀው ምስኪን ቤተሰብ ያለው እዚህ የመን ‹‹…የእገሌ ሰርግን የሚያክል የለም፡፡ ስድስት ማርቼዲስ ተከራይቶ..ከነመልሱ አዳራሽ ተከራይቶ..የነበረው ግብዣ..ህዝቡን ያበላው….›› እየተባለ የሚወራለት ሰሞን ነው የመን የገባሁት፡፡ ልጁ የጓደኛዬ ወንድም ነው፡፡  በዛው ወቅት ግን ከደ/ዘይት ከተማ ወጣ ብላ የምትገኝ እናታቸው በችግር መሟቀቋን ስለማውቅ ለእሱ ጥላቻ እንጂ አድናቆት አልቸርኩትም፡፡ ለጉራ ሲባል በችግር የተያዘን ቤተሰብ መርሳት የማንነት ማጣት ነው፡፡  የመን በልቶ ማደር በቸገረበት ሁኔታ እየኖሩ ሰርግ ምን ደስ ሊል? እስከመቼ የቦይ ውሀ ሆነን እንጓዛለን? ሰው ስላደረገ ብቻ እናደርጋለን? ወደ ርዕሳችን እንመለስ



      ሰዎች ልብ በሉ ከርዕስ ውጭ.. የተፃፈው እኔን አይመለከትም የጸሀፊው ሀሳብ ነው፡፡ እኔ አቅሜ ውስን፣ የምናገራት ምጥን ነች፡፡ ሰርጉ አዳራሽ ውስጥ ነው፡፡ አንዷ አይኔን ብቻ ሳይሆን እግሬን ጭምር ሳበችው እና እብስ….እየጨፈረች ነው፡፡ ሙዚቃው ሐገርኛ ይሁን እንጂ ውዝዋዜው የውጭኛ ነበር፡፡ ከመሞከሬ በፊት የእሷን እንቅስቃሴ ማጥናት ግድ አለኝ እና ማየት ጀመርኩ፡፡ እናንተዬ የአንዳንዱ ዳንስ ስታዩት የሚገርም ነው፡፡ በቃ!.. ቡኮ የሚለውስ የሚመስል አለ፡፡ ሸማ እየሰራ የሚመስል እንቅስቃሴ የሚያሳይ አለ፡፡ ኧረ!..ልብ ካላችሁት ሾፌርም፣ ቀያሽ መሀንዲስም፣ አትክልተኛም የሚመስል አለ፡፡ እናላችሁ የእኔዋ በአይኔ የመረጥኳት ተጋጣሚዋን የምታጠቃ ቦክሰኛ ትመስላለች፡፡ ወዳጄ ትንሽ ችግር ያለ ቀን ጥርሴን በኪሴ የምታሲዘኝ ልምድ ያላት ቦክሰኛ መስላ ታየችኝ ‹‹ አልመጣም ቀረሁኝ ሸጌ…›› ብዬ ቀኝ ኋላ ዙር ነዋ!.. የሚገርመው ስዞር እንዳጫፍራት አንዷ ጋበዘችኝ፡፡ ቅጥነቷ እና ርዝመቷ ተደማምረው ሲያሳጧት ውሀ የነካው ፓስታ አስመስለዋታል፡፡ ትምዘገዘገዋለች፣ ትርገፈገፈዋለች.. አቤት!!..ጭፈራ ይሄ ነገረኛ ቴሌቪዥን ከሚያመጣቸው ተወዛዋዦች ትበልጣልች ብል ‹..ወይ ፎንቃ በአንዴው ቲፎዞ ሆንካት…› እባላልሁ ብዬ ስለፈራሁ ነው ያላልኩት፡፡

 

      ህዝቡ በደስታ ሰክሯል፡፡ ወጭው የሙሽሮች ጭፈራው የእኛ ሆኖ ብናደምቅላቸው ምን አለበት? ውይ የኔ ነገር ለካ ትራንስፖርት አውጥቻለሁ፡፡ ምናለ በነካ እጃቸው ቢከፍሉልን ኖሮ..አያዞራቸው፣ አያሳብዳቸው፡፡ በመቶ ዶላር ሰርተው በ3 ሺህ ዶላር መደገስ እብደት ስለሆነ ቀድመው ነው ያበዱት፡፡ እዳውን ከፍለው እስኪጨርሱ ልጅ ተወልዶ በእከከኝ ልከክልህ ኑሮ ለትምህርት ይደርሳል፡፡ አንዳንዴ ዘፈኖችን ከማስማት ይልቅ ማዳመጥ ጥሩ ነው፡፡ ‹‹አቅምን አውቆ መኖር ጥሩ ነው ታላቅ ችሎታ ነው..›› ብሎ ነበር ድምጻዊ ጥላሁን ነፍሱን ይማርና፡፡



   የምንጨፍርበት ዘፈን አለቀ እና የደረጄ ደገፋ‹‹አበራሁኝ ሻማ ሞቅ አለ ጎጆዬ በራሴ ተማመንኩ ኮራሁ በምርጫዬ..›› የሚለውን ከፈቱት፡፡ መቼም ነገር ማንሸዋረር ለምዶብናል አይደል አንሸዋረርኩ እና ኮራሁ በምርጫዬ የምትለውን..‹‹ኮራሁ በሻማዬ..›› አልኩላችኋ፡፡ ሻማዬ ናት ከጨለማ ያወጣችኝ፡፡ የመን መብራት እንደ መንግስት ሰማያት ተስፋ ነው፡፡ በቀን ሁለት ሰዓት ሊበራ አለያም ብቅ ላይልም ይችላል፡፡ ሁሌ የመብራት መስመሩን ተቃዋሚዎቹ መቱት ይባላል፡፡ አመት ከአራት ወር ‹‹ንፋስ ነው ዘመዴ..›› እንዳለው አረጋኸኝ እኛም ሻማ ነው ዘመዴ ብለናል፡፡ ከውጭ ሀገር እንግዳ ሲመጣ እና የምርጫው ሰሞን ግን ለሳምንት ለሳምንትም  ቢሆን አብርተውልናል እና እናመሰግናለን፡፡ ሌላ ቀን ተመታ እየተባለ እንግዳ ሲመጣ እና ምርጫ ሰሞን የማይመታው እንግዳ አክባሪ ሆነው አይመስላችሁም? ምስጢር አለው ካላችሁ ፈልጋችሁ ድረሱበት፡፡



    ከተማው በጨለማ ከመዋጡ ጋር በየቦታው ጄኔሬተሩ ሲንፈቀፈቅ ግዙፍ ፋብሪካ ውስጥ የምንኖር ሁሉ ይመስለኛል፡፡ በቃ!..የማርያም መንገድ ካገኘሁ መገስገስ ነው፡፡ ‹‹ገስግስና በለው..ገስግስና በለው..ጠላትን እንደ በሬ.. ›› የሚለው ዜማ ትዝ አለኝ፡፡ ወደ ታሪኩ ስመለስ አዲስ ሞቅ ደመቅ ያለ ባህላዊ ዜማ ተከፈተ፡፡ ጋባዥ ሳልሻ፣ አጫፋሪ ሳልፈልግ ንሽጥ አድርጎኝ ድረግም፡፡ እናቴ የማይወጡት ዘቅጥ ውስጥ ገባሁላችኋ፡፡ ቡርቅ..ቡርቅ..ትከሻዬን ሰበቅ ሳደርግ አምሬያት ይሁን ማርኬያት ወደ እኔ አንዲቷ ቆንጆ መጣች፡፡ ‹‹እሰይ ደስ ይበለን እሰይ ደስ ይበለን አውዳመት መጣልን..›› የሚለውን ዜማ ገልበጥ አደረኩላችሁ እና ‹‹እሰይ ደስ ይበለኝ..እሰይ ደስ ይበለኝ አጣማጅ መጣልኝ..›› አልኩ፡፡ ምነው እኔ ላይ ሲሆን ተኮሳተራችሁ ሁሉም የየሰዉን እየገለበጠ ነው የሚዘፍነው፡፡ እንኳን የእኛ የአረቦቹ እና የፈረንጆቹ ሁሉ ተገልብጦ አልቋል እኮ!!..፡፡



    ጭፈራውን ሳስነካው ላቡም አባይ ስለሚገደብ ከወዲሁ ፈርቶ በእኔ አናት ላይ መንገድ የቀየሰ እስኪመስል አጥለቀለቀኝ፡፡ በዚህች ሰዓት አንዱ ከኋላዬ ነካ..ነካ.. ሲያደርገኝ በጭፈራዬ የተማረከ ሰው እንዳጫፍረው አለያም ላቤን እንድጠርግ ሶፍት ሊሰጠኝ እንጂ እንደ አዝማሪ ቤት ግርባሬ ላይ ሊለጥፍልኝ አይሆንም ብዬ ዞርኩላችሁ፡፡ ከዛ ምን እንደተፈጠረ አላውቀውም፡፡ ቤት የተቃጠለ እስኪመስለኝ የቀለም ሁሉ አይነት ቦግ ብሎብኝ ሲጠፋ ተዝለፍልፌ ወደኩ፡፡ ምን ባጣፈሁ ነው የእናቴን ገበር ምጣድ በሚያክል እጁ በጥፊ የከደነብኝ፡፡ አሁን ሳስበው ያኔ ይቺ ድንቡሎ ፊቴ እሱ እጅ ላይ ስታርፍ የቡሄ ሙልሙል መስላ ይሆን? ምነው ያኔ ፎቶ ባነሱኝ ነበር፡፡ እኔ ወድቄ እሱ ለያዥ ገናዥ አስቸገረ…



             አንዴ ታጥቤ፣ ደሜን ጠራርጌ እመለሳለሁ ጠብቁኝ፡፡          





          

Monday, April 16, 2012


                         ግሩም ተ/ሀይማኖት
       እጅግ የተከበሩ ሜተር አርቲስት የአለም ሎሬት አፍወርቅ ተክሌ..
                                         
      እረፍተ ዜናቸውን /የሞታቸውን ዜና/ ያረዳኝ ፌስቡክ ላይ የተለጠፈ ዘገባ ነው፡፡ አዘንኩ፡፡ በእውነት አዘንኩ ብቻ ሳይሆን አንጋፋዎቹ መከታተላቸው አስደነገጠኝ፡፡ በሰዓቱም ስለተደናገጥኩ የለጣፊውን ማንነት ልብ ስላላልኩ እገሌ ብዬ ማመስገን አልቻልኩም፡፡ ከዛ በኋላ በርካቶች ለጥፈውታል፡፡ ሁሉንም ላመሰግን ወደድኩ፡፡ ከምንም በላይ ያስደነገጠኝ የጥበብ ሰዎቻችን እና የኩዳዴ /የፋሲካ/ ጾም ቁርኝት ነው፡፡ ከሁሉም የከፋው የዘንድሮው ሁለት ወር ጸም ሶስት አንጋፋዎችን አሳጣን፡፡ ጾሙ ሲገባ በአጻጻፍ ስልቱ ከልጅነቴ ጅምሮ የምወደው ጋሽ ስብሀትን አጣን፡፡ እኩለ ፆሙ አካባቢ በትርጉም ስራቸው በርካታ የስለላ መጻህፍትን ያስነበቡን፣ በርካታ መጽሀፍትን የተረጎሙት ደራሲ፣ ጋዜጠኛ እና ተርጓሚ ማሞ ውድነህን አጣን፡፡ የሁሉም ሲታሰብ ቤተሰብ የማጣት ያህል ነው የተሰማኝ፡፡
  
    ጋሽ ማሞ ውድነህን ከሁሉ በላይ የማውቃቸው ለሰርካለም አሳታሚ ድርጅት /ቢሮአችን/ በነበራቸው ቅርበት ነው፡፡ ሞታቸውን ስሰማ ቶሎ የታወሰኝ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና ሰርክዓለም ፋሲል ናቸው፡፡ በተለይ እስክንድር ነጋ ይወዳቸው ነበር፡፡ ያከብራቸዋልም፡፡ በእስር ሳለ ስለሆነ ስላልቀበራቸው ምን ተሰምቶት ይሆን? የተሰማውን አንድ ቀን ጽፎ እንደሚያስነብበን አምናለሁ፡፡ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በገዢው ፓርቲ ‹‹አሸባሪ..›› ተብሎ በእስር ላይ ነው፡፡ ቢሆንም ፔን ኢንተርናሽናል በምርጥ ጋዜጠኝነት ተሸላሚ አድርጎ ስለመረጠው ደስታዬ ወደር የለውም፡፡ ሲያንሰው ነው እንጂ የሚበዛበት አይደለም፡፡ አንድ ቀን እውነት ሲያሸንፍ፣ ስልጣን ኤስፓየርድ ሲያደርግ፣ ነገር ሲገለበጥ እስክንድርም ነፃ ይሆንና....እስከዛው ግን በቀጣይነት ስለ እስክንድር ነጋ በማሰፍረው ፅሁፍ እመለሳለሁ፡፡ አሁን ወደ ጅምሬ ልመለስበት፡፡

   የእረፍተ ዜናቸው ያስደነገጠኝ እጅግ የተከበሩ ሜተር አርቲስት የአለም ሎሬት አፍወርቅ ተክሌ አንድ ጊዜ ‹‹ለውዱ ግሩም ተ/ሀይማኖት ከመልካም ምኞት ጋርና ከወንድምነት ጋር..›› ብለው በእጅ ፅሁፋቸው ፅፈው ፊርማቸውን ያኖሩበትን ማስታወሻ ሰጥተውኝ ነበር፡፡ ይህ ማስታወሻ ከላይ ያስቀመጥኩት ፎቶዎች ያሉበት ነው፡፡  የእሳቸው፣ የቤታቸው እና አፍሪካ አዳራሽ ውስጥ ያኖሩት ድንቅ ስዕላቸው ያለበት ሆኖ ከውስጡ በፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት የተፃፈ የህይወት ታሪካቸው ያለበት ነው፡፡ ሰዓሊ ሆኜ አይደለም የተገናኘነው፡፡ ስለ ስዕል ምንም አይነት ግንዛቤ የለኝም፡፡ ቢያንስ ጥሩ ተመልካች አይደለሁም፡፡ በልጅነቴ በስዕል ፕሮፌሽናል ደደብ ከመሆኔ የተነሳ ጂኦግራፊና ባዮሎጂ በካርቦን ነበር የምገለብጠው፡፡ ነፃ ፕሬስ ውስጥ ከገባሁ በኋላ ግርማ የሚባል ካርቱኒስት የሚስላቸውን ካርቱኖች እያየሁ ትንሽ ሞካክሬያለሁ፡፡ ታዲያ በደፍተር ሉክ ላይ ከመሳል አልፌም አላውቅም፡፡

   ኢትዮጵያ ነፃ ፕሬስ ውስጥ በነበርኩበት ጊዜ አንድ ጊዜ ለምኒልክ መጽሄት፣ ሌላ ጊዜ ለምኒልክ ጋዜጣ ቃለ-ምልልስ ሳደርጋቸው ነው የተቀራረብነው፡፡ የጋዜጣውን ቃለ-ምልልስ በኋላ አቀርበዋለሁ፡፡

   በአንድ ወቅት ቀንዲል ቤተ-ተውኔት ውስጥ በጥላሁን የህይወት ታሪክ ዙሪያ አንድ ዝግጅት ይደረጋል፡፡ ሳንዲያጎ ፕሮዳክሽን ወይም ሙዚቃ ቤት ነው ያዘጋጀው፡፡ ድንገት ጊዜው ከመርዘሙ ጋር ሳንዲያጎ ሙዚቃ ቤት ይባል ፕሮዳክሽን ከተሳሳትኩ ይቅርታ፡፡ በወዳጄ ጋዜጠኛ ወርቅአፈራሁ አሰፋ ጠሪነት ቦታው ላይ ተገኘሁ፡፡ ጋሽ አያልነህ ሙላትን ላናግረው ቢሮ ስገባ ሎሬት አፈወርቅ ተክሌን አገኘኋቸው፡፡ አጋጣሚው የገረመኝ ስለእሳቸው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ መረጃ ነበረው እና ቃለ-ምልልስ ባደርጋቸው ጥሩ እንደሚሆን ጠቁሞኝ ነበር፡፡ በቀጥታ ራሴን አስተዋውቄ የአለም ሎሬትነት ማዕረግ ሊሰጣቸው እንደሆነ መረጃ እንዳለኝ ነግሬ ቃለ-ምልልስ እንድናደርግ ጠየኳቸው፡፡ ቀናት አመቻችተው ሲመቻቸው እንደሚደውሉልኝ ተነጋግረን ስልክ ቁጥሬን ሰጠኋቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ካሉኝ የማስታውሰው ‹‹ሞባይል ስልክ የሚባል ነገር መያዝ አልወድም፡፡ ስራ ያስፈታል፡፡ ስቱዲዮ ውስጥ እየሰራሁ ቢደወል እንዴት የምናደድ ይመስልሀል?›› አባባላቸው እውነት መሆኑን ጋሽ አያልነህ ሙላት ጠንቅቆ አስረዳኝ፡፡

     እደውልልሀለሁ ብለው ስልክ ቁጥሬን የመውሰዳቸውን ነገር ግን ማንም ቢሯችን ሰዎች አልተዋጠላቸውም፡፡ ‹‹..እሳቸው እኮ የፈለገ መገናኛ ብዙሀን በደብዳቤ ጠይቋቸው እንኳን እሺ አይሉም...›› የሚለው ዋነኛ መነጋገሪያ ሆነ፡፡ ደካማ ጎኔ ጠንከር ብሎ ወይም ተጠራጣሪው ጎኔ አመዝኖ ሌላ አርቲስት ቃለ-ምልልስ አደረኩኝ፡፡ ከ13 ቀን በኋላ ግን በቢሮው ስልክ ሲደውሉ እኔ ስላልነበርኩ እስክንድር ይመስለኛል ወይም ሰርክዓለም መልዕክት ተቀበሏቸው፡፡ በማግስቱ አራት ሰዓት ቀጠሮ እንደተያዘልኝ ነው መልዕክቱ፡፡ በሰዓቴ ጦር ኃይሎች አካባቢ ያለው ቪላ አልፋ ቤታቸው ደረስኩ፡፡ ሰዓት ላይ የማያዛንፍ አቋም እንዳላቸው ሰምቼ ነበር እና በሰዓቱ ተጠንቅቄ ደረስኩ፡፡ ይህን ቤታቸውን ደርግ ወስዶባቸው እንደነበር ሲመለስላቸው ለማደስ ብቻ በሚሊዬን የሚቆጠር ገንዘብ እንዳወጡበት ራሳቸው ነገሩኝ፡፡ በውበቱ ተማርኬ መፍዘዜን አውቀው ይሆን የነገሩኝ? እያንዳንዱ ነገር ጥበብ ወለድ ረቂቅ ስራ ነው፡፡ ስቱዲዮ ውስጥ ስገባ ግን ረጅም አመት ወደ ኋላ የሚመልስ እና የልጅነት ጊዜዬን የሚያስታውስ ምስል አየሁ፡፡ የአባታቸው ነው፡፡

    እዚህ ጋር አምሮ ተኩሎ ይሳል እንጂ በህጻንነቴ የማውቃቸው ሰው ምስል ጋር ተመሳሰለብኝ፡፡ ራስ መኮንን ድልድይ አካባቢ ከፍ ብሎ ያለ ካብ ጊቢ ውስጥ የነበሩ ‹‹የአፈወርቅ አባት›› ስንላቸው የሚያባርሩን ሰው ለመሆናቸው አልተጠራጠርኩም፡፡ ግን የወጣትነትና የሽምግልና፣ የመክሳትና የመወፈር ለውጥ ጎልቶ ይታያል፡፡ የአባት ጡረተኞችን አይነት አለባበስ ከነ ኒሻናቸው እንደሚለብሱ እንኳን ያኔ አሁንም በአይነ ህሊናዬ ይታዩኛል፡፡ አርባ ደረጃ..ራስ መኮንን ድልድይ አካባቢ፣ ቅ/ማርያም፣ አራት ኪሎም በተወሰነ ቦታ ያደጋችሁ እኝህን ሰው ታውቋቸው ይሆናል፡፡

   ከሰዓሊ አፈወርቅ ተክሌ ጋር ሻይ ጠጥተን ከስቱዲዮ ጀምረው ቤታቸውን እያዞሩ ሲያሳዩኝ በመሀል ብልጭ እያለ ደስታዬን ሰልቦኝ የሚሄደው ‹‹ለምንድን ነው የአፈወርቅ አባት..›› ሲባሉ ያባርሩን የነበረው? ይሄን የመሰለ የሚያኮራ ልጅ እያላቸው? ችግሩ ምንድን ነው? የሚል ሀሳብ ነበር፡፡ የአንድ ሰው ጊቢ፣ የአንድ ሰው ስቱዲዮ የምጎበኝ አልመሰለኝም፡፡ ብሔራዊ ሙዚየም ነው የሆነብኝ፡፡ ይሄ እንደ ፕላዝማ ስክሪን የሰፋ ፊቴ ስሜቴን ያሳብቃል መሰለኝ፣ አለያም ጥሩ አንባቢ ናቸው ማለት ነው፡፡ ይሄ የመጀመሪያዬ ቤት ስለሆነ ነው ቪላ አልፋ ያልኩት እንጂ መገናኛ እና አዋሳም ከዚህ የማይተናነሱ ቤቶች አሉኝ ሲሉ በግርምቴ ላይ ግርምት እንድጨምር አድርገው ነገሩኝ፡፡ የሽልማታቸው ብዛት ዛሬ ላይ ሆኜ ማስታወስ የሚከብድ ነው፡፡ የልብሶቹ ለብቻ ዋንጫዎቹ፣ ኒሻኖቹ.. ሁሉም ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል፡፡ እንደ ቢሮ የሚጠቀሙበት ቦታ ላይ በትልቅ ወረቀት ላይ ያገኙትን ሽልማቶች፣ መቼ እንደ ተሸለሙ፣ የሸላሚው ድርጅት ወይም ሀገር ዝርዝር ተመዝግቦ ተቀምጧል፡፡ አስታውሳለሁ ሰባ ሁለት አካባቢ ነበር፡፡

     ስላየሁትም፣ ስለሰማሁትም፣ ስናወራ ስለታዘብኩትም ለመጠየቅ መቅረፀ ድምፄን አስተካክዬ ተቀመጥን፡፡ በመጀመሪያ የጠየኳቸው ጥያቄ ከስማቸው በፊት ስለሚገቡት የማዕረግ መጠሪያዎች እና ሙሉው ካልተጠራ ስለሚሉበት ምክንያት ነበር፡፡ ይህን ቃለ-ምልልስ ሐምሌ 6 እና 13 1993 ዓ.ም ለንባብ በበቃው ‹‹ምኒልክ›› ጋዜጣ ላይ ነበር ያሰፈርኩት፡፡ በአጋጣሚ ካስመጣኋቸው መረጃዎቼ ጋር መጥቶ እጄ ላይ ስላለ  የሰጡኝን ምላሽ ላስነብባችሁ፡፡

     ‹‹አንዴ ለአንባቢህ ሙሉ ስሜን ከነማዕረጌ መስጠት አለብህ ከዛ በኋላ ግን እየደጋገምክ ያንን ማለቱ የሞኝ ለቅሶ ነው፡፡›› አሉኝ በዚህ ብስማማም አንዴ ሲናገሩ ‹‹ስትጠሩ አንጠልጥላችሁ በግማሽ አትጥሩኝ ከጠራችሁ ሙሉውን ጥሩ ካልሆነ ግን በስሜ ብቻ ጥሩኝ..›› ሲሉ ሰምቻለሁ ስለዚህ አሁን ካሉኝ ጋር አይቃረንም? ወይስ ይህ ነገር ተደጋግሞ አሰልችቶት ነው ይህን ያሉት? አልኳቸው፡፡ አይኔ ግን ትርጉማቸው ያልገባኝ አብስትራክት ስዕሎች ላይ ይንከራተታል፡፡ ‹‹ምን መሰለህ..›› ሲሉ ጀመሩ፡፡

    ‹‹ምን መሰለህ በፅሁፍ ለሚደረግ ነገር ሲጀመር ሙሉ አርዕስቱ መጠራት አለበት፡፡ ማለት እጅግ የተከበሩ ሜተር አርቲስት የአለም ሎሬየት አፈወርቅ ተክሌ የሚለው መስፈር አለበት፡፡ እነዚህ አርዕስቶች...አንተ አጋጣሚ እዚሁ ክፍል ውስጥ ነው ያለኸው አንኳር..አንኳር የሆኑ ዲፕሎማዎችና የምስክር ወረቀቶች አሉ፡፡ ይህንን አይተህ ሁሉንም ነገር መረዳት ትችላለህ፡፡እነዚህ ነገሮች ሲሰጡ ሴኔት ተቀምጦ፣ ኮሚቴ ተቀምጦ ወይም የአካዳሚ አባላት ተቀምጠው ይህ ሰው እስካሁን ድረስ በሰራው ስራ ይህ ማዕረግ ይገባዋል ብለው ነው የሚሰጠው፡፡ በስራህ በድካምህ የመጡ ናቸው፡፡›› ሲሉ ውስጤ ተፀንሶ የሚላወስ ብልጭ ያለ ጥያቄ ነበርና የእነዚህ ነገሮች /ሽማቶች/ ዋጋቸው ወይም ጥቅማቸው ምን ያህል ነው? አልኩኝ፡፡

     ሲመልሱልኝ ‹‹..እነዚህ ነገሮች ከዩንቨርስቲ ዲግሪ በላይ ናቸው፡፡ ሲሰጡህ እኛ ለዚህ በቂ ነህ ብለን እናምናለን ትቀበላለህ ወይ ብለው ይጠይቁሀል፡፡ እቀበላለሁ ካልክ ያንን ስም ማክበር ማስከበር ግዴታህ ነው፡፡ እኔ ይሄ ይጠራ፣ ይሄ ይጠቀስ የምለው ለዛ ነው፡፡ ካልሆነ አፈወርቅ ተክሌ በቂዬ ነው፡፡ ለማናም አርቲስት ለማንም የፈጠራ ሰው ስሙ በቂው ነው፡፡ እነፒካሶ እርዕስት ሳይኖራቸው ቀርቶ አይደለም፡፡ ግን በጽሁፍ ከሆነ ያ-ያገኙትን እርዕስት መፃፍ አለበት፡፡ በመናገር ከሆነ ግን ፒካሶ ነው የምትለው፣ ዳቪንቺ ነው የምትለው፣ እከሌ ነው የምትለው፡፡ እኔንም አፈወርቅ ልትለኝ ትችላለህ፡፡

     ግን በሀገራችን የሆነው ምንድን ነው፡፡ መንግስት የሰጠህ አርዕስት ካልሆነ በስተቀር የተከበሩ፣ ክቡር መባል አትችልም የሚል መንፈስ ጭቅላታቸው ውስጥ ገብቷል፡፡ እንጂ ለእኔ አፈወርቅ የሚያሰኘኝ ስራዬ ነው፡፡ እሱ ይበቃል፡፡ ግን ለምንድን ነው ይሄን የሚቃረኑት?..›› አሉኝ፡፡ በዚህ አይደለም ያበቃነው፡፡ ጠቅለል አድርጌ እመለስበታለሁ፡፡
                        ቸር እንሰንብት፡፡      


Thursday, April 12, 2012

ጥቁሯ ቦርሳዬ

ወግ በግሩም ተ/ሀይማኖት

    ስደት ስደት ነው፡፡ ስሙን ብናሰማምረው፣ ብንኩለው፣ ብንኳኩለው ያው ስደት ነው፡፡ እዚህማ ያለነው በሁለት እንከፈላለን ይላሉ አንዱን ከፍ አንዱን ዝቅ ሊያደርጉት፡፡ ገፈቱን እኩል እየተጎነጩት በባህር የገባ እና በአየር የገባ ብለው…ቂ…ቂ…ቂ…ቂ… አይ ወዳጄ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እግዚአብሄር ካንተ ጋር ሆኖ ከእስር ያውጣህ እንጂ ይቺ ቂ..ቂ.. የምትል ሳቅ በተጻፈች ቁጥር ትውስ ትለኛለህ፡፡ ትወዳት ነበር፡፡

    በዛ ያሉት አዳሜዎች፣ እና የአዳሜ እህቶች በአየር ነው የገቡት፡፡ ታዲያ አውሮፕላን ላይ ተሰቅላ የተጓዘችው በጉብኝት ቪዛ ይሁን እንጂ ቱሪስት ሆና አይደለም፡፡ ቦዶ ኪስ ቱሪስት ቢኮንስ የኔብጤ ይመስል የሰው እጅ እጅ ከማየት ይዘላል ብላችሁ ነው? ለነገሩ ቱሪስት አይሁኑ እንጂ የሰው እጅ ላለማየት መስራትን አማራጭ አድርገው የሚሄዱ ስለሆኑ ያኮሩኛል፡፡ ግን በኮንትራት ስራ አረብ ቤት ልትጠመድ ነው እያንዳንዷ አካሄዷ፡፡ የእኔው ለየት የሚለው ግን ባህር አቋርጨ..በየብስ በላብ ጨቅይቶ ብስብስ እስኪል ካልሲዬ…እግሬ እስኪላላጥ ተጉዤ ነው የመን ያለሁት፣ የገባሁት፡፡

   እይ!!!...ብቻ ተዉኝ እስኪ…ይሄን ለማንሳት አይደለም አነሳሴ፡፡ በስደቱ አለም ብቸኝነት ድቁስ ድቁስቁስ ያደረገኝ የዋዛ አይለም፡፡ እናቴ አሽቶ!..አሽቶ!! አድቅቆኛል፤ አልሞኛል፡፡ አንፍሶ፣ አንገዋሎ አንቀቀጥቅጦ…አበጥሮኛል፡፡ እንደ ወንደላጤ ካልሲ አዝረክርኮ..አልጋ ስር ባይሆንም እስር ቤት ወርውሮኛል፡፡ ስደት..የጨው ጆንያ አስመስሎ፣ አመድ ነዝቶ፣ በችግር ጠቅልሎ ጢባ ጢቢ…ጢባ ጢቢ ተጫውቶብኝ..ወዜን መጦ በጀሪካን ባዝሊን የማይመለስ ግርጣትና ንጣት አልብሶኛል፡፡ ብቻ ምን አለፋችሁ ፌድ ያደረገ ጅንስ መስዬ እንገላወዳለሁ በብቸኝነት ተተብትቤ፡፡

       ወዳጄ አሞህ ነው አጣሞህ? ከተማ እያለህ..በርካታ ኢትዮጵያዊያን እንደጉንዳን የሚርመሰመሱባት ሰነዓ ቁጭ ብለህ ብቸኝነት የሚያሰኝህ? ማለትዎ የማይቀር ቢሆንም ልክ መሆኖትን እኔም አሰምርበታለሁ፡፡ እኔ ግን ብቸኛ መሆንን መርጨ ብቻ ሳይሆን ብቸኛ ሆኛለሁ፡፡ ብቸኝነትን እኔ ብቻ ፈልጌው ሳይሆን እሱ ፈልጎኝ እንደሆነስ የሙጥኝ ያለኝ? ይጣራልኝ ይመርመርልኝ፡፡

   ታዲያ ይህን ግርጣትና ንጣት ያመጣ ብቸኝነት ለመቅረፍ ስትራቴጂያዊ ጥናት አደረኩልዎት እና ‹‹ጥንድ..ጥንድ ሆነው ሲሄዱ ባይ ለካስ..›› የሚለውን ለማቀንቀን አሰብኩ፡፡ ባዝሊን፣ ቅባት ይዛ መጥታ ልታወዛኝ አስቤ አይደለም፡፡ እንዲያውም የቀረውን ወዝ አንጠፍጥፋ የምትወስድ መሆኗን መቼ አጥቼ? ሰው ትሁን ብቻ!...በቃ የሚፈለገው ሰው መሆን ነው፡፡ ግን ዝም ብሎ ሰው መሆን ብቻ መስፈርት አይደለም፡፡ ፤ሌላ መስፈርት ያስፈልገዋል፡፡  ማሟላት ያለባት አልኩ እና መሰፈርት ብጤ በውስጤ ከተብኩ፡፡ አሁን ቀሪው ነገር ቅኝት የተባለ ፕሮግራም ዘርግቶ ማጧጧፍ ነው…‹‹ፍለጋው አያልቅም..›› የሚለውን እያቀነቀንኩ ተሰማራሁ፡፡..ውሀ አጣጬን ፍለጋ..ውይ የኔ ነገር እዚህ የመን ውሀ አጣጭ ሳይሆን ለስላሳ አጣጭ ነው የሚፈለገው ቢባል ያስኬዳል..የሚረክሰው ለስላሳው ነዋ!...ውሀ 70 የየመን ሪያል  ሲሸጥ ፔፐሲ 50 ሪያል ነው፡፡
    
    ለቅሶ ቤትም፣ ሰርግ ቤትም ብቻ የሄዋን ዘር የምታተኩርበት ቦታ ሁሉ አይኔን ማተርኩ፡፡ አንዴማ በቃ! ደም ግባትዋ ይጣራል ብዬ አስኔን ስባው..ስባው ሊወጣ ጥቂት ሲቀረው ፈገገች፡፡ ተመስጌን ብዬ ፈጣሪዬን በሆዴ አመስግኜ እኔም ፈገግሁ፡፡ ልብ ስል እይታዋ ከኔ የዘለለ መሆኑን አወኩ እና አይንዋን ተከትዬ ላኩት አይኔን፡፡ እኔ በአካል ኦርጅናሉ ቁጭ ብዬ እስዋ ለካ የምትፈገው ግርግዳ ላይ ከተለጠፈ የፈረንጅ ፎቶ ኮፒ ጋር ነው፡፡ አስቡት እሲኪ አያናግራት፣ አይመልስላት እሱ ላይ የምታፈጠው ምነው፡፡ እኔ በአካል ያለሁትን ትታ....ካንተ ይልቅ የተለጠፈ የፈረንጅ ፎቶ ይሻላል ማለቷ እንደሆን የገባኝ ረፍዶ ነው፡፡ ፍለጋው አያልቅም ብዬ ብነሳም አሰልቺ ሆነብኝ እና እስኪ ሀሳብ የሚጋራ የወንድ ጓደኛ ልያዝ..የሚል ሀሳብ መጣብኝ፡፡

በእርግጥ የወንድ ጓደኛ የሚሆን ማግኘት ይቸግራል፡፡ እዚህ ያለ ወንድ ሁሉ ሴት ነው እያሉ ሴቶቹ በአደባባይ ሲያውካኩ ስሰማ ተጠራጥሬ እንትኔን ሁሉ ፈልጌያለሁ፡፡ ተመስጌን በእሱ ከሆነ አለኝ፡፡ ሌላው ስለሌለው ይሆን ሴት ያስባለው? እንጃ!!! ምን ይሆን ሴት ያስባላቸው? ታዲያ ክንክን ቢለኝ፣ ሴት ለመባላቸው ሰበብ ምህኛቱ ቢያጥረኝ…ጥሪው ቢጎስጠኝ፣ ቢጎረብጠኝ…መንስዔውን ለማወቅ ዳከርኩ፣ ተውተረተርኩ…በዚህ የተነሳ በእኔው ጥናት እንኳን ሁለት ነገር አገኘሁ፡፡

     ‹‹የታዘሉ ወንዶች..›› የሚል ስያሜ የሰጠኋቸውን እና ‹‹ባልጦ የለበሱ ወንዶች›› የሚል ስያሜ የሰጠኋቸውን ግሩፖች ለየሁ፡፡ ‹‹የታዘሉ ወንዶች..›› ያልኳቸው የሴት እጅ ጠብቀው ጉርሳቸውንም፣ ጫታቸውንም፣ ልብሳቸውንም..የሚሸፍኑ ሲሆኑ ከእነዚህ ውስጥ በአንድ ያልተወሰኑ እንደ እሳት አደጋ ሰራተኛ ስሜት በተቀጣጠለበት ዞረው አስክነው የሚኖሩም አሉበት፡፡

      ‹‹ባልጦ የለበሱ ወንዶች..›› ባልጦ የሚባለው እዚህ የመን ውስጥ ሴቶች የሚለብሱት ጥቁር ቀሚስ ነው፡፡ ያን- ቀሚስ ሳይለብሱ መውጣት ነውር ነው፡፡የሴትነታቸው  መገለጫ ነው፡፡ ወሬ ቀደው ወሬ ሰፍተው..ወሬ ደርተው ወሬ በልተው..የሚኖሩ በመሆናቸው ባልጦ የለበሱ ወንዶች ብያቸዋለሁ፡፡

      ሳስበው እና ሳስባቸው የሚገርሙኝ ነገሮች ብዙ ናቸው፡፡ ዘይገርም ሻሸመኔ ይባል ነበር አሁን ዘይገርም ሰነዓ ልል ነው፡፡ ስደት ከገባሁ ጀምሮ ብዙ ነገሮች ስለምታዘብ ከላይ የጠቃቀስኳቸውን እና ሌሎች ነገሮችን መታዘብ ቻልኩ፡፡ ያለውን የፍቅር ሁኔታ ሳጠና ግን ሜትሪዎሎጂው የሚያመለክተው እንደሚከተለው ሆኖ አገኘሁት፡፡ ታዲያ ልብ ይበሉ ይህ የፍቅር ሜትሪዎሎጂ በየመን ያለ ሀበሻን ትኩረት አድርጎ የተጠና የእኔ ምስኪኑ ጥናት ነው ..….ከፈለጉ ሜትሪዎሎጂ ሚለውን ትተው ሚስኪኖሎጂ..ሊሉትም ይችላሉ፡፡
                      የፍቅር ሜትሪዎሎጂ በሰነዓ

    ፍቅር ፍቅር ነው፡፡ፀባዩም ተለዋዋጭ ነው..ልክ እንደዘመኑ ሰው፡፡ እንደ ሌባ ኪስ ኪስ የሚያይ ፍቅር አለ፡፡ እንደታክሲ./ከፒያሳ ቄራ..ከአጣና ተራ ኮተቤ../ የሚያዞር ፍቅር አለ፡፡ እንደ ዲጄ ቴፕ የሚያስጎረጉር፣ ካሴት ሲያስመርጥ የሚያስውል ፍቅር አለ፡፡ እንደ አልቃሽ አስለቅሶ እንደኮሜዲ የሚያስቅ ፍቅር አለ፡፡ እንደጨጓራ በሽታ እህል የማያስበላ፣ እንደመጥፎ ህልም እንቅልፍ የሚያባርርም ፍቅር አለ፡፡ እንደ 15 ልጆች አባት መንገድ ለመንገድ ለብቻ የሚያስወራ፤ እንዳልተያዘ የቤት ጣጣ ጨርቅ የሚያስጥል፤ እንደትራፊክ መንገድ አስገትሮ የሚያውል ፍቅር አለ፡፡ እንደ ፓስታ የሚያምዝለገልግ፣ እንደ ፔፕሲ የሚያገነፍል፣ የሚያስቆዝም የሚያስተክዝ ፍቅር አለ፡፡ እንደጥፍር መቁረጫ ጥፍር የሚያስከረክም ፍቅር አለ፡፡ አይኑካ የሚባል በአይን የሚገባ ፍቅርም አለ፡፡ ፍቅር አይነቱ ተቆጥሮ አያልቅም፡፡ ዘመን እየጠበቀ እንደዘመኑ ከሰዉ ጋር ይለዋወጣል፡፡ እንደ አየር ሁኔታው ይሞቃል ይቀዘቅዛል፤ ይበርዳል፡፡ ታዲያ ብርዱ በ60 መርፌ አይመለስም፡፡ በ60 ዙር አልጋ መውደቅ ላይም ፤ላይመለስ ይችላል፡፡ ስለፍቅር ሁሉም ያስባል ያልማል፤ ይፈላሰፋል፡፡ ከዱብዳው ግን ማምለጥ የሚቻለው የለም፡፡ ሲመጣ ማጣጣም እና መጣጣም ነው ዋናው፡፡ መኝታ ቤት፣ መናፈሻ፣ መዝናኛ ቦታ፣ ፊልም ቤት፣መንገድ ላይ ፣ ጓሮ ፣ቢሮ ውስጥ …ብቻ ቢያሻዎት ሽንት ቤትም ቢሆን ሊያጣጥሙት ይችላሉ፡፡ እንደ ፍላጎትዎ..እንደመሩት እንደመራዎት እንደ አመቺነቱ እንደቀልብያዎ..ሊያጣጥሙት ፣ ሊያጣጥሞትም ይችላል፡፡ ስለዚህ የፍቅር ሜትሪዎሎጂውን ማውቁ……

  ፍቅር በተመላላሽ፡-የሰነዓን አየር በአማከለው ሁኔተታ..ስራ አዳሪ ተቀጥረው እየሰሩ..የፍቅርን ንፋስ ሀሙስ እና አርብ ብቻ ለሚያጣጥሙትን ነው የሚመለከተው  ስራ በአዳሪ ፍቅር በተመላላሽ የሚባለው፡፡

    ፍቅር በአዳሪ፡- ሀሙስ እና አርብ አይበቃም ብለው ተመላላሽ ለሚሰሩ ቤታቸው ለሚያድሩ የሚያንዣብብባቸው ጠንካራ ሀሳብ ነው፡፡

    ፍቅር በኮንትራት፡- ጠንከር ብሎ አላስበላ፣ አላስጠጣ ሲል እና ስራ አስትቶ ቤት ሲያስውል ነው፡፡…ስንፍና ሲጨመርበት እና እጅ እጅ ሲያሳይ ባለው ሁኔታ ተጠቂዎቹ ወንዶች ናቸው፡፡

   ፍቅር በቶክ ሾው፡- እየተገናኙ ለረጅም ሰዓት በወሬ ብቻ የሚያሳልፉ ፍቅረኞችን የሚያመላክት ነው፡፡ጀማሪዎች ላይ ይጠረነክራል፡፡

እግረኛው ፍቅር፡- በእግር ጉዞ ተጀምሮ ዛል እስኪሉ ወክ የሚገባበዙትን ያማከለ ነው፡፡

ፍቅር በቀን ስራ፡- ተባራሪ ለአንድና ከዛ በላይ ለሆነ ጊዜያዊ መውደቅ የሚሞከር …በድንገተኛ የስሜት ተጠቂዎች ላይ ያንዣብባል፡፡

    ውጤት ተኮር ፍቅር፡- የሚያስገኘው ጥቅም ከግምት ውስጥ ገብቶ ያዋጣል አያዋጣም ተብሎ በውጤት ተኮር ጥናት የሚመሰረት ነው፡፡ውጤት ካላስገኘ ምላዕተ ጉባዔው ይወስን፣ ርቄን ማቄን፣ አስቸኳይ ስብሰባ ሳይባል አዲስ ስልት ሊያስቀይስ ወይም ማፈግፈግን ሊያስከትል ይችላል፡፡ ‹‹…የተሸለ..ካገኘ ድርጅቱ በጨረታው አይገደድም›› እንደሚለው ማስታወቂያ ማለት ነው፡፡ ይሄ እንደነጋዴ ጥቅም ብቻ ታርጌት ያደረገ ነው፡፡

ወጪ መጋራት፡- ይሄኛው ሁሉን በጋራ ለማድረግ የሚፈልጉት ላይ የሚታይ መተሳሰብ የሞላበት ነው፡፡

ቱሪዝም፡ በውጭ ዜጋዎች ላይ ያተኮረ ሀብተም ከደሃ ያለየ ብቻ ነፍስ ኖሮት የሚንቀሳሰቀስ የውጭ ዜጋ ላይ የሚያተኩር ቢያንስ ከሀገር እንዲያስወጣ የሚያገለግልበት ሁኔታ የሚጠናበት ነው፡፡

  11ኛው ሰዓት፡- እድሜ ነጉዶ ከሽበት ጋር ያጣመዳቸው ሹገር ዳዲ እና ሹገር ማሚን እያሳደዱ ማጣጣም ላይ ተመሰረተ ነው፡፡

አይኑካ፡- እስር ቤት ውስጥ ከወንዶች ክፍል ወደ ሴቶች ክፍል ወይም በተቃራኒው መስመር የሚወረወር ምልከታ ብቻ ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ በተረፈ በዚህ ሳምንት እንደ ወትሮው ከፊል ደመናማ/ፀባማ/ ከፊል ፀሀያማ/ፍቅራማ/ ሆኖ ይሰነብታል፡፡
 ብዬ ተነተንኩት እና እርፍ ማንም ልክ ነህም አይደለህም ሊለኝ ይችላል፡፡ ግን ማን በእኔ እይታ አየው? ስለዚህ…..   
   
    አፈር ስሆን እስካሁን ማነህ አላላችሁኝ እኔም እገሌ ነኝ አላልኩ፡፡ ይህ ታሪክ የጸሀፊው አይደለም፡፡ ፀሀፊው የፈጠረኝ የእኔ የፍጡሩ ታሪክ ነው፡፡ አንተ ማነህ ካላችሁ ለስሜ አልጨነቅም፡፡ ከበደም በሉኝ በለጠ፣ መሀሙድ በሉኝ እንድሪስ…መጠሪያው አያጨቃጭቀንም፡፡ ለእኔ ስሜ ምግባሬ ነው፡፡ አልዳሰስ አልከሰስ…ሳልፈጠር በፍጡር የተፈጠርኩ፡፡ ያለነበርኩ በእሱ ዘንድ የኖርኩ፡፡ ለእናንተ እንግዳ ነኝ፡፡ ለፀሀፊው እስኪፈጥረኝ አርግዞ እስኪወልደኝ ምንያህል እንዳማጠኝ እሱኑ ጠይቁት፡፡ ለስሜ አልጨነቅም ማንነቴን የምነግራችሁና ምግባሬ ይገልጸዋል እውነቱን ይዞ መሄድ ነው ፍላጎቴ፡፡ ለስሙ ከሆነ በፈለጋቸሁት ጥሩኝ ግን ማን ብባል ነው ደስ የሚላቸሁን? ስም ነገሩኝ እስኪ…  በዚህ ዘመን ለበዛ ትርጉም አልባ ስም ችግር አንዱን ለጥፉልኝ እግር የለም አትከፍሉበት፤ አይፈልጣችሁ አይቆርጣችሁ ደስ ያላችሁን አንሱ እና…
ትርጉም ያለው ቢሆን ግን ደስ ይለኛል፡፡
    
የከርሞ ሰው ይበለን እንጂ ጥቁሯ ቦርሳዬ ውስጥ ስላለው ነገር እናወራለን ገና፡፡                            
                            
                                   ቸር እንሰንብት

Wednesday, December 21, 2011


                  ሀበሻ በየመን
     ለመሆኑ እንዴት ናችሁ? አቀማመጣችሁን አላልኩም። ኮምፒዩተራችሁ ላይ አፍጥጣችሁ ይመስለኛል የምታነቡት። እሺ በስደት ያላችሁ..የስደት ኑሮ ቅብብሎሹ እንዴት አድርጓችሁዋል? እንዴ ምነው ተገረማችሁ? ልክ ነኝ እኮ ኑሮ ቅብብሎሽ አይደል እንዴ? ሰኞ ወደ ማክሰኞ ሲጠልዘን፤ ማክሰኞ ተቀብሎ አባብሎ ወደ ረቡዕ ሲወረውረን .. መስከረም ወደ ጥቅምት ሲጠልዘን፤ ጥቅምት ለህዳር፣ ህዳር ለታህሳስ…እያለ ቅብብሎሹ በርትቶ ጠውለዛው ደርቶ እዚህ ደርሰን የለ? አሁንም ቅብብሎሹ አንዱ ወደ አንዱ መለጋቱ  እንደቀጠለ ነው። ገና እንለጋለን፤ እንጠለዛለን። ስንት አመት ይሆን በቅብብሎሹ ውስጥ የምናሳልፈው?...

      አቦ ዛሬ ጣፋጭ ወግ እናውጋ ነው የሚባለው የብሶት ቁስል እንከክ እንበለው? ስለስደት ብናወራ አይመቻችሁም? ከስደትም ስደት አስከፊውን የአረብ ስደት…ከአረብ ሀገርም ስለየመን እናውራ። ምነው  ፊታችሁ ጨፈገገ? የስደት ነገር ሲነሳ ቤተሰብ ትዝ አላችሁ? ወደ እውነታው እንምጣ ከኑሮ ጋር ያለውን ትግል ለማሸነፍ ፣ ለመሸነፍም ቢሆን የትግል ሜዳ አድረጋችሁ የመረጣችሁት የመንን ነው እንበል። የመንን በሀሳብ ለመቃኘት ተዘጋጁልኝ። የመን ደሞ ጥሩም አለ መጥፎም አለ። ሞቱም፣ ዱላውም፣ መደፈሩም፣ ማግኘት፣ ማጣቱም ሁሉም አለ። ከሌሎች በከፋ ሁኔታ አለ።

      የመንም ይኖራል። ለጉድ!!..ይኖራል። ኑሮ ከተባለ ሀበሻ በየመንም እየኖረ ነው ማለት ይቻላል። ይህም ስደት ነው። ወደ ተሻለው ሳይሆን…ብዙ ብዙ እውነት የማይመስሉ እውነቶች የተሰገጡበት ህይወት ነው በየመን ያለው። ኑሮ ካሉት ፍሪጅም ይሞቃል ኮካኮላን ያስተረተው በየመን ያለ ሀበሻን ኑሮ ታይቶ ነው ማለት ይቻላል። አይደለም ካላችሁም አሁን እኔ ብያለሁ። ማነው የሚከራከረኝ? ከየመን በከፋ ሁኔታ ላይ ሱማሊያ የሚኖሩ መኖራቸውን ሳትረሱ ማለት ነው። አትቸኩሉ እኔው እነሱንም አሳያችሁዋለሁ።

      ችግር የማይነቅለው የለም። ኢየሱስ ክርስቶስም ተሰዷል። ነብዩም ተሰደዋል። አረ ቆራጡ እና ተፈጥሮን በቁጥጥር ስራ እናውላለን ያሉት ኮረኔል መንግስቱም ተሰደዋል። እኛ ለስደት አዲስ አደለንም። አለም ለስደት አዲስ እንዳልሆነ ሁሉ እኛም እየተሰደድን ነው። ተሰደናልም ገናም እንሰደዳለን።

    ሀበሻ በየመን እጅጉን አሰልቺ የሆነ ደግሞም ያልሆነ ዝብርቅርቅ ህይወት ከጥሩ ጎኑ መጥፎው ያመዘነበት ኑሮ መሀል ተሰንጎ ነው የሚኖረው። እርስ በእርስ የጎሪጥ መተያየት፣ ጥርጣሬ.. የበዛበት ነው ህይወቱ። መሰደብ.. <<ያ-ሀበሺ..ሸቃላ..ኦሪያ..ያ ሱማሌ..ያ አስወድ..>> የዘውትር መጠሪያ ኤጭ!..ድሮስ ክብር በሀገር አይደል? ነው እንጂ። ክብር በሌለበት ተንቆ፣ ተዋርዶ መኖር ያውም ከራስ ባልተሻለ ሰው። የመን ያለ የሀበሻ ቁጥር እንዲህ በዋዛ የሚሰላ አይደለም። በህጋዊ መንገድ ያለውና ህጋዊ ያልሆነው ከ70- 80 ይደርሳል ተብሎ ይገመታል። ታዲያ ይገመታል ነው። ይበልጣል እንጂ አያንስም። ወደ ሳዑዲ አረቢያ ተጓዡም ቀላል ተብሎ የሚጠራ አይደለም።

     በእናታቸው፣ በአባታቸው፣  አልፎም በአያታቸው ኢትዮጵያ የሆኑ…ግማሽ ጎናቸው የመናዊ ትውልደ ሀበሻ 5.000.000/ አምስት ሚሊዮን/ አካባቢ ናቸው። ይህ የሚያሳየው የየመንና ኢትዮጵያ ትስስር የጥንት መሆኑን ነው። በፊት የመኒዎች በችግር ወደ ሀገራችን ይሰደዱ ነበር። ዛሬ ነገር ተገልብጦ እኛ ወደ እነሱ  ሆኗል። አሁንም ቢሆን ግን ኢትዮጵያ ያለው የመናዊ ቁጥር በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ነው። ከዚህ ከዚህ ጋር በተያያዘ ሳይሆን አይቀርም የመን ከአረቢኛው ቀጥሎ አማርኛ በሰፊው ይነገራል።

    <<ገንዘብ ካለ…>> ሁሉም የመናዊያን የሚያውቋት ተረት ናት።<<እወዲሻሎ..ኢንደሚኖ…አንቺ..>> በሁሉም ዘንድ የተለመደች ቃል ነች። ልክ እኛ ጋር ማዘር ፋዘር..እንደተለመደ ሁሉ። ጫት ሲነሳ ሐረርን የማያነሳ የመናዊ የለም።

    የዛሬዋ የመን ጥንት ወይም በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ <<ሀገረ ናግራን>> እንደምትባል ታሪክ ያስረዳል።በመጽሀፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ <<ኤደን>> ደግሞ <<አደን>> ተብሎ መለወጡን አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ። ዋና ከተማዋ ሰነዓ ጥንታዊነቷን ለማስረገጥ ከንግስት ሳባ የንግስና ዘመን ጋር ቁርኝት እንዳለው ይጠቀሰል። የመናዊያን ንግስት ሳባ ኢትዮጵያዊ ሳትሆን የመናዊ ነች ብለው ያምናሉ። ግብጾች የእኛ ናት እንደሚሉት ማለት ነው። ሳባ የመን ውስጥ ማሪብ የተባለ ቦታ ቤተመንግስት አላት። ምክምያታቸው ይህ ብቻ ነው። አባቷ ማነው? እንዴት ንግስት ሆነች ምላሽ የላቸውም። ምሁሮቻቸውም ሳባ ኢትዮጵያን አስተዳድራለች እንጂ ኢትዮጵያዊ አይደለችም ሲሉ ሽንጣቸውን ገትረው…ሽንጥ አላቸው እንዴ? እንጃ!.. ብቻ ለአባባሉም ቢሆን እንበለውና ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከራሉ።

      በአንድ ወቅት ፋጡማ ሁሬቢ… ከተባለች እንጋፋ የየመን ጋዜጠኛ ጋር የጦፈ ክርክር አድርገናል።
   
    <<ለመሆኑ ኢትዮጵያ በውጭ ንጉስም ይሁን ንግስት የተዳደረችበት አጋጣሚ አለ ወይ? እንደዚህ አይነት ታሪክ አንብበሽስ ታውቂያለሽ? ካልሆነ ግን ድንገት አለም ያለወቀው ታሪክ ልናገኝ ነው ማለት ነው እና ማስረጃውን ስጭኝ?>> አልኳት። <<እምቢኝ!...ያባ ቢላዋ ልጅ ለማን ተገዛንና የመንን የእኛ ንጉሶች ማስተዳደራቸውን እንጂ እኛ በየመናዊያን ስለመተዳደራችን ማን ተናገረና ያለመረጃ ልቀበል?እምቢኝ……የአባት፣ አያቴን ታሪክ መድገም ቢያቅተኝ ጠብቄ እኖራለሁ>> እያለ ውስጤ ፉከራ ይሁን ቀረርቶ ብጤ ፎካከረ። ከሌሎች ጋርም እንዲሁ ተከራክሬያለሁ። እነሱን ለመርታት ከመሞከር ይልቅ ድንጋይ መፍለጥ ይቀላልና በእንጥልጥል እተወዋለሁ።

      ከክርስቶስ ልደት በሁዋላ በ575 ዓ.ም ጀምሮ ንጉስ አብርሃ ለ50 ዓመታት ልጆቹ 20 አመት የመንን ባስተዳደሩበት ወቅት አሁን ያለንባት ሰነዓ ከተማ ለአቢሲኒያ ዋና ከተማ ሆና አገልግላለች። በዛ ዘመን የተገነቡ ቤቶች ዛሬ ባብል የመን /የየመን በር/ በሚባለው ኦልድ ሰነዓ አካባቢ አሉ። የየመን ዋና የቱሪስት መስህብ ነው። በፎቶው ላይ የምታዩት ማለት ነው። ከአንድ ሺህ አመት በላይ ያስቆጠሩ 14000 ቤቶች አካባቢ አሉ። ሌላው ስለየመን አንስቶ ሳይወሳ የማይታለፍ የእርሻ ዘዴያቸው ነው። ለም አፈር የወርቅ ያህል ውድ ነው። ከመሬቱ ደረቃማነት የተነሳ የሚታዩትን አትክልቶች፣ የእህል አይነቶች ሲያዩ የመናዊያን ምን ያህል ጠንካራ እንደሆኑ ምስክሮች ናቸው። ለም የሆነውን አፈር ከሩቅ ቦታ ፈልገው ጭነው ያመጣሉ፣ ውሀ ከመሬት ለማውጣት እስከ 300 ሜትር ይቆፍራሉ።ያወጡትን ያጠጡታል፣ የፈለጉትን ይዘሩበታል። ያ- ደረቅ ድንጋያማ መሬት ህዝቡን አጥግቦ ያድራል።

     ሌላም ስለየመን ሲነሳ ሳይወሳ የማይታለፍ አለ።

    ጫት…….ጫት የህዝቡ መንቀሳቀሻ የደም ሴል ነው ማለት ይቻላል። ያለ ጫት ህይወት ያለ የማይመስላቸው ያገኙትን ሁሉ ለጫት የሚያውሉ ጥርሳቸው አልቆ ተፈጭቶላቸው በማንኪያ ሁሉ የሚወስዱ አሉ። በቀን ከ25000 ሺህ ሪያል በላይ /ከመቶ  አስር ዶላር በላይ/ ለጫት ወጪ የሚያደርግ ቤተሰብ በብዛት እንዳለ በአንድ ወቅት የመን ታይምስ ለንባብ ያበቃ መሆኑን አስታውሳለሁ።

    የመን ያለ ሀበሻ ባህሪውን፣ አብሮነቱን፣ መተሳሰቡን፣ ፍቅሩን፣ መተዛዘኑን፣ መደጋገፉን፣ መነቃቀፉን፣ ወሬ መውደዱን፣ ተንኮሉን፣ አብሮ መብላት መጠጣቱን፣ ሀሜቱን፣ በነገር መነቋቆሩን…ይዞ ነው የተሰደደው። ሀበሻ እርስ በእርሱ ፍቅር አለውም የለውምም የሚያሰኙ ብዙ እንከኖች አሉት። እዚህ ያለ ሀበሻ የወሬ ፍቅር አለው።

     ወሬ ይወዳል።

     የምን ወሬ ይወዳል ብቻ ነው? ወሬ በልቶ ወሬ ጠጥቶ፤ ወሬ ቀዶ ወሬ ሰፍቶ ነው የሚኖረው ያሰኛል። የመን ውስጥ ሀበሻ በገንዘብ እና ዕቃ ስርቆት አይደለም የሚታወቀው። ብዙም አይጠረጠርም። ስልክ ሰርቆ በመደወል ግን የሚያህለው የለም። ሱሱ ወሬ ነዋ!! ያማል ያሳማል።

    እዚህ ያለ ሀበሻ ሁሉ ህጋዊ አይደለም። በህጋዊ መንገድ የገባም አይደለም። አገባቡ በሁለት መንገድ የተከፈለ ነው። በባህር እና በአየር ነው የሚገባው። በባህር የሚገቡት የሚደርስባቸውን ስቃይ በተመለከተ ጥቂት ልበል።      
   
      ስለ የመን አሰቃቂ ጉዞ ከዚህ በፊት በባህር ስለሚደረግ ጉዞ፣ ሬሳው በየቦታው ውደቆ፣ የባህሩ ውሀ ሰውነት ላይ የሚፈጥረው ችግርን በተመለከተ …ያሰባሰብኩትን መረጃ በቪዲዮ መልክ አዘጋጅቼው ስለነበር እንድታዩት አስቀምጨዋለሁ። እዩት…
    
                                         በቀጣዩ እንገናኝ……….